መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ለቃና ዘገሊላው ተአምራትህ ሰላም እላለሁ !

የትምህርቱ ርዕስ | ለቃና ዘገሊላው ተአምራትህ ሰላም እላለሁ !

ያለ ክፍያ ተአምራት የምታደርግ ፣ የተአምራትህ ታዳሚዎች ችግረኞች እንጂ ጋዜጠኞች ያይደሉ ፣ ከተአምራቱ በኋላም ምስጋናን እንጂ ምንዳን የማትጠይቅ ክርስቶስ ሆይ ሰላም እልሃለሁ ! ሰው ሰውነትን በጠላበት ዓለም ሰው ሁነህ ፣ ለይሉኝታ ሳይሆን ለፍቅር ሰርግ ቤት ተገኝተህ ፣ አለቀ ሲባል “መጥነው አይደቁሱም ወይ ?” ሳትል ፣ በእናትህ በድንግል ማርያም ምልጃ ውኃን የወይን ጠጅ ያደረግህ ጌታ ሰላም እልሃለሁ ። ውኃውን ወይን ጠጅ ለማድረግ ያልለፋህ ፣ ተአምራት ለማድረግ ላቦት ማውጣት ያላስፈለገህ ፣ ታዳሚው ጸጥ ይበል ብለህ መናገር ያላሻህ ፣ አንተና ችግረኞቹ ብቻ በምትተዋወቁበት ምሥጢር ጉድለትን ለመሙላትህ ሰላም እላለሁ ። ያንተ ስጦታ ዜና የለውም ፤ ቸርነትህም ደብቀህ የምታጎርሰው ነው ።

ቅዱሳን ከመታዘብ መጸለይ ይወዳሉና እናትህ ለመነችህ ። አንተም ማልዱ ብለህ አዘሃልና ተለመንሃት ። ዙፋንህን ሳትለቅ በበረት ፣ ምስጋናህ ሳይጓደል በሰርግ ዘፈን መሐል ለመገኘትህ ሰላም እላለሁ !! በሰማይ ሳትታጣ በምድር የተገኘኸው ፣ ሁሉን ቻይነትህን ሥጋዌህ ያልሻረው ፣ ተዋሕዶህ እንደ ቃና ውኃ መለወጥ የሌለው ፤ ምድሩን እንዳልጠላ የምድር ነዋሪ ሆነህ ፣ ሰውነትን እንዳልመረር ሰው ሁነህ መጥተህ የረዳኸኝ ፣ ደስታው ቶሎ ኀዘን ሲሆንብኝ ከጉድ ያወጣኸኝ የቃና ዘገሊላ እድምተኛ ኢየሱስ ሆይ ሰላም እልሃለሁ !!

ያንተ ተአምራት የዕድገት ሕግ የለውም ። ማስተዋልህም ካምና ዘንድሮ አይባልም ። ሁሉን ከፍጹምነትህ ትሰነዝራለህና ሰላም እልሃለሁ !! አንተ የቆሮንቶስ ባሕታዊ ነህ ፣ ብሕትውናንም ትባርካለህ ። አንተ የቃናው እድምተኛ ነህ ፣ ማኅበራዊነትንም ትወድሳለህ ። ሁሉ ገንዘብህ ነው ፣ ሁሉ ግዛትህ ነውና የምትታጣበት ቦታ የለም ፤ ለከሀሊነትህ ሰላም እላለሁ ። እንዳይናገሩት ሐፍረት ዱዳ ፣ እንዳይኮሩ ባዶነት ዕራቁት ላደረጋቸው የአደባባይ ሸማ ሆንካቸው ። በአደባባይ የተራቆተውን ካንተ በቀር የሚያለብሰው ማንም የለምና ሰላም እልሃለሁ !! ሰርጉ ኀዘን ፣ ጅምሩ ፍጻሜ ፣ ማለዳው ሠርክ ለሆነባቸው አንተ ተስፋ ነህ ። ቶሎ የሚያልቀው ወዳጅነት ፣ ቶሎ የሚጠናቀቀው የዓለም ደስታ ልቡን ለሰበረው እባክህ አንተ ተዋሰው ። ነጻነት የሆነው ፍቅር ሸክም ፣ መልስ የሆነው ቸርነት ዕዳ ለሆነበት እባክህ አሳርፈው ። የተጠራው ትውልድ መጥቶ ሳያበቃ ዓለም ድግስዋ እየተጠናቀቀ ነውና ከመጨረሻው የምትጀምረው ሆይ ክንድህን አንሣ ። አሜን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ጥር 15 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም