የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ልታነጻኝ ትችላለህ /2/

              
     /ማቴ. 82/
ኑሮው ላይጠቃ እኔን እያጠቃ መስሎ ተሰምቶኝ ነበር ትላንት ሙሉ ቀን ደክሜ ወደ ቤቴ ብገባም ዛሬ ደግም ሁሉም ነገር እንደ አዲስ ይጠብቀኛል ።ዓለ
በየቀኑ አዲስ ናት የጠበቅነው ሁሉ ቢሆን ሕይወት ይሰለች ነበር ።ከጠበቅነው የተለየ ነገር ስለሚገጥመን ግን ሕይወት እንግዳ ትሆናለች ብርሃን ሲሉት ጨለማ ደህና ሲሉት ክፉ ይሆናል እንደገና ጨለማ በብርሃን ይሸነፋል ክፉ በደግ ይተካል ሁልጊዜ ጨለማ ቢሆን ሕይወት ይቆም ነበር ሁልጊዜ ብርሃን ቢሆንም እግዚአብሔር ይረሳል እርሱ ግን ጠቢብ ነውና እያመጣጠነ ያኖረናል ታዲያ ከድካምና ከማይሞላው ኑሮ መቼ ነው የማርፈው ? እያልሁ እገሰግስ ነበር የሚሞላው በመንግሥተ ሰማያት ነው እያለ ሌላኛው ማንነቴ ያነጋግረኛል ምሬት ምሬት ይወልዳል መሰለኝ ካማረሩት እየባሰ ይሄዳል ወደ ቤቴ ገብቼ
ሥራውን
ትጥቅ ስፈታ ድንገት ሚስቴ ይህን አይተኸዋል ብላ ወደ ገዛ አካሌ ጠቆመችኝ በእኔ ላይ ያለውን እኔ ሳላየው እርሷ በማየቷ ገረመኝ ራሳችንን እንኳ ገና አናውቀውም መሽቶ እስኪነጋ ለመበላሸት የምንቸኩል ነን አለሁ ብሎ ለሰላምታ መልስ መስጠት ሐሰት ነው አለሁ በእግዚአብሔር ማለት የተሻለ ነው ሚስቴ ወዳሳየችኝ አካሌ ወደ ገዛ እጄ ስመለከት ለምጽ እየጀመረኝ ነው እንኳን በደጅ የማይሸፍኑኝ ባዕዳን አላዩኝ ብዬ ተጽናናሁ ከክፉ ነገርም ደግ ነገር አይታጣም

ይህ ለምጽ መሆኑን የሚያረጋግጠው ካህኑ ነውና እንደገና ከድካም ተነሥቼ ወደ ቤተ መቅደስ መገስገስ ጀመርሁ ለምጽ ካልሆነ ልቤ አርፎ እንዲተኛ ከሆነም ቁርጤን አውቄ በመገለል እንድኖር ወደ ካህኑ ገሰገስሁ ብዙ ነገሮች በውስጤ ይተራመሳሉ የቤተሰብ ፍቅር እንደ እሾህ ወጋ ያደርገኛል ከሰው ጋር ሆኜ እንኳ ብቸኝነቱን አልቻልኩትም ምን ልሆን ነው ? ብዬ መተከዝ ጀመርሁ ካህኑ አዛርያ አንድ ጊዜ ሲያስተምሩ፡– “ብቸኝነት ከሰው ሳይሆን ከእግዚአብሔር መራቅ ነውያሉት ትዝ አለኝ እግሮቼ እየተራመዱ ቢሆንም ብርክ ስለያዘኝ መንገዱ ራቀኝ እንዳልሰማ የምፈልገውን ነገር መስማት የዓለም መገለጫ ነው ብዬ አሰብሁ ልጄ በታመመ ጊዜ ሞቱን እንዳልሰማ አልኩኝ ግን ሰማሁ ፍላጎት እውነትን አያስቀርም ወዳጄን ሳልረዳው እንዳይሞት አልኩኝ እጅ አጥሮኝ እርሱም ሞተ ዛሬ እንዳልሰማ የምፈልገውን ላለመስማት ምን ዋስትና አለኝ ? ማሩ ካልተገኘ እሬቱን እያጣጣሙ መኖር ግድ ነው
ካህኑ የተረበሸ ስሜቴን ያነበበ መሰለኝ እርሱስ ለስንቱ አዝኖ ይዘልቀዋልየደነዘዘ መሰለኝ ሐኪሙን አክሙት ሰሚውን ስሙት አማካሪውን አማክሩት መሪውን ምሩት እያልኩኝ ልጮህ ትንሽ ቀረኝ ካህን በሰው ችግር ሲወጠር የሚውል ነው ያውም መለስ ብለው በማይወዱትና በማያመሰግኑት ሕዝብ መሐል የሚኖር ነው እንደውም በኢየሩሳሌምማ ካህን የሰርግና የልቅሶ ቤት ማድመቂያ ሁኗል ለጌጥ እንጂ ለትምህርት መፈለግ ካቆመ ሰንብቷል ካህኑም ቀኑ እየመሸ ቢሆንም የእግዚአብሔር ቤት ሰዓቱ አለፈ ተብሎ የማይዘጋበት ነውና አስተናገደኝ ይህም መጽናናትን ሰጠኝ ካህኑ እጄ ላይ የወጣውን ለምጽ ዙሪያውን በጥቁር ቀለም አከበበና ከሰባት ቀን በኋላ ተመልሰህ ክበቡን ካለፈ ለምጽ ነው ካላለፈ ጊዜያዊ የቆዳ በሽታ ነው ብሎ ሸኘኝ ሰባቱ ቀን ግን የምጥና የጭንቀት ነበረ ሚስቴ ያለ ልክ እየወፈረች ነበር ሰባቱ ቀን ግን ያለ ልክ የከሳችበት ሆነ እኔም ውስጤ ሲፈራ መፍራቴን ግን በወንድነቴ መግደርደር ለመሸፈን ሞከርሁ ምን ቢቀጥሩ ቀን ይደርሳል በእግሩነውና ደረሰ ቁርጥ ያጠግባል አንድ መሆኑ ካልተቻለ መራቁ ነገር እስኪለወጥ የፈውስ ያህል ነው ብዬ አኩተመተምሁ
ካህኑም እጄን አየ ለምጹ ገደቡን ጥሶ ወጥቷል ከዚህ በኋላ መላውን ሰውነቴን ለመውረር ይቸኩላል ተላላፊ በመሆኑ ቤተሰቤን ሁሉ ይበክላል ።የእነርሱ መታመም እኔን ላያድን ሁሉም ታማሚ መሆን የለበትም ይህ ከራስ ወዳድነት መላቀቅ ነው ወደ ቤቴ ሳልመለስ የለበስኩትን ልብስ ብቻ ሀብት አድርጌ በካህኑ አዋጅ ተለየሁ ካህኑ በልዑል ቃል ተናገረ፡– “ከዚህ ቀን ጀምሮ እስኪፈወስ ድረስ ከቤተሰቡና ከማኅበረሰቡ የተለየ ይሁንአለ ልጆቼን እንኳ ሳልስም በዚያው ተለየሁ እኔም ሰው እንዳይነካኝና እንዳይረክስለምጻም ነኝ ለምጻም ነኝእያልሁኝ በራሴ ላይ አወጅሁ ከግርግር ወደ ፀጥታ ከከተማ ወደ ዱር ገባሁ ከለምጻም ጋር ካልሆነ ከሌላ ጋር መኖር የማልችል ነኝ እኔን ከሚመስሉ ጋር ለመኖር ብዙ ሞከርሁ በኤፍሬም ግዛት በዳን ሰፈር በንፍታሌም ርስት በይሁዳ ምድረ በዳ ተንከራተትሁ ለምጹ ግን አልተለወጠም ችግሩ ካልተለወጠ እኔ መለወጥ አለብኝ ብዬ አሰብሁ ከዚያን ቀን ጀምሮ ብስጭት አቆምሁ ደስታዬ በግማሽ ተመለሰ ሰው ራሱን መቀየር ትቶ መቅደስ ይቀይራል እኛ ስንለወጥ ሁሉም ነገር ይለወጣል ከእኔ ያልጀመረ ለውጥነውጥሁኖ ይቀጥላል
ወደ ጥብርያዶስ የመጣሁት በቅርብ ጊዜ ነው ከሰዎች ድብቅ እያልሁኝ በብፁዓን ተራራ ላይ እመላለሳለሁ አንድ ቀን ግን ብዙ ሕዝብን አስከትሎ አንድ መምህር ወደ ብፁዓን ተራራ ወጣ እኔም በተራራው ጀርባ ሸሸሁ ትምህርቱ ግን ያለሁበት ድረስ የልቤን በር ያንኳኳል እንደዚህ ቀን ልቤ ወደቡን ሲያገኝ ሸክም ሲቀለኝ አልተሰማኝም ሲሰሙት እንዲህ የሚጥመው ሲኖሩት እንዴት ይፈውስ ይሆን ? ብዬ ማሰብ ጀመርሁ ትምህርቱ መንግሥታዊ አዋጅ አንድ ንጉሥ የሚናገረው የመንግሥቱ ቋሚ መርሕ የሕዝብም እውነተኛ መገለጫ ነበር ከመደበኛ ተማሪዎች ባልደመርም ተሸሽጌ የምሰማ የጫካ ተማሪ ነኝ ያለበት ድረስ መሄድ አልችልምና መምህሩ ያልሁበት ድረስ መጣ ለፍለጋው መታከት የለበትም ያለሁበት ስፍራ የብቸኝነት ዓለም ማንነቴም ሰው የማይቀርበው የተገፋ ነው መምህሩ ግን አንድን ሰው ፍለጋ ብዙዎችን አስከትሎ መጣ አንድ ሰው ብዙ ሰው ነው ብዙ ሰውም አንድ ሰው ነው ዓለም የጠፋት ሐቅ ይህ ነው
ይቀጥላል
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ