መግቢያ » ከመጻሕፍት » ወዳጄ ሆይ » ወዳጄ ሆይ /18

የትምህርቱ ርዕስ | ወዳጄ ሆይ /18

ወዳጄ ሆይ
ፈገግታ የነፍስ ስጦታ ነው ። ፈገግታ በብርሃን ላይ የሚታይ ብርሃን ነው ። ፈገግታ ካማሩ ሳሎኖች ይልቅ እንግዳ ተቀባይ ነው ። ፈገግታ የእኔ ሀብት ሰው ነው ብሎ ማመን ነው ። ፈገግታ ለቀጣይ ግንኙነት በር መክፈቻ ነው ።ፈገግታ ወደ ሌላው ሰው የሚጋባ ደስታ ነው ። ፈገግታ ትልቁና የመጀመሪያው ግብዣ ነው ። ፈገግታ እንኳን ሰው እንስሳም የሚሰማው ቋንቋ ነው ። ፈገግታ ልብን ለደስታ የሚያነቃቃ ዜማ ነው ። ፈገግታ ብርሃን ለብሶ መታየት ነው ። ፈገግታ በትንሹ የፊት ሜዳ ላይ ቢገለጥም መላውን ዓለም የሚወርስ ነው ። ፈገግታ ያለ ችግር የመኖር ምልክት ሳይሆን ከችግር ፍቅር ይበልጣል የሚል መልእክት ነው ። ፈገግታ ለቆዳ ጤንነትና መነቃቃት ትልቅ ስፖርት ነው ። እባክህ ምንጊዜም ፈገግ በል ። ሁሉም ነገር ፈገግ ይልልሃል ።
ወዳጄ ሆይ
ያንተን ድርሻ በቅጡ ከተወጣህ ዓለም ድኗል ማለት ነው ። እንደ ሕፃን አጠገብ ያለውን እያየህ ሥራህን አትሥራ ። ያለችግር ካለህ መፍዘዝ ትጀምራለህ ፤ ተግዳሮትም መነቃቃትና እልኸኛ ያደርግሃል ። አዝነው ወዳንተ የመጡትን በንጹሕ ፍቅር ተቀበላቸው ፣ ሊነግሩህ የፈለጉትን ችግር ንቀውት ይተውታል ። መድኃኒት ላላቸውና ለሌላቸው በሽታዎች ትልቁ ፈውስ ፍቅር ነው ። ፍቅር ከተራራው በላይ ያራምዳል ። የአቅምህን ያህል ተራመድ እንጂ መንገድን ሁሉ እጨርሳለሁ ብለህ አታስብ ።
ወዳጄ ሆይ
በትንሽ ምክር የሚያረጋጋህ የእግዚአብሔር መንፈስ ዛሬም ካንተ ጋር ነው። ደፋር ኃጢአተኞች ፣ በፈሪ ኃጢአተኞች ፊት እንደ ጻድቃን ይንጎማለላሉ ። ያላየኸው ብዙ መልካም ነገር ከቦሃልና ጌታ ሆይ ዓይኔን ክፈት በለው ። የአልማዝ ጉድጓድ ላይ ተቀምጠው ስለተራቡ ሰዎች ብዙ ኀዘን ተሰምቷል ፤ ከዚያ ይልቅ በጸሎት የማይጠቀም ክርስቲያን ምስኪን ነው ።
ወዳጄ ሆይ
ብርሃን እንጂ ጨለማ ጥላ የለውም ፣ የሚከተልህን ጉድለት ያወቅኸውም በሌላ ሙላት ውስጥ ስላለህ ነህ ። ፍጹም ባዶ ሰው ፣ ፍጹምም ሙሉ ሰው የለም ።ከተሰበረ እጅ ይልቅ የማይሰጥ እጅ የተጎዳ ነው ። እጅ የተፈጠረው ለመቀበል ብቻ ሳይሆን ለመስጠትም ነው ። የማይሰጥ ድሀ የለም ፣ የማይቀበልም ባለጠጋ የለም ። በልብህ ውስጥ ያለውን በሙሉ ከተናገርህ ልብህ ልብ መሆኑ ቀረ ማለት ነው ። የተሰማህን ሳይሆን ያመንህበትን ኑር ። ዛሬ እየቻልህ ነገ አደርገዋለሁ የምትለውን ነገም አታደርገውም ፣ ምክንያቱም ነገ የዛሬ ውጤት ነውና ። ከሌላ የሚመጣውን ሳይሆን ካንተ የሚወጣውን ክፋት ተጠንቀቅ ።
ወዳጄ ሆይ
ሥሩ የበሰበሰ ዛፍን ከመውደቅ የሚያድነው የለም ። አስተሳሰቡ የተበከለም መጨረሻው አሳዛኝ ነው ። መለወጥ የሌለበት ጸጸት ጭቃ ላይ ተቀምጦ መታጠብ ነው ። ደስታን ስትከተል ይርቅሃል ፣ እግዚአብሔርን ስትከተል ደስታ አንተን ይከተልሃል ። ሰዎች ችግራቸውን የሚነግሩህ እንድትፈጽምላቸው ሳይሆን በአብዛኛው እንድታዳምጣቸው ነው ። በሕይወትህ ትልቅ ባለውለታዎችህ የገፉህ ሰዎች ናቸው ፣ ባትገፋ ኑሮ ይህ እውቀትና ኑሮ አይኖርህም ነበር ። መውደድህንና ምስጋናህን ቀጠሮ አትስጠው ፤ የምትወደውና የምታመሰግነው ሰው ያለው ቀን ዛሬ ብቻ ሊሆን ይችላልና ። ሥልጣን ካላዘዙበት የደነዘ ቢላዋ ነው ። ሥልጣን ካላዘዙበት ባለሥልጣኑን መቃብር የሚከትት ነው ። እሺ ካሉህ ይልቅ በጊዜው እንቢ ያሉህ ትልቅ ሰዎች ናቸው ። አንድ ካላልህ ሁለት አትልም ። ምቹ ጊዜ የምትጠብቅ ከሆነ ምንም አትሠራም ፣ ምቹ ጊዜ የመሥራት ውጤት ነውና ።
በደስታ ዋል !!!
ምክር 18
ዲአመ ሚያዝያ 15 ቀን 2011 ዓ.ም.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም