የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ልበ ብርሃን

“ይህም የልባችሁ ዓይኖች ሲበሩ የመጥራቱ ተስፋ ምን እንዲሆን በቅዱሳንም ዘንድ ያለው የርስት ክብር ባለ ጠግነት ምን እንዲሆን ለምናምን ከሁሉ የሚበልጥ የኃይሉ ታላቅነት ምን እንዲሆን ታውቁ ዘንድ ነው፤” ኤፌ. 1፡18-19።

ሐዋርያው የጸለየው አንድ ነገር ነው ። ያ አንድ ነገር ደግሞ ሦስት ነገሮችን ያሳያል ። እርሱም የልባቸው ዓይኖች እንዲበሩ ነው ። ልብም ሁለት ዓይኖች አሉት ወይ ? ቢሉ ሁለት ዓይን ለሚዛን ይረዳል ። ልብ አንዱ ሲጨክን አንዱ የሚራራ ሁለት ዓይኖች አሉት ። ልብ አንዱ ሲያለቅስ አንዱ የሚያስለቅስ ሁለት ዓይኖች አሉት ። ልብ አንዱ ሲያፈቅር አንዱ የሚበቀል ሁለት ዓይኖች አሉት ። ልብ አንዱ ስህተት ሲፈልግ አንዱ ይቅርታ የሚያደርግ ሁለት ዓይኖች አሉት ። ልብ አንዱ ሲሰበር አንደኛው የሚጸና ሁለት ዓይኖች አሉት ። ሙሉ ለሙሉ መልካም ሰው ፣ ሙሉ ለሙሉ ክፉ ሰው የለም ። አንድ ሰው እንደገለጸው፡- በጣም ጥሩ የሚባለው ሰው በውስጡ ሰው ያላያቸው ጥቂት መርዛም እባቦችን ተሸክሞ ይሄዳል ። በጣም ክፉ የተባለው በውስጡ ሌላውን የሚያጠግቡ ጥቂት ፍሬዎች ይዞ ይኖራል ። ከብዙ መልካም ጥቂት ክፋትን ያዩ ሰዎች ፣ ሰው ክፉ ነው ይላሉ ። ከብዙ ክፉ ጥቂቱን መልካም ያዩ ደግሞ ሰው መልካም ነው ይላሉ ። ይህ የሚሆነው ግን የልብ ዓይኖች ሲበሩ ነው ። በዓለም ላይ ብዙ ጨለማዎች ቢኖሩም የልብ ጨለማ ግን አስፈሪ ነው ። ብርሃን ለማግኘት ግድብ ከመገደባችን በፊት ፣ የሰው ልብ እንዲበራ ክፋትን መገደብ አለብን ።

አንዳንድ ጊዜ በመኖሪያ ቤታችን የሳሎኑ መብራት ይጠፋና የጓዳው ይሠራል ። አንዳንድ ሰዎች የላይ ዓይናቸው ጠፍቶ የውስጡ ግን ይበራል ። ሌሎች ደግሞ የሳሎኑ መብራት አለ ፣ የአውቶብስ ቍጥር ከሩቅ ይመነጥራል ፣ ውስጣቸው ግን ክርስቶስን ላለማየት ታውሯል ። የላይ አለማየት ኃጢአት አይደለም ፣ የውስጥ አለማየት ግን ጠፍቶ ማጥፋትን የሚያመጣ ኃጢአት የሆነ ነው ። የላይ ብርሃን በተአምራት ሲመለስ ፣ የውስጥ ብርሃን ግን በትምህርት ይመለሳል ። የልብ ጨለማ ሲጸና ሰው አፈር ላፈር ብቻ ይጫወታል ። ከሩቁ የቅርቡን እያሰበ ፣ ከእውነቱ ለስሜቱ እየታመነ ታሪኩን ያበላሻል ። የልብ ጨለማ ያለባቸው ሰዎች ማሳነስና ማራከስ ትልቁ ተግባራቸው ነው ። ለአገር የሚበቃውን ለማኅበር በማድረግ ማሳነስ ፣ ሌሎች ሊሠሩት ያለውን በተንኮል በመጀመር ማራከስ ይፈጽማሉ ። ሁሉን በእኔና ለእኔ ሲሉ ብዙ ደጎችን ይቀጫሉ ። ሰው የሚፈልገውን እንደ አዝማሪ እያዜሙ በልባቸው ግን ያልካዳቸውን ይክዳሉ ።

በጣም ድንቅ ከሆኑ ዝማሬዎች አንዱ፡-
“ቃልህ ሲነገር ልስማ ፣ ጌታ ሆይ እባክህ ፤
ልቤን ክፈተው ፣ ልቤን ክፈተው ፤
የልድያን ልብ እንደ ከፈትኸው” የሚለው ነው ። ቃለ እግዚአብሔር ለመስማት ተመጥቶ ይህን መዘመር ትልቅ ጥበብ ነው ። መስማትን ማስተዋል ፣ መናገርን መተግበር ካልተከተለው ሁሉም ነገር ከንቱ ነውና ። በቅዳሴአችንም፡- “ሀበነ እግዚኦ አዕይንተ አእምሮ ወትረ ኪያከ ይርአያ ወአዕዛንነሂ ቃለ ዘባሕቲትከ ይስማዓ” እንላለን ።
ትርጉሙ:-
“አቤቱ የዕውቀት ዓይኖችን ስጠን ። ዘወትር አንተን ያዩ ዘንድ ፣ ጆሮቻችንም ያንተን ብቻ ቃል ይሰሙ ዘንድ ።” ማለት ነው ። (ቅዳሴ እግዚእ/ የጌታ ቅዳሴ) ።
የልብ ዓይኖች ሲበሩ ምን ይከሰታል ?

1- የመጥራቱ ተስፋ ታላቅነት ፤
2- በቅዱሳን ዘንድ ያለው የርስት ክብር ባለጠግነት ፤
3- የኃይሉን ታላቅነት መረዳት ይከሰታል ።

የተጠራነው በተስፋ ካርድ ነው ። የተስፋ መጥሪያ ካርድ ያለው እግዚአብሔር ብቻ ነው ። መጀመሪያ ባለጠጋውን እናገኛለን ፣ ከዚያ ጸጋውን እንቀበላለን ። እኔን አስቀድሙ ከዚያ ወዲያ የእኔ የሆነውን ትወርሳላችሁ ይለናል ። እግዚአብሔር ባለመጥፋት እንድናበራ ፣ ባለጸጋውን ይዘን ጸጋውን እንድንቀበል ጠርቶናል ። ከሰማዩ ቤተ መንግሥት ፣ ከንጉሡ አዳራሽ ፣ ከዘላለም ድንኳን የእራት ግብዣ ተጠርተናል ፤ እግዚአብሔር በአንድ ልጁ ሰርግ ላይ ታዳሚ ሳይሆን ሙሽሪት እንድንሆን ወስኗል ። ይህ ትዳርም ከሞትና ከምጽአት የሚጀምር ነውና ለዘላለም የሚጸና ነው ።

በቅዱሳን ዘንድ ያለው የርስት ክብር ባለጸግነት የሚደንቅ ነው ። ተቆጥሮ የማይፈጸም ነውና “ባለጠግነት” አለው ። የስርቆሽ አይደለምና “ክብር” በማለት ጠራው ። ብዙ ርስት የያዙ ሌቦች አሉ ። እግዚአብሔር ሰጥቷቸው ሳይሆን የድሆችን ቀምተው ባለጠጋ የተባሉ ብዙዎች ናቸው ። እነ ውርደት ልብሱ በሌላው ሞት ላይ መኖርን ያቅዳሉ ። ይህ ሁሉ ጥሏቸው የሚሄድ ሀብት ፣ ጥለውት የሚሄዱት ርስት ነው ። ያችን ሦስት ክንድ ከስንዝር የሆነችውን የመቃብር ስፍራም በምጽአት ጊዜም እንለቃታለንና በምድር ላይ ምንም ርስት የለንም ። የእግዚአብሔር ርስት ግን ክብርና ባለጠግነት ያለው ነው ።

ከሁሉ በላይ የኃይሉን ታላቅነት ማወቅ ነው ። ኃይለኞች ነን የሚሉትን ስናይ ተስፋ እንቆርጣለን ። የኃይሉን ታላቅነት ብናይ ግን ሁሉን እያሳለፈ ነዋሪ በሆነው ጌታ እንደገፋለን ። ትላንት ያስፈራን አልፏል ። ላያልፍ የመጣም ማንም የለም ። ኃይል የእግዚአብሔር ነው ብሎ ማረፍ በእውነት መታደል ነው ። ቀድሞ ለኤፌሶን ሰዎች ፣ ዛሬ ይህን መልእክት ለምናነበው ሐዋርያው የጸለየልን የልባችን ዓይኖች እንዲበሩ ነው ።

ሐዋርያው የኤፌሶን ሰዎች ጥሩ ባለሀብት ሁነው አሕዛብን እንዲያስቀኑ ፣ በሥልጣን ማማ ላይ ወጥተው “ኢየሱስ ልጆቹን ያከብራል” እንዲሉ ፣ መልካም ትዳር ይዘው “ንጉሥ ለወደደው እንዲህ ይደረግለታል” ብለው ለራሳቸው እንዲያዜሙ ፣ ብዙ ሺህ ሕዝብ እያጋፉ እግራቸውን እንዲያሳልሙ ፣ የተዋቡ ልጆችን ወልደው ያልወለዱትን “ርግማን አለባችሁ” እንዲሉ ፣ ያማረ ለብሰው የተራቆቱትን እንዲያሳቅቁ ፣ የተገፉበት ዳገት ላይ ሲደርሱ እነርሱም ተረኛ ገፊ እንዲሆኑ ፣ ማንነታቸውን በአደባባይ ሳያፍሩ እንዲገልጡ ፣ የቤተሰባቸውን ታሪክ እየተረኩ “ይህን ሁሉ ጥዬ ነው ፣ ክርስቲያን የሆንሁት” ብለው ምስክርነት እንዲሰጡ አልጸለየላቸውም ።

“አቤቱ የዕውቀት ዓይኖችን ስጠን ፣ ዘወትር አንተን ያዩ ዘንድ ።
ጆሮቻችንም ያንተን ብቻ ቃል ይሰሙ ዘንድ ።”

አሜን ጌታ ሆይ !

የኤፌሶን መልእክት ትርጓሜ /26

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 24 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ