መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የደስታ ጠላት

የትምህርቱ ርዕስ | የደስታ ጠላት

“በተናደድህበት እያንዳንዷ ደቂቃ ስድሳ ሰከንድ የደስታ ጊዜ ታባክናለህ ።”

መናደድ መበሳጨት ፣ መንደድ ፣ መቃጠል ፣ ራስን መጉዳት ፣ ሰዎችን ማሳቀቅ ፣ ለበሽታና ለጭንቀት ሰውነትን አሳልፎ መስጠት ነው ። መናደድ ስላለፈው ፣ ስለ አሁኑና ስለሚመጣው ሊሆን ይችላል ። ስላለፈው የሚናደዱ ሰዎች በራሳቸው ስህተትና በሰዎች ክፋት ልባቸው የሚያዝንባቸው ሊሆኑ ይችላሉ ። እንዲህ ባይሆን ኖሮ እንዲህ አይሆንም ነበር የሚል ስሜት መናደድን ያስከትላል ። ይህ ስሜት ለአንድ ጊዜ ሊሰማን ይችላል ። እየመረዘን እንዲኖር ግን መፍቀድ አይገባንም ። የሆነን ነገር መለወጥ አይቻልም ። ከተማርንበት ግን የትላንቱ ለነገ ስንቅ ይሆነናል ። ያለፈው ጊዜ ላይ መማር እንጂ ማቀድ አይቻልም ። እንደ ሞኝም ምነው እግሬን በሰበረው ፣ ምነው አፌን ዱዳ ባደረገው ማለት የንስሐን ጥቅም አለመረዳት ነው ። ቆሻሻ ባይኖር ኖሮ ውኃ ለንጽሕና አያስፈልግም ነበር ። በራሳችን ስህተትና በሰዎች ግድፈት ላይ መዘግየት አይገባንም ። የተሰጠን ዕድሜ የተሰፈረ ነውና ሥራን በቁጭት ተክተን ማሳለፍ አያስፈልገንም ። የትላንት ጥሩ ጊዜ በትዝታነቱ ፣ ክፉ ገጠመኙ ደግሞ በትምህርትነቱ ይኖራል ። የሰው ልጅ የማይረሳ ትምህርት የሚያገኘው ከደስታው ይልቅ በጉዳቱ ነው ።

ሰዎች በዛሬው የሚናደዱት ምንም ተግዳሮት በመንገዳቸው ላይ እንዲቆም ባለመፈለጋቸው ነው ። ቀኑ የራሱ ክፋት ወይም ትግል አለው ። አንድ ቀን የምንለው ግማሽ ጨለማ ፣ ግማሽ ብርሃን ነው ። ሕይወትም በየቀኑ ደስታና ኀዘንን የምታስተናግድ ናት ። በየቀኑ ሊመጡ የሚችሉትን እንቅፋቶች ከግምት ውስጥ በማስገባት “የዛሬው ትግል ይህ ነው ማለት ነው” ብሎ መረጋጋት ይገባል ። የዛሬውን የምናልፈው የትላንቱን እንዳለፍነው ነው ። ችግር ጊዜያዊ ነው ። በመበሳጨት ግን ዘላቂ እናደርገዋለን ። በመንቀሳቀስ እንጂ በመናደድ የሚወገድ ተራራ የለም ። የመጣው የዛሬ ፈተና ይለወጣል ፣ ችግሩ ካልተለወጠ ደግሞ እኛን ይለውጠናል ። በእያንዳንዱ ገጠመኝ እውቀታችን እየጨመረ ይመጣል ። ለዕለቱ ተግዳሮትም በብስጭት አለመወሰን ፣ ለደስታውም በስሜት ቃል አለማግባት ይገባል ። ሲያድር ሁሉም ነገር ይለወጣል ። የደፈረሰውም ውኃ የሚጠራው በጊዜ ውስጥ ነው ። ሰከንድም ጊዜ ነውና እያንዳንዱ ደቂቃ ትዕግሥትን ይጠይቃል ። ሥራችንን በጸሎት መጀመር ፣ “እግዚአብሔር ሆይ ሁሉን ባንተ አግኝቻለሁ” ብሎ የምስጋና ልብ መያዝ ፣ ደኅና ብሎ በሞተው ነገር ላይ ሕይወትን ማወጅ ይገባል ።

ስለ ነገ መናደድ የሚከሰተው እውቀታችን ያድግና አሻግሮ ያያል ፣ የሚመጣውን ችግር በመገንዘብም ያስባል ፣ ያሳስባል ። ለማንቃትም ደወል ሲደውል አገርና ትውልድ ይተኛል ። በዚህ ጊዜ አዋቂው መናደድ ይጀምራል ። መክረን ምክራችን ተቀባይነት ሲያጣ መገንዘብ ያለብን ነገር አለ ። የሰው ልጅ ነጻ ፈቃድ ያለው ፍጡር ነውና ማስገደድ አንችልም ። ዳግመኛም ሁሉም ሰው የሚጓዘው የምርጫውን ውጤት ለመቀበል ነው ። የታየን ሁሉ ለሰዎች ላይታያቸው ይችላል ። ከማዘንና ከመናደድ “ያሳየኸኝን ግለጥላቸው” ብሎ መጸለይ ይገባል ። ማወቅ ያለ እግዚአብሔር እርዳታ ኀዘንን ይወልዳል ። አላዋቂው የገዛ ሞቱ ላይ ተኝቶ ያንኮራፋል ። አዋቂው ግን ያዝናል ። ኖኅ መርከብ የሠራው መዓት የመጣ ቀን አይደለም ። መዓቱ ከመምጣቱ ከብዙ ዓመታት በፊት ነው ። ቢተባበሩት ብዙ ሰዎች ከእርሱ ጋር ይድኑ ነበር ። እያፌዙበት ይሄዱ የነበሩት ሲጠፉ ኖኅ ግን ዳነ ። አዋቂና መንፈሳዊ ሰውም ይመክራል ፣ አልሰማ ካሉት እንደ ሎጥ ራሱን ያድናል ። ሎጥ ሚስቱንም ልጆቹንም አላተረፈም ። እውቀት በመማር እንጂ አብሮ በመኖር የሚጋባ ነገር አይደለም ። መንፈሳዊነትም ምርጫ እንጂ አብሮ የመኖር ውጤት አይደለም ። መጽሐፍ፡- “በዚያን ጊዜ ሁለት ሰዎች በእርሻ ይሆናሉ ፤ አንዱ ይወሰዳል አንዱም ይቀራል ፤ ሁለት ሴቶች በወፍጮ ይፈጫሉ ፤ አንዲቱ ትወሰዳለች አንዲቱም ትቀራለች” ይላል ። ማቴ. 24፡40-41።

እግዚአብሔር እያንዳንዱን ደቂቃ የደስታ ምክንያት አድርጎ ሰጥቶናል ። በእግዚአብሔር ሀልወት ፣ በተቀደሰው ጠባያቱ ፣ እኛን ባዳነበት ምሕረቱ ፣ በማያቋርጠው መግቦቱ ፣ በቀኑ በምሽቱ ፣ በማብላት በማጠጣቱ ፣ በልደት እያመጣ በሞት በመውሰድ ታሪክን በማስቀጠሉ ደስታችን ብዙ ነው ። መኖራችንን በማይፈልጉ ጠላቶች መካከል በሕይወት በመኖራችን ፣ ከሚያጠቁን አጋንንት የሚራዱን መላእክት ብዙ ስለሆኑ መደሰት ይገባናል ። ቆጥረን እንዳማረርን ቆጥረን ብናመሰግን ምሬት ይጠፋልን ነበር ፣ ያለን ከጎደለን የብዙ ብዙ ነውና ። ከትላንት የተሻለ ዛሬ ብለን የምንጠራው መክሊት በእጃችን አለ ፣ ከሄደው የመጣው መልካም ነገር ብዙ ነው ።

ቢሆንም ስንናደድ አእምሮአችንን እናጣለን ። ስሜታችንን እናዳምጣለን ። የዓመቱን በዕለት እናፈርሰዋለን ። ጤናችንን እናቃውሳለን ። አመላችንን እናስገምታለን ። አልምጦችን ደስ እናሰኛለን ። መንፈሰ እግዚአብሔር እንዲርቀን እናደርጋለን ። በጸሎት ሳይሆን በጉልበት ለመፍታት እንነሣለን ። ከሁሉ በላይ ኀዘን ፊታችንንና ልባችንን ያጨልመዋል ። ንዴት አቃጥሎ ይጨርሰናል ። ብስጭት በጎዳና በቤት እንደ ዕብድ እንድንታይ ያደርገናል ። ጭንቀት ወጥሮ ይይዘናል ። አጥፍቶ መጥፋት ያምረናል ። በተበሳጨንበት ሰዓት ቦታ እንለውጥ ፣ ውኃ አብዝተን እንጠጣ ፣ ሊያበርዱን የሚችሉ ሰዎችን እንፈልግ ፣ የዜማ መሣሪያ መጫወት የምንችል ከሆነ በገና መደርደር እንጀምር ። ንዴታችን ለመንፈሰ እግዚአብሔር ቦታ እየለቀቀ ይመጣል ። ጭስ የማይታይበት ቃጠሎ ንዴት ነው ። አዎ “በተናደድህበት እያንዳንዷ ደቂቃ ስድሳ ሰከንድ የደስታ ጊዜ ታባክናለህ ።”

በደስታ ዋሉ ።

የብርሃን ጠብታ 26

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ኅዳር 23 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም