“… እኛ ለክብሩ ምስጋና እንሆን ዘንድ ነው ።” ኤፌ. 1፡12።
መናገርም መስማትም የማይችል ፣ አካሉም ለመሥራትና ለመንቀሳቀስ ደካማ የሆነ ወጣት ነው ። ይህ ወጣት በምልክት ቋንቋም ለመነጋገር ያንን አልተማረም ። ካለበት ገጠር መጥቶ በሰለጠነው ከተማ ተቀመጠ ፣ ወትሮም እዚህ ተወልዶ ገጠር ያደገ ነበር ። አንድ ቀን ብስጭት ብሎ ከቤተሰቡ ተጣልቶ ወጣ ። እንደ ልማዱ ሲበርድለት ይመለሳል ብለው ቢጠብቁት እንደ ወጣ ቀረ ። ዓመታት በተቆጠሩ ቍጥር ጥፋቱ የእኔ ነው የሚል ራሱን የሚከስስ በቤተሰብ ውስጥ መፈጠር ጀመረ ። “ያን ቀን ምነው ባልተናገርኩት” የሚል ጸጸተኛ ብቅ እያለ መጣ ። ከሁሉም በላይ እናት እህ እያሉ የአልጋ ቁራኛ ሆኑ ። አየሁ ሰማሁ ፣ ያየሁ መሰለኝ የሚል ምልክት በተገኘበት ሁሉ መሮጥ የዚያ ቤተሰብ ሥራ ሆነ ። ገና ከጠዋቱ ዕድሉ ለመከራ ተጽፎ ፣ በሽታና እንግልት የተፈራረቁበት በመሆኑ የሚያውቀው ሁሉ ማዘን ጀመረ ። ቤተሰቡም ጭንቀቱ እየበረታ ሲመጣ “አንቺ ነሽ” “አንተ” በሚል መካሰስ ውስጥ ገባ ። “አዲሱ ሬሳ የቆየውን አሥነሣ” እንዲሉ ከልጅነት ጀምሮ እየተረኩ ለመጣላት የተዘጋጁ መሰሉ ። በዚህ ሁሉ ጭቅጭቅ ውስጥ ሁሉም በየራሱ ወጣ ብሎ ፈልጎ ይመለሳል ። ያ ወጣት ግን ሕልም እልም ሁኗል ። “ቀብሬው ቢሆን ኖሮ አይቆጨኝም ነበር ፣ ከዘመድ ጋር አልቅሼ ይወጣልኝ ነበር” የሚል ድምፅ እየጨመረ መጣ ። “ደኅና ነዎት ወይ?” ስላቸው እኒያ እናት፡- “ምን ደኅና ነኝ ፣ ልጄ አብሉኝ አጠጡኝ እንኳ እንዳይል አንደበት እንኳ የለው ፣ ይህን ሳላይ ምነው በሞትሁ” ይላሉ ።
አንድ ታላቅ ገዳም ቆይቼ ለዓይን ያዝ ሲል በምሽት ጉዞ ጀመርሁ ። ቤተ ክርስቲያኑን አለፍ እንዳልሁ የሚለምኑ ድሆች በቀኑ ውሎአቸው ተስፋ ቆርጠው ይሆን ተስፋ አድርገው ለመተኛት ይሰናዳሉ ። ድንጋይ ላይ ተቀምጠው ውለው ፣ አፈር ላይ ለመተኛት ሲሰናዱ በጨለማው ውስጥ በጥቂቱ ይታያሉ ። እኔም ግራ ቀኙን አማተርሁ ። ድንገት አንድ ወጣት መኝታውን እያነጠፈ ፣ አፈር ከመሰለው መልኩ ጋር አፈር የመሰለ ልብስ አፈር ላይ ያነጥፋል ። ልብሱም ከአፈር አይሻልም ፣ አፈርን ለመሸሽ አፈር ላይ አፈር መሳዩ ያነጥፋል ። አፈር ሰው ፣ አፈር መሳይ ልብስ ፣ የልብሱና የሰው መገኛ የሆነው አፈር በደንብ ይታዩኛል ። መኝታውን እያነጠፈ ወደ ግራ ዞር ብሎ ፈገግ እያለ ያየናል ። አዝነን ብንሰጠው ተመኝቶ ቀኑን ከመዝጋቱ በፊት እንድ ምጽዋት ናፍቆ ይሆናል ። እኔም ልቤ ደነገጠ ። ያየሁትን ማመን አቃተኝ ። እንዳያውቀኝ ዞር ለማለት ሞከርሁ ። ያ የጠፋው ልጅ ነው ። ስልክ አነሣሁና ወንድሙ ጋ ደውዬ “ወንድምህ ተገኘ ወይ” ብለው “በፍጹም” አለኝ ። “አገኘሁት” ስለው ስልኩን ሌሎች ቤተሰቦች ነጥቀው ጠየቁኝ ። በፍጥነት እየበረርን አዲስ አበባ መጣን ። ሰዓቱ ከምሽቱ 2፡30 ሆኗል ። ቤቱ በጎረቤት ተሞልቷል ። ወንድሙም ጥሩ ልብስ አዘጋጅቶ ፣ ድሬቶዬን አልጥልም ቢልስ ብሎ መያዣ ነገር ከረጢት አዘጋጅቶ ነበርና በመጣንበት ፍጥነት ሄድን ።
ያንን ወጣት ሲያነጥፍ አይቼዋለሁና ባትሪ አበራንበትና አሥነሣነው ። እኛ መሆናችንን ሲያውቅ የሚሆነውን አጣ ። መሬት ላይ ይወድቃል ፣ ይነሣል ። በዙሪያው የነበሩ ድሆች በሙሉ ማልቀስ ጀመሩ ። ወንድሙም ከደስታውና ከመተቃቀፉ በኋላ ልብሱን በሙሉ ቀየረለት ። የፈራው አልቀረም ፣ ድሪቶዬን አልጥልም አለ ። ድሪቶውን ከኋላ ጭነን እርሱን ከፊት አስቀምጠን ለመሄድ ስንነሣ ድሆቹ ወገኖቻችን፡- “ምነው እኛንም እንዲህ የሚሰበስበን ባገኘን” ብለው ስንሄድ ምርቃትም ምኞትም አስተላለፉልን ። ለካ ያ ልጅ የእናቱን ቤት ያገኘ እየመሰለው ሲጓዝ መመለስ አልቻለም ነበር ። እቤት ስንደርስ እገሌ ተገኘ ተብሎ ሰው ሁሉ እንቅልፉን ትቶ ወጥቶ እየጠበቀን ነው ። የእናቱን ቤት የተከራዩ ብዙ ተከራዮች ከነልጆቻቸው ወጥተው እየጠበቁን ነው ። ደስታው ምስጋናው ድብልቅልቁ ወጣ ። እኔንም ሁሉም እየተነሣ ያቅፈኛል ፣ ያመሰግነኛል ። ፈልጌ እንዳገኘሁት ተቆጠርሁ ። በዚያ ጨለማ እንዴት ላየው እንደ ቻልሁ አምላክ ብቻ ያውቀዋል ። ተገኝ ሲለው መላ ያዝለታል ከማለት ውጭ ምን ይባላል ? ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ያቺን ቀን እያስታወሱ ያመሰግኑኛል ፣ ላልሰማ እርሱ ነው እያሉ ይመሰክሩልኛል ።
ለካ አዳም ትእዛዝን ባለመስማቱ ፣ የእግዚአብሔርን ፍቅር ባለማየቱ ጠፍቶ የነበረው እንዲህ ነው ። ለሰማይ መዳረሻ ተፈጥሮ ሳለ አሁን ግን የመጣበትን አፈር ሲያርስ ኖሮ መልሶ አፈር ይሆናል ። የሕይወት ታሪኩ ሲነበብም “ከአፈር ተፈጥሮ ፣ በአፈር ሲጫወት ኖሮ ፣ ወደ አፈር ተመለሰ” የሚል ነው ። ይህ ግን የእግዚአብሔር አሳብ አልነበረም ። አዳም በጨለማው ፣ በመቃብሩ ፣ በአፈር መኝታው በተገኘ ጊዜ ቅዱሳን መላእክት የሰማይን ደጅ ከበው ይጠብቁ ነበር ። ሁሉ እያለው ሁሉ የሌለው ሁኖ በመኖሩ ፣ እመለሳለሁ ሲል መጥፋቱ ፣ ደረስሁ ሲል መራቁ በሰማይ ኀዘን ፈጥሮ ነበር ። አዳም በአጋጣሚ አልተገኘም ። አዳም በታላቅ ፍለጋ ፣ በደም ዋጋ ተገኘ ። የተገኘው አዳም በታየ ቍጥር ያገኘውን ክርስቶስ ሲያመሰግኑት ፣ ሲስሙት ፣ ሲመሰክሩለት ይኖራሉ ። አዳም ለክርስቶስ ምስጋና ሕያው ርእስ ነው ።
ሐዋርያው እንዲህ አለ፡- “… እኛ ለክብሩ ምስጋና እንሆን ዘንድ ነው ።” ኤፌ. 1፡12።
የኤፌሶን መልእክት ትርጓሜ /22
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 10 ቀን 2014 ዓ.ም.