የትምህርቱ ርዕስ | ለፍቅር እንኑር

“ፍቅር በማንኛውም ሰው ልብ ውስጥ በተፈጥሮ አለ ። በተቃራኒው ጥላቻ በትምህርት እንጂ በተፈጥሮ አይገኝም ።” /ኔልሰን ማንዴላ/

እግዚአብሔር በፍቅር ፈጠረን ። ከፍቅር ፈጠረን ። ለፍቅር ፈጠረን ። እግዚአብሔር እኛን ለመፍጠር ሲያስብ ይህን አገኛለሁ ብሎ አላሰላም ። እርሱ ብቻው ለዘላለም የኖረ ፣ በፍጥረቱ የማይደገፍ ነው ። የመላእክት ውዳሴ ፣ የሰዎች ምስጋና ፣ የአእዋፋት ዝማሬ ሳይጀመር እርሱ በራሱ ምስጋና ነበረ ። እከብር አይል ክቡር ፣ አገኝ አይል ባለጠጋ ፣ አሸንፍ አይል ድል ነሺ ፣ አልፍ አይል አሳላፊ ነው ። ሰውን ለመፍጠር ሲያስብ መልኩን ቅድስናውን ፣ ምሳሌውን ገዥነቱን ሊያካፍለው ብሎ ነው ። ሰው በመልኩ ሰማይን ሲመስል ፣ በገዥነቱም ምድርን ያስተዳድራል ። መልኩ እስካለ ግዛቱ ይጸናል ። እግዚአብሔር ሰውን በፍቅር ምክንያት ብቻ ፈጠረው ። እግዚአብሔር ፍቅር ባሕርይው ነው ። እግዚአብሔር ዘላለማዊ አካል ብቻ ሳይሆን ከአካሉና ከባሕርይው ጋር የጸና ዘላለማዊ ፍቅር አለው ። ፍቅርን ከእግዚአብሔር ተቀብለናል ፣ እንደ ንጹሕ መስተዋትም የፍቅሩን ብርሃን ለዓለም እንድናስተላልፍ ተጠርተናል ። ይህ ጥሪም በተፈጥሮና በመዳን ነው ። በተፈጥሮ በመልኩ ፈጠረን ፣ ይህ ማለት መልኩ ፍቅር ነውና በፍቅር ፈጠረን ማለት ነው ። ፍቅር ዓለም ሁሉ በጥላቻ ቢያዝ እኔ ግን በመውደዴ እጸናለሁ ብሎ የሚያምን ነው ። ፍቅር እግዚአብሔርን እንጂ ሁኔታዎችን ፣ ብድራትን ፣ ዘመኑን አያይም ። ለማፍቀር ምክንያቱ ፍቅር ብቻ ነው ። ፍቅር ለጥገኝነት የሚቀርብ ደብዳቤ አይደለም ። ፍቅር ራሱ አምባ ነውና ። አፍቃሪ ማለት ፈሪ ፣ ከሌላው የሚከጅልና የሚለማመጥ ሳይሆን የተፈጠረበትን ዓላማ ለማሳካት ቆርጦ የወጣ ነው ። ፍቅር በፍቅር ብቻ ይቆማል ። ፍቅር መቆሚያ ታኮ ፣ መደገፊያ ክራንች ከፈለገ ፍቅር አይደለም ። ክብርን በመፈለግ ባለሥልጣንን ፣ ሀብትን በመፈለግ ባለጠጋን ፣ ግርማን ተፈሪነትን በመፈለግ ጀግናን ፣ መኖርን በመፈለግ ጊዜ የሰጠውን መውደድ ፍቅር አይደለም ።

የሰው ልጅ በተፈጠረበት በፍቅር መልክ እስከ ጸና ድረስ ሁሉም ነገር ይታዘዝለት ነበር ። በዚህ ፍቅር ላይ ሲያምጽና ፍቅርን ገሸሽ ሲል ግን የገዛ ፈቃዱም ዓመጸበት ፣ አራዊት በጠላትነት የሚፈልጉት ፣ ምድርም የምትነፍገው ሆነች ። መብሉ ጣር ያለበት ፣ ልጅንም የሚያገኘው ከምጥ በኋላ ሆነ ። ያለ ጣር የተገኘው በረከት ከሄደ በኋላ በጣር የሚገኝ ቢገኝም የማያጠግብ ሆነ ። አዳም ከመሬት እናቱ ያለ ድካም ፣ ሔዋን ከአዳም እናትዋ ያለ ሕመም ተወለዱ ። አቤል ግን በምጥ ተወለደ ። በነጻ የተሰጠው ነገር ክብር ካላገኘ በዋጋ የሚገኝ ይሆናል ። በዋጋ ቢገኝም የማያስደስት ይሆናል ። ያለ ፍቅር የምንኖርበት ዓመት አይደለም ሰከንድ መኖር የለበትም ። ያለ ፍቅር ሰዎችን መታገሥ ፣ በእምነት መቀራረብ ፣ ይቅርታ ማድረግ አይቻልም ። ፍቅር ሰማይን መውረሻ ብቻ ሳይሆን የምድር ኑሮን ማጣፈጫም ነው ። አክመን መስማት ሲያቅተን አጣመን እንሰማለን ። ፍቅርን ካልዘራን ጠብን እንዘራለን ። እያንዳንዱ ቀን የትላንትን ስናጭድበት ፣ የነገን እንዘራበታለን ። መልካሙን ካልዘራን ክፉውን እንዘራለን ። መልካሙ ነገር ሲዘራ ያደክማል ፣ ሲታጨድ ያስደስታል ፤ ክፉ ነገር ሲዘራ ቀላል ነው ፣ ሲታጨድ የሚያስለቅስ ነው ።

ከፍቅር ተገኝተናል ። እግዚአብሔር በፍቅር ፈጠረን ። ከወላጆቻችንም ከፍቅር ተገኝተናል ። እግዚአብሔር ወንድን የሚያህል ጠንካራ ፣ ሴትን የሚያህል ንቁ አዘጋጀና ልጅን ሰጣቸው ። የሴት ንቃት የወንድ ጥንካሬ ልጁን ልዝብ አድርገው ያሳድጉታል ። በፍቅር የተፈጠረና በፍቅር የተወለደ የሰው ልጅ ያለ ፍቅር መኖር አይችልም ። ያለ አየር ለመኖር የሚያቅድ ካለ ያለ ፍቅር ለመኖር የሚያስብ ሞኝ ሰው ነው ። የሰው ልጅ ለፍቅር ይኖራል ። በፍቅር ተፈጠረ ፣ ከፍቅር ተወለደ ፣ ለፍቅር ይኖራል ። ለፍቅር ሲኖር የእግዚአብሔርንና የሰውን ውለታ እየከፈለ ነው ። እግዚአብሔር በመልኩ በአምሳሉ ፣ በልጅነት ማዕረግ ፈጠረው ። ወላጆቹም በምጥ ወለዱት ። እርሱ ሲወለድም ጎረቤቶች እልል አሉ ። የደስታ ጥይት ተተኮሰ ። ሲያድግም ማሙሽ እያሉ ሰዎች ሳሙት ። ከረሜላ ገዙለት ። ሲኮላተፍ አደመጡት ፣ ሲሳሳት ወደዱት ። እያንዳንዳችን ለእግዚአብሔርና ለሰው ያለብንን ዕዳ የምንከፍለው በፍቅር በመኖር ብቻ ነው ።

ኔልሰን ማንዴላ፡- “ፍቅር በማንኛውም ሰው ልብ ውስጥ በተፈጥሮ አለ ። በተቃራኒው ጥላቻ በትምህርት እንጂ በተፈጥሮ አይገኝም” ያሉት ለዚህ ነው ። ፍቅርን ያለ ልምምድ ይቀበለዋል ። አዲስ ምግብ ለመመገብ የሚታገለው ሕጻን ፍቅርን ግን ያለ ጥናት ይቀበለዋል ። ገና ሲወለድ የእናቱ እቅፍ ውስጥ መግባት ፣ ጡት መለመን ይጀምራል ። ፍቅር በተፈጥሮው ውስጥ አለ ። ጥላቻን ግን በተፈጥሮ ሳይሆን በትምህርት ያዳበረው ነው ። በቂመኞች ፣ በበቀለኞች ፣ በዘረኞች እጅ ሲያድግ ጥላቻን እየተማረ ይመጣል ። ዓለም ለፍቅር ካላት በጀት ለጥላቻ ያላት በጀት ይበልጣል ። እንደውም ለፍቅር ምንም በጀት የላትም ። ለጥላቻ ግን የጦር ኃይሏን በማደራጀት ትባጅታለች ።

ፍቅር በተፈጥሮ በውስጣችን የተቀበረ ነገር ሲሆን ያስቀመጠውም እግዚአብሔር ነው ። ከተቀበረበት ቆፍረን ማውጣት አለብን ። ጥላቻ ግን ሰዎች ያሸከሙን ትብትብ ነው ። መምረጥ ያስፈልገናል ። እግዚአብሔር ከሰጠንና ሰዎች ካሸከሙን ነገር አንዱን መምረጥ ያሻናል ። የእግዚአብሔርን ስንመርጥ አፍቃሪ ፣ የሰዎችን ስንመርጥ የጥላቻ ሰው እንሆናለን ። ማንም ሰው ፍቅራችንን በመጠራጠር መቀበል ይቸገር ይሆናል ። ፍቅር ሰላም እንደሚሰጠው ግን ሁሉም ሰው ይመሰክራል ። ውድ ነገር ሁሉ በጥልቀት የተቀበረ ሲሆን ሲቆፈር ይወጣል ። ፍቅርም በጥልቀት ተቀብሯልና ልናወጣው ይገባል ። መስቀሉን ቀብረው በላዩ ላይ ጉድፍ ቆሻሻ ጥለውበት ተራራ አህሎ እንደ ነበር ፣ ያንንም የተቀበረውን መስቀል ንግሥት ዕሌኒ እንዳወጣችው እናውቃለን ። መስቀሉ ዛሬም ተቀብሯል ። መስቀል ፍቅር ነው ። መቀበር ብቻ ሳይሆን ብዙ ጉድፍ ቆሻሻ ተከምሮበታል ። ዛሬም ቆፍረን እናውጣው ።

ጥላቻ መራራ ዋጋ ያስከፍላል ። ፍቅር ግን ይክሳልና እንፋቀር ።

የብርሃን ጠብታ 17
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ጥቅምት 21 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም