የትምህርቱ ርዕስ | አልለውም

አንቱ የምለውን ሰውዬ ፣
አንተ አልለውም አቃልዬ ፤
ዓባይ ይጎድላል እንኳን ሰው ፣
ጊዜ ሲያዋርደው ።

የቅጥር ተሳዳቢዎች አሉ ። ከተከፈላቸው ለሰው ጠብ ተሳዳቢ ይሆናሉ ። አልቃሽ በሚቀጠርበት ዓለም ፣ ዘፋኝ በሚጠራበት ምድር የሚሳደብም ይገዛል ። ይህች ምድር ብዕራቸውን ያረከሱ ፣ አንደበታቸውን ያጎደፉ ፣ በሐሰት ምስክር ሃይማኖታቸውን የጣሉ ፣ ሌላውን ዝቅ በማድረግ እንጀራ ለመብላት የሚጥሩ ሰዎችን ተሸክማለች ። እገሌ ሞተ ሲሉን ከማዘን ይልቅ ቀብሩ የት ነው ? ብለን የምንጠይቀው የአዩኝ አላዩኝ ኑሮ ስለምንጫወት ነው ። የወደቀን ሰው ለማቃለል የምንሽቀዳደመው ቀድሞም ያከበርነው በሐሰት ላይ ተመሥርተን ነው ። የምናከብረው ውብ ፀጉርን ከሆነ ፀጉሩ ላሽ ሲበላው ፣ በራነት ሲያጠቃው ሰውዬውን እንጠላዋለን ። የምናከብረው ለገንዘብ አለመሰሰቱን ከሆነ የሚሰጠው ያጣ ቀን እንርቀዋለን ። የምናከብረው ቁመናውን ከሆነ እጅ እግሩ ታስሮ ቤት ሲውል ገሸሽ እንለዋለን ። የምናከብረው ተጫዋችነቱን ከሆነ ዱዳ የሆነ ቀን እንጸየፈዋለን ። የምናከብረው ሥልጣኑን ከሆነ የወረደ ቀን እናዋርደዋለን ። የምናከብረው የእርሱ ጎሣዎች እየገዙ ነው ብለን ከሆነ ገለል ሲሉ “ምን ያመጣል ?” ብለን እንተርትበታለን ። የምናከብረው ሃይማኖቱን ከሆነ ሃይማኖቱን የለወጠ ቀን ድሮስ ? ብለን ካከበርነው በላይ እናዋርደዋለን ። የምናከብረው ሥነ ምግባሩን ከሆነ የተሳሳተ ቀን ከሳሽ ወቃሽ እንሆናለን ። የምናከብረው ጥሩ ሰላምታውን ከሆነ ቀዝቀዝ ያለብን ቀን ጠላት እናደርገዋለን ።

የምናከብረው ሙያውን ከሆነ ከሙያው ገለል ያለ ቀን ስልካችንን እናጠፋበታለን ። የምናከብረው ልጅነቱን ከሆነ ሲያድግ እንጠላዋለን ። የምናከብረው ሽምግልናን ከሆነ ወጣቶችን በክፉ ዓይን እናያለን ። የምናከብረው ጾታን ከሆነ እግዚአብሔር በሰጣቸው ነገር ሰዎችን ለምን ወንድ ወይም ሴት ሆናችሁ ብለን እንጋፋቸዋለን ። የምናከብረው ጎበዝ ልጆች ስለወለደ ከሆነ ልጆቹ የሞቱ ቀን እናንጓጥጠዋለን ። የምናከብረው ሰውነቱን ከሆነ ክብራችን ጸንቶ ይኖራል ።

ወንድም ሴትም ሰው ናቸው ። ሰው የወል መጠሪያ ነው ። ሰው የሚለው የተፈጥሮ ስም ነው ። ሰው የሚለው ባሕርያችንን የሚገልጥ ስም ነው ። ጠባያችን ይለዋወጣል ፣ ባሕርይ ግን የጸና ነው ። ጠባያችን ልዩ ልዩ ነው ። ባሕርይ ግን ወጥ ነው ። ሰው መሆን ቀዳሚ ነው ። ሰው መሆን በእግዚአብሔር ፊት እውቅና አለው ። ሰው መሆን ዋጋ አለው ። ሰው መሆን አርአያ ሥላሴ ነው ። ክርስቶስ የሞተው ለሰው ነው ። ለሀብታም ለድሀ ፣ ለጥቁር ለነጭ አልሞተም ። ሰውን ለማክበር ሰው መሆኑ በቂ ነው ። ለወዳጃችን ሰው ሆነን ከመቅረብ በላይ ምንም ማድረግ አንችልም ። ሰው መሆን ንጉሥ ዳዊት ለአልጋ ወራሹ ለሰሎሞን የመከረው ነው ። ንጉሥነትም ሰው አያደርግም ። ሰውነት ተፈጥሮ ነው ። ሰው ሆኖ የተወለደው በምርጫው አይደለም ። ሰው ሆኖ ለመኖር ግን ምርጫ ያስፈልጋል ። ሰውን የምናከብርበት መስፈርት ማንነታችንን ይገልጣል ።

አንቱ ለማለትም አንተ ለማለትም መቸኮል መልካም አይደለም ። አክብረን ስናዋርድ የሰማን ሰው ይታዘበናል ። እየሸሸን ይመጣል ። ቀኑ ወጥ አይደለም ። ጠዋት ቀዝቃዛ ፣ ከሰዓት ሙቅ ፣ ሰርክ ነፋሻ ይሆናል ። ሰውም ወጥ ኑሮ የለውም ፣ ከአየሩ ጋር ሲለዋወጥ ይውላል ። በደስታ የጀመረውን ቀን በሕመም ሊፈጽም ይችላል ። ምድር ብትዞርም በራስዋ ምሕዋር ላይ ሆና ነው ። የምትዞረውም ሰውን ይዛ ነው ። በምትዞር ምድር ላይም ሰው ኑሮው ተዘዋዋሪ ነው ። ኑሮው ቢዘዋወርም ሕይወቱ ግን ቋሚ ነው ። ትላንት ሰጪ የነበረ ዛሬ ለማኝ ይሆናል ። ትላንት አሳሪ የነበረ ዛሬ ታሳሪ ይሆናል ። የትላንት ዳኛ ዛሬ ተከሳሽ ይሆናል ። ትላንት አዛዥ የነበረ ዛሬ ታዝዞ ለመኖር እንኳ ዕድሉን ያጣዋል ። ትላንት ሰገነት የሚለቀቅለት ዛሬ መቃብር ይቆፈርበታል ። ትላንት ስም አጠራሩ ረጅም የነበረ ዛሬ በሁለት ቃል “ሌባ” ይባላል ። ትላንት ጥሩ ሥነ ምግባር የነበረው ዛሬ ተሳስቶ ይሆናል ። የትላንት ዘማሪ ዛሬ ዘፋኝ ፣ የትላንት አማኒ ዛሬ ከሀዲ ፣ የትላንት ሰባኪ ዛሬ ሰነፍ ሆኖ ይሆናል ። ክብራችን ግን እንደ ጥንቱ ሊሆን ይገባዋል ። በማክበር ውስጥ ክቡርነታችንን እናሳያለን ። ክቡር ያከብራልና ። ሰው ሰውን አይንቅምና ።

አባ መስጠት እያለ ያወድስ የነበረ ዛሬ ሲያጡ ድሮም በሌብነት የተገኘ መቼ ይበረክታል ? ካለ ፣ አገር ወዳድ ብሎ ይመሰክር የነበረ “ባንዳ” ብሎ ከሰደበ ፣ ቅዱስ እኮ ነው ብሎ አወድሶ “ሰው መሳይ በሸንጎ” ካለ ፣ “በአንተ መዝሙር ባንተ ስብከት ሕይወቴ ተለውጧል” ብሎ የመሰከረ “ሊያሳስተኝ ነበር” ብሎ ከከሰሰ … ይህ ራስን ማዋረድ ነው ። ሰውን ቋሚ በሆነ አድራሻ ማግኘት ከባድ ነው ። ሰው ሲዋዥቅ የሚኖር ተወዛዋዥ ፍጡር ነው ። ለመጣው ጌታ ሁሉ መነስነስ ፣ ያከበሩትን እያዋረዱ አዲሱን ልዘልህ ማለት ቀላል መሆናችንን የሚያሳይ ነው ።

አንቱ የምለውን ሰውዬ ፣
አንተ አልለውም አቃልዬ ፤
ዓባይ ይጎድላል እንኳን ሰው ፣
ጊዜ ሲያዋርደው ።

ያከበርነው ሰው ዝቅ ብሎ ፣ ራሱን ሸጦ ፣ ቀኑን መስሎ ፣ ኑሮውን ከስሮ ብናየውም ክብራችን ቋሚ መሆን ይገባዋል ። ነገ ለማዋረድ ዛሬ ማክበር አይገባንም ። በዚህ ሕሊናችንን ፣ ሰዎችንና እግዚአብሔርን እናተርፋለን ። እርሱ ለተጎዳው የእኛ ማቃለል ከንቱ ነው ። ክፉ ሰው ቢሆንም በፍርድ እንጂ በበቀል ልናሳምነው አይገባንም ። ጉዳት በራሱ ተናጋሪ ነውና የተጎዳን ሰው መናገር አያስፈልግም ። ራሱን እንዳያይ እናደናግረዋለን ። ክፉ ሰውም መልካም ስናደርግለት ያልዘራውን እያጨደ ነውና እየከበደው ይመጣል ። ከዚህ ሁሉ በላይ ያከበርነውን ማዋረድ አይገባንም ። እኔን ጠብቀኝ እያልን ለደከሙት ፣ ለሰነፉት መጸለይ ይገባናል ። ባልጸናው ዓለም ላይ ሰው የተለዋወጠ ኑሮ ይኖራል ። ባገኘው ዕድል ይከብራል ፣ ተራው ሲያበቃ ዝቅ ይላል ። ይህ የሚገርመን እንግዳ ሰዎች ሳንሆን ይህ በእኛም እንደሚደርስ የምናምን ሰዎች መሆን ይገባናል።

ቃል እንግባ ። በምንም ሁኔታ ውስጥ ቢሆን ያከበርኩትን ሰው አላቃልለውም ። እግዚአብሔር ሆይ እባክህ አግዘኝ ።

የብርሃን ጠብታ 15
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ጥቅምት 15 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም