መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ልባችሁ አይታወክ

የትምህርቱ ርዕስ | ልባችሁ አይታወክ

 “ልባችሁ አይታወክ ፤ በእግዚአብሔር እመኑ ፥ በእኔም ደግሞ እመኑ ።”
                                  /ዮሐ. 14፡1 ።/
እጃችን ሲንቀጠቀጥ የያዝነውን ዕቃ እንጥላለን ፣ እግራችን ሲንቀጠቀጥ መሬት መርገጥ ያቅተናል ፣ ዓይናችን ሲርገበገብ ማየት ይሳነናል ፣ አፋችን ሲንቀጠቀጥ መናገር ያቅተናል ። ልባችን ሲታወክም ማሰብ ያቅተናል ። መታወክ የያዝነውን በቁማችን እንድንለቅ ያደርገናል ። የሚወዱንን እንድንገፋ ፣ ዋጋ የከፈልንላቸውን ወዳጆቻችንን እንደ ቀላል እንድንተው ያደርገናል ። መታወክ ሁሉም ነገር ሥፍራውን የለቀቀ አስመስሎ ይስልብናል ፣ ስንታወክ መሬት የተናወጠ ፣ ሰማይ የተቆረሰ ፣ አድማስ የጠበበ ይመስለናል ። ታውከን መስማት የማንፈልገው ድምፅ ታውካችኋል የሚለውን ነው ። ሁሉም ነገር ባለበት ነው ፣ እኛ ግን በመታወክ ባለንበት እምነትና ድፍረት አይደለንምና ሁሉም ነገር ዞር ያለ ይመስለናል ። ልጆቻችን ጥሩ ናቸው ፣ ለምን ፍጹም አልሆኑም ብለን መቀጥቀጥ እንጀምራለን ። የትዳር ጓደኛችን ከሌላው የተሻለ ወይም የተሻለች ናት ። ነገር ግን ለምን ሣራን አልሆነችም እያልን መፍታትን እንፈልጋለን ፤ ለምን አብርሃምን አልሆነም እያልን ገላግለኝ የሚል ጸሎት እንጀምራለን ። መታወክ እኛ እየተጓዝን በመሆኑ ሁሉም ነገር እየሄደ አስመስሎ ያሳየናል ። እኛ ወደፊት ስንበርር የቆመው ነገር ወደ ኋላ እየበረረ ይመስለናል ። የቆመው ነገር እንዳለ ነው ፣ እኛ ስለምንጓዝ ግን የሄደ ይመስለናል ። ስለ ከዱኝ ከዳኋቸው ፣ ስለ ተናገሩኝ መለስኩላቸው የሚያሰኘን መታወክ ነው ። የከዳነውም የተናገርነውም ግን እኛ ነን ። ከመጠን በላይ የትክክለኛነት ስሜት ሲሰማን መታወክ ውስጥ ነን ማለት ነው ። ስንታወክ ንግግር ብቻ ሳይሆን ዝምታም ቃል አውጥቶ ሲናገረን ይሰማናል ። የልባችን ትርታ እንደሚፈለጥ ድንጋይ እንሰማዋለን ፣ ቀጭ ቀጭ የሚለው ሰዓትም ማንም ባይሰማውም እኛ እንደ ጥይት ድምፅ እንሰማዋለን ። ነቅቶ መዋል ነቅቶ ማደር እርሱ መታወክ ነው ። የብዙ ውጫዊ ጦርነቶች መንስኤው ይህ ውስጣዊ ጦርነት ነው ። መታወክ የሰዎችን መልካምነት እንዳናይ ፣ ያደረግንላቸውን እንጂ ያደረጉልንን እንዳናይ ግርዶሽ ይሆንብናል ። እኔ ፣ እኔ የሚል ንግግር መታወክ የሚወልደው ነው ። እግዚአብሔር ያደረገልንን እንዳንቆጥር ፣ በምናመሰግንበት ዘመን እንድናማርር የሚያደርግ በአጠቃላይ የአመል ድሀ የሚያደርገን መታወክ ነው ። ከገንዘብ ድህነት ስንላቀቅ የአመል ድሀ መሆናችን ያሳዝናል ። ሌላው ከሚቀጣን ራሳችንን የቀጣነው ይበዛል ። መታወክ ውስጣዊ ጅራፍ ነው ። የምንፈልገውን አናውቀውምና በመታወክ ውስጥ የምንፈልገውን አናገኘውም ። መታወክ ንግግራችንን ጎምዛዛ ያደርገዋል ፣ አሳብችንን መግለጥ ስለሚያዳግተን በቍጣ ማውራት እንጀምራለን ። ከግድግዳ ጋር ፣ ከእንስሳ ጋር እንደ በለዓም ማውራት እንጀምራለን ። የማይካድ ነገር ለእኛ ብቻ የሚሰማን አሉታዊ ድምፅ አለ ። ማንም አይወድህም ፣ ስለ ሙያህና አገልግሎትህ እንጂ ፈላጊ የለህም የሚል ድምፅ ከሰይጣን ይመጣል ። ለስላሳ ግን የሚያሻክር ድምፅ ነው ። በሰላም ቀን አስበን ስንናገር ፣ በመታወክ ቀን ተናግረን እናስባለን ።

የእኔ ነው ብለን የያዝነው ሲከዳን ፣ ሁሉንም ነገር ለመቆጣጠር ተነሥተን ሲያቅተን መታወክ ውስጥ እንገባለን ። ልጆቻችን አቅም ባጡ ዘመን እሺ ይሉንና አቅም ሲያገኙ እምቢ ሲሉን ዓለም ይጨልምብናል ። የእኔ ብቻ ብለን የያዝነው ነገር የሌሎችም መሆኑን ስናውቅ መታወክ ውስጥ እንገባለን ። የተጨበጡ ስጋቶች ሐኪም ቤት ያለው ወዳጃችን ፣ እስር ቤት ቀጠሮ እየጠበቀ ያለው አጋራችን የመታወክ ምክንያታችን ናቸው ። ያልተጨበጠው ስጋት ደግሞ ጤነኛ ወዳጆቻችንን በአሳብ እየገደልን ያን ቀን ምን እሆናለሁ ብለን ስናስብ መታወክ ውስጥ እንገባለን ። አገር ቢበጠበጥ ፣ ረሀብ ቢነሣ ፣ የዘር ፍጅት ቢጀምር የት እሄዳለሁ ? በማለት መታወክ እንጀምራለን ። የሰማናቸው የሐኪም ቤት ውጤቶች የምንገምታቸው የላብራቶሪ ውጤቶች እነዚህ ሁሉ ታውከን ሌላውንም እንድናውክ ያደርጉናል ።
የነገ ኑሮዬ እንዴት ነው ብለን ስናስብ ፣ ያለ ጡረታ ከመሥሪያ ቤታችን መውጣታችን ፣ የራሳችን ቤት አለመሥራታችን እነዚህ ነገሮች የሁከት ማዕበል ሁነው በነፍሳችን ላይ ማጓራት ይጀምራሉ ። እግዚአብሔር የነገረንን ነገር በጆሮአችን ፣ ሰይጣን የሚያንሾካሹክብንን ድምፅ በልባችን ስንሰማ መታወክ ዘመዳችን ይሆናል ። እንቅልፋችን እየታጎለ ከነገ እየተበደርን መኖር እንጀምራለን ። ብቻዬን ነኝ የሚለውን አስደሳች ዜማ ማንጎራጎርና ለራሳችን ማልቀስ ትልቁ የመታወክ ግብዓታችን ነው ። ለምን እንዳመንን ፣ ለምን ቤተ ክርስቲያን እንደምንሄድ አለማወቅ ፣ ብዙ የሃይማኖት ደጆችን መርገጥ ፣ አንዴ ኦርቶዶክስ ሌላ ጊዜ ሌላ ስንሆን ይህ በራሱ መታወክን ይወልዳል ። መታወክ ያንቀዠቅዣል ፣ የሃይማኖት ቅልውጥ ውስጥ ይወስዳል ፣ ሄደንም መርካት ሲያቅተን ሁሉም ጋ ሰው ሰው ሲሸተን እንደገና ያላመንበትን ነገር መኖር ፣ ካፈርኩ አይመልሰኝ በሚል እልህ መታወክ ውስጥ እንገባለን ። መታወክ እየጸና ሲመጣ ድብርት ውስጥ ይከተንና ለምንም የማንደነቅ ፣ ቦምብ ቢፈነዳ የማንደነግጥ ድንዙዝ ሰዎች ያደርገናል ።
ወዴት እንደሚሄድ የማያውቅ ሰው ፣ በነፍሱ አድራሻ ያጣ ወገን መታወኩ ቅጥ የለውም ። የራሱን መንገድ ማስመር የሰለቸው ፣ ሰዎችን ያሳመነበት ዲስኩሩ ራሱን ማሳመን ሲያቅተው መታወክ ይጀምራል ። በእርሱ ውሸት ሰዎች ተኝተው እርሱ ግን ነቅቶ ያድራል ። መንገዱን አለማግኘት ብዙ ዋጋ ያስከፍላል ። መንገዱን ስናገኝ ገንዘብም ፣ ጉልበትም ፣ ጊዜም ፣ ፍርሃትም ይድናል ። እውነቱ የቱ ነው በማለት የሃይማኖት ውዝግብ ውስጥ የገባ ፣ መሐል መንገድ ላይ ቆሞ የዛሬን ለሁለት ሰንጥቀኝ የሚል በርግጥም መታወክ ውስጥ እየዋኘ ነው ። እግዚአብሔር ያላሸከመው ሸክም ረድኤተ መንፈስ ቅዱስ የለውምና ይህ ሰው ይጎብጣል ። ሕይወትና ኑሮ የተምታቱበት ፣ ኑሮን አስቀድሞ ሕይወትን መጎተት የሚፈልግ ፣ ፈረሱና ጋሪው ቦታ ተለዋውጠዋልና መታወኩ አይደንቅም ። መንታ መንገድ ያለ የሚመስለው ፣ ባሻው መንገድ እግዚአብሔርን ለማግኘት ተነሥቶ ከዘላለሙ አሳብ ጋር ይጣላልና ይታወካል ።
የመታወክ መድኃኒቱ ምንድነው ?
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፡- ““ልባችሁ አይታወክ ፤ በእግዚአብሔር እመኑ ፥ በእኔም ደግሞ እመኑ” አለ ። ጌታችን ልባችሁ አይታወክ ያለው የታወከ ሰው ልብሱ ሽቅርቅር ፣ ጨዋታው ደማቅ ፣ ችግር የለም የሚለው ድምፁ የማያቋርጥ ነው ። መታወኩን ሰው እንዳያውቅበት ቅባት ዘቅዝቆ የሚቀባ ፣ ልብስ አማርጦ የሚለብስ ነው ። ሰዎችም እያዩት እርሱማ ምን አለበት ? ይላሉ ። ከልብስና ከቤት ዘልቆ የሚያይ ጌታ ብቻ ነው ። ስለዚህ ልባችሁ አይታወክ አለ ። መርከብ ማዕበልን የምትሰጋው ወደቡ ላይ አይደለም ፣ በሰማይም ፈተና የለም ። መርከቧ ከማዕበሉ ለመዳን መልሕቋን መጣል ወይም ወደቡ ላይ መድረስ አለባት ። ከመታወክ የምንድነውም በመልሕቁ በእምነት ነው ። እኛን የሚሸከም መልሕቅ ቅድስት ሥላሴን ማመን ብቻ ነው ። አለማመን መታወክን ይወልዳል ። ስለዚህ በመታወካችን ያወክናቸውን ይቅርታ እንጠይቅ ። ኃጢአትም ሰላም ይነሣልና ያሳዘናቸውን በጉልበታችን ሂደን ማሩኝ እንበል ። ሰውን እያሳዘኑ እግዚአብሔርን ማስደሰት አይቻልም ። የታዘነበት ሰው ቢጸልይም ወደ ተዘጋ ሰማይ የሚጸልይ ነው ። መኖሪያችን የዘላለም አምላክ ነው ። እግዚአብሔር ገንዘብም ሥልጣኔም እንደማያኖር ለማሳወቅ ቆርጦ የወጣበት ዘመን ነው ። ሁሉንም ነገር እንድንቆጣጠር ሁነን አልተፈጠርንም ፣ አያስፈልገንምም ። ስለዚህ ነገሮች አመለጡኝ ከሚል ሁከት እንውጣ ። እምነት የራስን ስህተት ፣ የእግዚአብሔርን ተቀባይነት ማመን ነውና ፈጥነን ንስሐ እንግባ ። ባለቤቱ የልብ አውቃ ነውና “ልባችሁ አይታወክ” ይለናል ። እልፎች ከእኛ ጋር ከሚኖሩ እርሱ ከእኛ ጋር ካለ በቂ ነው ። የሰማዩ ፈርሶ የምድሩን ብናንጽ አሁንም እንደ ፈረሰ ነው ።
ጸሎት
ጌታዬ ሆይ በሞትና በሕይወት መካከል ነፍሴን ያፈናትን መታወክ በቃልህ ሥልጣን ዛሬ ድል ንሣልኝ ። በሁሉ ላይ የበላይ መሆኔ ሳይሆን ሁሉን ለማገልገል ዝቅ ማለቴ ሰላም እንደሚሰጠኝ እባክህ ንገረኝ ። አንተ እያለኸኝ ይህን ባጣ ከሚል ድንጋጤ መልሰኝ ። ነፍሴ በእጅህ ናትና መልሰህ ለእኔ አትስጠኝ ። የሰላም ምክንያት እንጂ ለሌሎች የሁከት ምክንያት ከመሆን ጠብቀኝ ። ምንም ነገር ጥያቄ እንዳይሆንብኝ የዘላለም መልሴ አንተ ከእኔ ጋር ሁን ። በተመሰገነው መንግሥትህ ለዘላለሙ አሜን ።
የመስቀሉ ገጽ 3
ሚያዝያ 9 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም