የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ሁለቱንም አዳናቸው

“ነገር ግን ሰው እንደሚገባ ቢሰራበት ሕግ መልካም እንደ ሆነ እናውቃለን፤” 1ጢሞ. 1፡8
ሕገ ልቡና ፣ ሕገ ኦሪት ፣ ሕገ ሐዲስ በመባል ሕግ በሦስት ይከፈላል ። ሕገ ልቡና የተፈጥሮ ሕግ ፣ ሕገ ኦሪት የጽሑፍ ሕግ ፣ ሕገ ሐዲስ የመንፈስ ሕግ ነው ። ሕገ ልቡና ለሰው ዘር ሁሉ ፣ ሕገ ኦሪት ለእስራኤል ልጆች ፣ ሕገ ሐዲስ በክርስቶስ ለሚያምኑ ተሰጥተዋል ። ሕገ ልቡና በኅሊና ሰሌዳ ላይ ተጽፎ በተፈጥሮ አማካይነት ተሰጥቷል ። ሕገ ኦሪት በድንጋይ ጽላት ተጽፎ በደብረ ሲና ተሰጥቷል ። ሕገ ሐዲስ በቀራንዮ ተሰጥቷል ። አንዳንድ ሰዎች ኦሪቱንም ሐዲሱንም አልሰሙም እንዴት ይጠየቃሉ ? ብለን እናስብ ይሆናል ። በተሰጣቸው የኅሊና ሕግ ይጠየቃሉ ። የኅሊና ሕግ ሙሉ በመሆኑ የሕገ ኦሪትን ያህል ያስጠይቃል ። እግዚአብሔር ሕጉን የጻፈባቸውን ነገሮች ስንመለከት ቅድስና ምርጫ አለመሆኑን እንረዳለን ። ሕገ ልቡናን ያለ ቀለምና ያለ ሰሌዳ በኅሊና ላይ ጻፈ ። ይህን ሊያደርግ የሚችልም እርሱ ብቻ ነው ። ሕገ ልቡና የእግዚአብሔርን ሀልዎትና የሰውን ክብረት ያስረዳል ። ሰው ከደመ ነፍስ እንስሳት የሚለየው በውስጡ ባለው ረቂቅ ሕግና የዘላለም ሕይወት ነው ። አዳም የተኰነነው በሕገ ኦሪት አይደለም ። በሕገ ልቡናና በገነት ውስጥ በተሰጠው “አትብላ” በምትለው አንዲቷ ትእዛዝ ነው ። ሕገ ኦሪትም የተሰጠው በድንጋይ ጽላት ላይ ተጽፎ ነው ። በድንጋይ ላይ የሚጻፉ ጽሑፎች ለሺህ ዓመታት ይነበባሉ ። እግዚአብሔርም እንዳይረሳ የሚፈልገውን ትእዛዝ በድንጋይ ጽላት ላይ ጽፎ ሰጠ ። ሕገ ሐዲስንም በደሙ ቀለም ፣ በመንፈስ ቅዱስ አስታዋሽነት ለቤተ ክርስቲያን ሰጠ ። የሕገ ልቡና ተቀባይ ነፍስ ነበረች ። የሕገ ኦሪት ተቀባይ ቤተ እስራኤል ስትሆን የሕገ ሐዲስ ተቀባይ ግን ቤተ ክርስቲያን ናት ።

ሕጉ ለሰው ክብረት ሰጥቷል ። የሰው ልጅ ከጥፋት የሚመልሰውና መሳሳቱን የሚነግረው ሕግ ስላለው ከእንስሳት ይለያል ። ሰውን ሕግና እቅድ ከእንስሳት ልዩ ያደርጉታል ። እንስሳት የነገ ተስፋና እቅድ የላቸውምና ። ሕገ ልቡና የሰው ክብር ነው ። ኢማኑኤል ካንት የተባለ ሰው ሁለት ነገሮች ይደንቁኛል ብሏል ። የመጀመሪያው በኅሊና ላይ የተቀመጠው ሕግ ሲሆን ሁለተኛው በሰማይ ሰሌዳ ላይ የማያቸው ከዋክብት ናቸው ብሏል ። ሕገ ልቡና ፈላስፎች እንኳ የተደነቁበት ነው ። በዓለም ላይ ለሚገኙት ሕግጋት መሠረቱም ይህ የኅሊና ሕግ ነው ። ማንም ሰው ቢማርም ባይማርም ክፉ ፣ ክፉ ደግም ደግ መሆኑን ያውቃል ። ይህ እውቀት የመጣው በሕገ ልቡና ነው ። ሕገ ልቡና ትልቅ ስጦታ ነው ። በሕገ ልቡና ተመርተው እግዚአብሔርን የተከተሉ እነ ሄኖክ ፣ ኖኅና አብርሃምን ማስታወስ አለብን ። ታላላቅ አባቶች የነበሩት በሕገ ልቡና ነው ። ሕገ ልቡና በቂ ሕግ ስለሆነ ነው እግዚአብሔር በኖኅ ዘመን በጥፋት ውኃ ፣ በሎጥ ዘመን በእሳት የቀጣው ። ሕግ ባይኖር ኑሮ ሰብአ ትካትና ሰብአ ሰዶም ባልተቀጡ ነበር ። ሕገ ልቡና ለቅጣት በቂ ሕግ ነው ።
የእስራኤል ሕዝብ በዙሪያቸው ከነበሩት አሕዛብ ቢያንስ በሁለት ነገር ልዩ ናቸው ። በግዝረትና በሕገ ኦሪት ። ግዝረት የቃል ኪዳን ማኅተም ሲሆን ሕጉ ደግሞ መሪ ነው ። ታላቁ እስክንድርን ሳይቀር ያስደነቀው የሞራል ሕጋቸው ፣ የአምልኮ ሥርዓታቸው ፣ ሁሉም ነገራቸው መጽሐፋዊ መሆኑ ነው ። እስራኤል ጥንታዊ ሥልጣኔና ሕገ መንግሥት ያላት አገር የሚያሰኛት ሕጉ ነው ። ሕጉ ለእስራኤል ክብር ነው ።
ሕገ ሐዲስም ፍቅር ሲሆን ይህም ሕግ የተሰጠን እግዚአብሔር ስለ ሰው ልጆች ቤዛ ሁኖ ነው ። በዓለም ላይ ለንጉሣቸው የሚሞቱ ሠራዊት አሉ ። ለሠራዊቱ የሞተው ግን መድኃኔ ዓለም ነው ። ሕገ ሐዲስ በፍቅር ተጀምሯልና በፍቅር ይፈጸማል ።
ሐዋርያው ጳውሎስ የሕግ አስተማሪዎች ለመሆን የሚፈልጉትን ወደ ወገኝነትና ወደ ፈራጅነት ለመሄድ የሚሹትን ኤፌሶናውያንን ሲመክር ሕጉን ከሕጋውያን በመለየት ነው ። ስስታም ባለጠጎች የሚሰጡ ይመስላሉ ፣ የተቀባቡ ሴቶችም ቆንጆ ይመስላሉ ፣ የሚፎክሩ ወንዶችም ጀግና ይመስላሉ ። ሕጋውያንም ሕግ አክባሪ ይመስላሉ ። እንደ ስስታሙ ቆይ እባክህ እያሉ ኪሳቸውን ይዳብሳሉ ። ነገር ግን ዕዳ አይከፍሉም ። እንደ ቆንጆዋ ሴት ቆንጆ ይመስላሉ ፣ ቤታቸው ሲገቡ ግን ጌጡን ያወልቃሉ ። እንደ ወንድ ጀግና ይመስላሉ ፣ ፈተና ሲመጣ ይሸሻሉ ። ሕጋውያን ሲገድሉ እንጂ ሲሞቱ አይታዩም ። ዘመነ ሰማዕታትም የሐዲስ ኪዳን ዘመን ነው ። ሕጋውያንን ከሕጉ መለየት በጣም ያስፈልጋል ።
ሕጋውያን ሕጉን የሚጠቀሙበት ሌላውን ለመግዛት ነው ። ፖሊስ የሚያከብር ሕጉን ግን የማያከብር ብዙ ሰው አለ ። ሕጋውያንም እነርሱ ከተከበሩ ለሕጉ መፍረስ ደንታ የላቸውም ። ክብራቸው ግን የሕጉ መከበር ነው ። ሕጉን የደፈረ ፖሊሱን ይደፍራል ። ትራፊክ ፖሊሱን የሚያከብር ሕጉን ግን የሚጥስ ሾፌር አለ ። ሕጋውያን የሚያመርቷቸውም አስመሳዮችን ነው ። ሕጉ ግን መልካም ነው ። ከመልካሙ እግዚአብሔር የተገኘ ነውና ።
ሕጉ መልካም ነው ። የሚመራን ወደ ቀና ጎዳና ነውና ። የግብረ ገብነት ደረጃ ብናወጣ፡-
1-  ጨዋ ፣
2-  በጎ አድራጊ ፣
3-  የእግዚአብሔር ልጅ ፣
4-  ክርስቶስን የሚመስል ብለን ማውጣት እንችላለን ።
ሕገ ልቡና ጨዋዎችን ፣ ሕገ ኦሪት በጎ አድራጊዎችን ፣ ሕገ ሐዲስ የእግዚአብሔር ልጆችን ያስገኛል ። የእግዚአብሔር ልጆችም እንደ ክርስቶስ በመኖር መልኩን ያሳያሉ ። “አባቱን የማይመስል ልጅ ዲቃላ ነውና ።” የሕግ አስተማሪ ሊሆኑ የሚወዱ ሕጉ በአብዛኛው “አታድርግ” የሚል ጨዋነት የሚሰብክ ነው ። ከዚያ የላቀ ዓለም ተገኝቷል ። አዲስ ፕላኔት ሲገኝ ወደዚያ የመርማሪዎች ቀልብ እንደሚሳብ ወደ አዲሱ ኪዳን እንዲሳቡ ይመክራል ። ክርስቲያን ማለት ልክ እንደ ክርስቶስ ወይም ክርስቶስ በምድር ማለት ነው ።የሕግ አስተማሪ ሊሆኑ የሚወዱ ከዚያ የተሻለውን የክርስቶስን ፍቅርና ርኅራኄ ለዓለም ሊያንጸባርቁ ይችላሉ ። ክፉን ባለማድረግ ሳይሆን በጎ በማድረግ ከዚያም በላይ ለወዳጅ ራስን አሳልፎ እስከ መስጠት የሚደርሰውን የፍቅርን ዓለም ማየት ይችላሉ ። ዓለም በመንደራችን ልክ አይደለችም ፣ ዓለም ሰፊ ናት ። እንዲሁም መንፈሳዊው ዓለም እጅግ ሰፊ ነው ። እነዚህ ኤፌሶናውያን መጀመሪያ ህልውናቸውን ለተቀበለው ሕገ ሐዲስ እውቅና መስጠት አለባቸው ። ለማያውቃቸው ሕግ አስተማሪዎች ሊሆኑ ከመከጀል ለክርስቶስ ክብር መስጠት ያሻቸዋል ። ሐዲሱ ያለው ኦሪቱም አለው ። ሐዲሱ የሌለው ኦሪቱም የለውምና ይኸው አይሁድ የገዛ መጽሐፋቸው ተጣልቷቸው ይኖራሉ ።
ሐዋርያው፡- “ነገር ግን ሰው እንደሚገባ ቢሠራበት ሕግ መልካም እንደ ሆነ እናውቃለን”ይላል 1ጢሞ. 1፡8 ። የሐዋርያው ቅሬታ ሰው ሕጉን መፈጸም አልቻለም የሚል ነው ። ሕጉ ደግሞ ተደልሎ የሚያሳልፍ አይደለም ፣ የሚጠብቀውን ይጠብቃል ። ሰው ግን ደካማ ሥጋ በመሸከሙ ሕጉን መጠበቅ አልቻለም ። በዚህ ምክንያት ሕጉና ሰው ዓይንና ናጫ ሁነው ሰነበቱ ። ክርስቶስ የሕግ ፍጻሜ ሁኖ በመምጣቱ ሁለቱንም አዳናቸው ። ለሰው ልጅ መንፈሱን በመስጠት ሕጉ እንዲፈጸም አደረገ ። በዚህም ሰው ከመሳቀቅ ፣ ሕጉም ካለመከበር ዳኑ ። ሮሜ. 8፡3-4 ። 
ክብር ምስጋና ለአምላካችን ይሁን !
1ጢሞቴዎስ /12/
ኅዳር 17 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ