“ኢየሱስም፦ እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም ። እኔንስ ብታውቁኝ አባቴን ደግሞ ባወቃችሁ ነበር። ከአሁንም ጀምራችሁ ታውቁታላችሁ አይታችሁትማል አለው።” ዮሐ. 14 ፡ 6-7 ።
የዮሐንስ ወንጌል የተጻፈበት ዓላማ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን አምነን እንድንድን ነው ። አይሁድ የሰው ልጅ መሆኑን አልካዱም ፣ ለሞት ያበቃው ግን “የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ” ይላል የሚለው ክስ ነው ። ሁሉም ሃይማኖቶች ክርስቶስ ደግ ሰው እንደሆነ ያምናሉ ። ሃይማኖት የለንም የሚሉ ሰዎችም በምድር ላይ የመልካም ሥነ ምግባር ተጽእኖ እንዳመጣ ይናገራሉ ። ነገር ግን ክርስትናን ልዩ የሚያደርገው ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እግዚአብሔር መሆኑን መቀበልና መመስከር ነው ። የዳነው ሰው በሆነው አምላክ ነው ። አምላክ በባሕርዩ አይሞትም ፣ በለበሰው ሥጋ ግን ለእኛ ቤዛ ሁኗል ። ቤዛነት አምላክነት ያሻዋል እንዲሉ ቤዛ የሆነው አምላክ ባይሆን ኖሮ ድኅነትን አናገኝም ነበር ፤ በፍጡር መዳን አይቻልምና ። በርግጥም ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ ነው ።
ማለዳውን ስነሣ ዘመን የሌለውን ባለ ዘመን ፣ ፍለጋ የሌለውን ባለጠጋ ፣ ምክንያት የሌለውን ነዋሪ እያሰብኩ ነበር ። ዘመን የተሰጠን ባለ ዘመን ፣ ዘመን የሚያልቅብን የጊዜ ተቀባዮች ነን ። ዘመናችን እንደ ቀኑ ነው ፣ ቀኑ ንጋትና ምሽት አለው ፤ የእኛም ዘመን ይነጋል ፣ ይመሻል ። ትላንት ንጉሥ የነበሩ ወርደው እስረኛ ሆነው ሊኖሩ ይችላሉ ። እግዚአብሔር ብቻ “ነበር” የሚል ኃላፊ ግስ አይስማማውም ። ህልውናው ከክብሩ ጋር ለዘላለም የሚኖር ነው ። ንጉሥ ፣ ንጉሥ ያልነበረበት ዘመን ነበር ፣ ንጉሥ የማይሆንበትም ጊዜ ይመጣል ። ወኪል ነውና የወከለው ውክልናውን ሲያነሣበት በቅጽበት ይታጣል ። የትላንት ጌታ ፣ የዛሬ ከርታታ ይሆናል ። በቅርቡ ሶሪያን ለ24 ዓመታት ያስተዳደሩት በሽር አል አሳድ ጠዋት ገዥ ከሰዓት ስደተኛ ፣ ጠዋት መላው ሶሪያ የእርሳቸው ፣ ከሰዓት በራሽያ በአንድ ቤት የሚወሰኑ ሆነዋል ። ቀጥሎ የእንቅስቃሴ ማዕቀብ ፣ ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት መጠራት ይገጥማቸዋል ። እግዚአብሔር ብቻ በግዛቱ ፀሐይ አይጠልቅም ። ፀሐያቸው የሚጠልቅ ነገሥታትን ከመተገን አንዱን አምላክ ማመን በእውነት የተሻለ ነው ። እግዚአብሔር በሰው ይሁንታ አልነገሠምና በሰው ዓመፅ አይሸነፍም ። አምላካችን ንጉሥ ያልነበረበት ዘመን የለም ፣ ወደፊትም አይኖርም ።
ባለጠግነቱ ፍለጋ የለውም ። ሲለምኑት ከየት ያመጣዋል ? ብለው አያዝኑለትም ። ሲሰጥም አያልቅበትም። አንድ ቢሊየነር አንድ ብር ቢሰጥ አይጎዳውም ፣ ግን አንድ ብር ጎድሎበታል ። እግዚአብሔር አምላካችን የዚህ ማለዳና ቀን ጌታ ሀብቱ ፍጹም ነውና አይጎድልበትም ። ሀብቱን ከየት አመጣው ? ተብሎ ፍለጋው አይጠናም ። ሐዋርያው በዚህ ቢደነቅ፡- “የእግዚአብሔር ባለ ጠግነትና ጥበብ እውቀቱም እንዴት ጥልቅ ነው ፤ ፍርዱ እንዴት የማይመረመር ነው ፥ ለመንገዱም ፍለጋ የለውም ።” አለ ። ሮሜ. 11 ፡ 33 ። የምድር ባለጠጎች በየዓመቱ የሀብታቸው መጠን ይዋዥቃል ፣ ተወዳድረው ከፍና ዝቅ ይላሉ ። እግዚአብሔር ግን ለሰውና ለመላእክት የህልውናቸው መሠረት ነውና ከማንም ጋር አይወዳደርም ። የማያበድሩት ባለጠጋ ነው ። ጸጋውን ሳይሰፍር የሚሰጥ ነው ። የሀብታት መዝገብ ነው ። ንብረቱንም ማንም አልቆጠረውም ። እንኳን የእኛ የሆነው እኛም የእርሱ ነን ። ብዙ ባለጠጎች የሀብታቸውን ምንጭ እንዳይጠየቁ ይሰጋሉ ። ስለዚህ ለነገሥታት ሎሌ ሆነው ፣ ጨለማውን ብርሃን እያሉ ይኖራሉ ። ሰውን ፈሪ የሚያደርግ ሁለት ነገር ነው ፤ እነርሱም አለማወቅና ገንዘብ ናቸው ። ሀብታቸውን በዘመድ ባዝማድ ስም የሚያደርጉ ፣ እንደገና ቢክዱኝስ ብለው የሚጨነቁ አሉ ። የሀብታቸው ምንጭ በደኅንነት ሠራተኞች ይጠናል ። በውጪው ዓለም የሰው ልጅ ነጻነት አለው ተብሎ ቢታሰብም በብዙ ሕጎች ተጠፍሮና ፈሪ ሆኖ የሚኖር ነው ። አንድ ትርፍ ገንዘብ በሂሳብ ቍጥሩ የገባ እንደሆነ የትመጡ ይጣራል ። በአንዳንድ አገር የቅርብ ዘመዶች ሳይቀር የሀብቱ ደባቂ ሊሆኑ ይችላሉ ተብለው ይበረበራሉ ። እግዚአብሔር ግን ለሀብቱ ፍለጋ የለውም ።
በእግዚአብሔር ተፈጥረን በእርሱ ሕያዋን ሆነን የምንኖር ነን ። ባሕር በወሰን እንደ ተያዘች እኛም የምንኖርበት ዘመንና ቦታ ተወስኗል ። እግዚአብሔር ለህልውናው በፍጥረቱ አይደገፍም ። በማንም ሞትም አይከሰስም ፣ ምክንያቱም መግደልና ማዳን ሥልጣኑ ነውና ። እግዚአብሔር ለህልውናው የተመረኮዘው ምንም ነገር የለም ። በራሱ ሕይወተ ባሕርይ ነዋሪ ነው ። እኛ ግን ከእርሱ የእስትንፋስ ምጽዋተኞች ነን ። እስትንፋስዋን ቢያቆማት በራሳችን ለመኖር የሰከንድ አቅም የለንም ። ታዲያ ይህ ሁሉ ትዕቢት ምን ይሆን ? አዎ ማለዳውን ዘመን የሌለውን ባለ ዘመን እያሰብኩ ፣ እያንጎራጎርኩ ነበር ።
ለማትታጣው ጌታ ምስጋናና ክብር ይሁን !
ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 18 ቀን 2017 ዓ.ም.