/ማቴ. 8፡2/
ኑሮው ላይጠቃ እኔን እያጠቃ መስሎ ተሰምቶኝ ነበር ። ትላንት ሙሉ ቀን ደክሜ ወደ ቤቴ ብገባም ዛሬ ደግም ሁሉም ነገር እንደ አዲስ ይጠብቀኛል ።ዓለ
ም በየቀኑ አዲስ ናት ። የጠበቅነው ሁሉ ቢሆን ሕይወት ይሰለች ነበር ።ከጠበቅነው የተለየ ነገር ስለሚገጥመን ግን ሕይወት እንግዳ ትሆናለች ። ብርሃን ሲሉት ጨለማ ፣ ደህና ሲሉት ክፉ ይሆናል ። እንደገና ጨለማ በብርሃን ይሸነፋል ፣ ክፉ በደግ ይተካል ። ሁልጊዜ ጨለማ ቢሆን ሕይወት ይቆም ነበር ፤ ሁልጊዜ ብርሃን ቢሆንም እግዚአብሔር ይረሳል ። እርሱ ግን ጠቢብ ነውና እያመጣጠነ ያኖረናል ። ታዲያ ከድካምና ከማይሞላው ኑሮ መቼ ነው የማርፈው ? እያልሁ እገሰግስ ነበር ። የሚሞላው በመንግሥተ ሰማያት ነው እያለ ሌላኛው ማንነቴ ያነጋግረኛል ። ምሬት ፣ ምሬት ይወልዳል መሰለኝ ። ካማረሩት እየባሰ ይሄዳል ። ወደ ቤቴ ገብቼ የ
ሥራውን ትጥቅ ስፈታ ድንገት ሚስቴ ይህን አይተኸዋል ብላ ወደ ገዛ አካሌ ጠቆመችኝ ። በእኔ ላይ ያለውን እኔ ሳላየው እርሷ በማየቷ ገረመኝ ። ራሳችንን እንኳ ገና አናውቀውም ። መሽቶ እስኪነጋ ለመበላሸት የምንቸኩል ነን ። አለሁ ብሎ ለሰላምታ መልስ መስጠት ሐሰት ነው ። አለሁ በእግዚአብሔር ማለት የተሻለ ነው ። ሚስቴ ወዳሳየችኝ አካሌ ፣ ወደ ገዛ እጄ ስመለከት ለምጽ እየጀመረኝ ነው ። እንኳን በደጅ ፣ የማይሸፍኑኝ ባዕዳን አላዩኝ ብዬ ተጽናናሁ ። ከክፉ ነገርም ደግ ነገር አይታጣም ።
ም በየቀኑ አዲስ ናት ። የጠበቅነው ሁሉ ቢሆን ሕይወት ይሰለች ነበር ።ከጠበቅነው የተለየ ነገር ስለሚገጥመን ግን ሕይወት እንግዳ ትሆናለች ። ብርሃን ሲሉት ጨለማ ፣ ደህና ሲሉት ክፉ ይሆናል ። እንደገና ጨለማ በብርሃን ይሸነፋል ፣ ክፉ በደግ ይተካል ። ሁልጊዜ ጨለማ ቢሆን ሕይወት ይቆም ነበር ፤ ሁልጊዜ ብርሃን ቢሆንም እግዚአብሔር ይረሳል ። እርሱ ግን ጠቢብ ነውና እያመጣጠነ ያኖረናል ። ታዲያ ከድካምና ከማይሞላው ኑሮ መቼ ነው የማርፈው ? እያልሁ እገሰግስ ነበር ። የሚሞላው በመንግሥተ ሰማያት ነው እያለ ሌላኛው ማንነቴ ያነጋግረኛል ። ምሬት ፣ ምሬት ይወልዳል መሰለኝ ። ካማረሩት እየባሰ ይሄዳል ። ወደ ቤቴ ገብቼ የ
ሥራውን ትጥቅ ስፈታ ድንገት ሚስቴ ይህን አይተኸዋል ብላ ወደ ገዛ አካሌ ጠቆመችኝ ። በእኔ ላይ ያለውን እኔ ሳላየው እርሷ በማየቷ ገረመኝ ። ራሳችንን እንኳ ገና አናውቀውም ። መሽቶ እስኪነጋ ለመበላሸት የምንቸኩል ነን ። አለሁ ብሎ ለሰላምታ መልስ መስጠት ሐሰት ነው ። አለሁ በእግዚአብሔር ማለት የተሻለ ነው ። ሚስቴ ወዳሳየችኝ አካሌ ፣ ወደ ገዛ እጄ ስመለከት ለምጽ እየጀመረኝ ነው ። እንኳን በደጅ ፣ የማይሸፍኑኝ ባዕዳን አላዩኝ ብዬ ተጽናናሁ ። ከክፉ ነገርም ደግ ነገር አይታጣም ።
ይህ ለምጽ መሆኑን የሚያረጋግጠው ካህኑ ነውና እንደገና ከድካም ተነሥቼ ወደ ቤተ መቅደስ መገስገስ ጀመርሁ ። ለምጽ ካልሆነ ልቤ አርፎ እንዲተኛ ፣ ከሆነም ቁርጤን አውቄ በመገለል እንድኖር ወደ ካህኑ ገሰገስሁ ። ብዙ ነገሮች በውስጤ ይተራመሳሉ ። የቤተሰብ ፍቅር እንደ እሾህ ወጋ ያደርገኛል ። ከሰው ጋር ሆኜ እንኳ ብቸኝነቱን አልቻልኩትም ፣ ምን ልሆን ነው ? ብዬ መተከዝ ጀመርሁ ። ካህኑ አዛርያ አንድ ጊዜ ሲያስተምሩ፡– “ብቸኝነት ከሰው ሳይሆን ከእግዚአብሔር መራቅ ነው” ያሉት ትዝ አለኝ ። እግሮቼ እየተራመዱ ቢሆንም ብርክ ስለያዘኝ መንገዱ ራቀኝ ። እንዳልሰማ የምፈልገውን ነገር መስማት የዓለም መገለጫ ነው ብዬ አሰብሁ ። ልጄ በታመመ ጊዜ ሞቱን እንዳልሰማ አልኩኝ ግን ሰማሁ ። ፍላጎት እውነትን አያስቀርም ። ወዳጄን ሳልረዳው እንዳይሞት አልኩኝ ፣ እጅ አጥሮኝ እርሱም ሞተ ። ዛሬ እንዳልሰማ የምፈልገውን ላለመስማት ምን ዋስትና አለኝ ? ማሩ ካልተገኘ እሬቱን እያጣጣሙ መኖር ግድ ነው ።
ካህኑ የተረበሸ ስሜቴን ያነበበ መሰለኝ ። እርሱስ ለስንቱ አዝኖ ይዘልቀዋል? የደነዘዘ መሰለኝ ። ሐኪሙን አክሙት ፣ ሰሚውን ስሙት ፣ አማካሪውን አማክሩት ፣ መሪውን ምሩት እያልኩኝ ልጮህ ትንሽ ቀረኝ ። ካህን በሰው ችግር ሲወጠር የሚውል ነው ። ያውም መለስ ብለው በማይወዱትና በማያመሰግኑት ሕዝብ መሐል የሚኖር ነው ። እንደውም በኢየሩሳሌምማ ካህን የሰርግና የልቅሶ ቤት ማድመቂያ ሁኗል ። ለጌጥ እንጂ ለትምህርት መፈለግ ካቆመ ሰንብቷል ። ካህኑም ቀኑ እየመሸ ቢሆንም የእግዚአብሔር ቤት ሰዓቱ አለፈ ተብሎ የማይዘጋበት ነውና አስተናገደኝ ። ይህም መጽናናትን ሰጠኝ ። ካህኑ እጄ ላይ የወጣውን ለምጽ ዙሪያውን በጥቁር ቀለም አከበበና ከሰባት ቀን በኋላ ተመልሰህ ና ፣ ክበቡን ካለፈ ለምጽ ነው ፣ ካላለፈ ጊዜያዊ የቆዳ በሽታ ነው ብሎ ሸኘኝ ። ሰባቱ ቀን ግን የምጥና የጭንቀት ነበረ ። ሚስቴ ያለ ልክ እየወፈረች ነበር ። ሰባቱ ቀን ግን ያለ ልክ የከሳችበት ሆነ ። እኔም ውስጤ ሲፈራ መፍራቴን ግን በወንድነቴ መግደርደር ለመሸፈን ሞከርሁ ። “ምን ቢቀጥሩ ፣ ቀን ይደርሳል በእግሩ” ነውና ደረሰ ። ቁርጥ ያጠግባል ። አንድ መሆኑ ካልተቻለ መራቁ ነገር እስኪለወጥ የፈውስ ያህል ነው ብዬ አኩተመተምሁ ።
ካህኑም እጄን አየ ፣ ለምጹ ገደቡን ጥሶ ወጥቷል ። ከዚህ በኋላ መላውን ሰውነቴን ለመውረር ይቸኩላል ። ተላላፊ በመሆኑ ቤተሰቤን ሁሉ ይበክላል ።የእነርሱ መታመም እኔን ላያድን ሁሉም ታማሚ መሆን የለበትም ። ይህ ከራስ ወዳድነት መላቀቅ ነው ። ወደ ቤቴ ሳልመለስ የለበስኩትን ልብስ ብቻ ሀብት አድርጌ በካህኑ አዋጅ ተለየሁ ። ካህኑ በልዑል ቃል ተናገረ፡– “ከዚህ ቀን ጀምሮ እስኪፈወስ ድረስ ከቤተሰቡና ከማኅበረሰቡ የተለየ ይሁን” አለ ። ልጆቼን እንኳ ሳልስም በዚያው ተለየሁ ። እኔም ሰው እንዳይነካኝና እንዳይረክስ “ለምጻም ነኝ ፣ ለምጻም ነኝ” እያልሁኝ በራሴ ላይ አወጅሁ ። ከግርግር ወደ ፀጥታ ፣ ከከተማ ወደ ዱር ገባሁ ። ከለምጻም ጋር ካልሆነ ከሌላ ጋር መኖር የማልችል ነኝ ። እኔን ከሚመስሉ ጋር ለመኖር ብዙ ሞከርሁ ። በኤፍሬም ግዛት ፣ በዳን ሰፈር ፣ በንፍታሌም ርስት ፣ በይሁዳ ምድረ በዳ ተንከራተትሁ ። ለምጹ ግን አልተለወጠም ። ችግሩ ካልተለወጠ እኔ መለወጥ አለብኝ ብዬ አሰብሁ ። ከዚያን ቀን ጀምሮ ብስጭት አቆምሁ ። ደስታዬ በግማሽ ተመለሰ ። ሰው ራሱን መቀየር ትቶ መቅደስ ይቀይራል ። እኛ ስንለወጥ ሁሉም ነገር ይለወጣል ። ከእኔ ያልጀመረ ለውጥ “ነውጥ” ሁኖ ይቀጥላል ።
ወደ ጥብርያዶስ የመጣሁት በቅርብ ጊዜ ነው ። ከሰዎች ድብቅ እያልሁኝ በብፁዓን ተራራ ላይ እመላለሳለሁ ። አንድ ቀን ግን ብዙ ሕዝብን አስከትሎ አንድ መምህር ወደ ብፁዓን ተራራ ወጣ ። እኔም በተራራው ጀርባ ሸሸሁ ። ትምህርቱ ግን ያለሁበት ድረስ የልቤን በር ያንኳኳል ። እንደዚህ ቀን ልቤ ወደቡን ሲያገኝ ፣ ሸክም ሲቀለኝ አልተሰማኝም ። ሲሰሙት እንዲህ የሚጥመው ሲኖሩት እንዴት ይፈውስ ይሆን ? ብዬ ማሰብ ጀመርሁ ። ትምህርቱ መንግሥታዊ አዋጅ ፣ አንድ ንጉሥ የሚናገረው የመንግሥቱ ቋሚ መርሕ ፣ የሕዝብም እውነተኛ መገለጫ ነበር ። ከመደበኛ ተማሪዎች ባልደመርም ተሸሽጌ የምሰማ የጫካ ተማሪ ነኝ ። ያለበት ድረስ መሄድ አልችልምና መምህሩ ያልሁበት ድረስ መጣ ። ለፍለጋው መታከት የለበትም ። ያለሁበት ስፍራ የብቸኝነት ዓለም ፣ ማንነቴም ሰው የማይቀርበው የተገፋ ነው ። መምህሩ ግን አንድን ሰው ፍለጋ ብዙዎችን አስከትሎ መጣ ። አንድ ሰው ብዙ ሰው ነው ፣ ብዙ ሰውም አንድ ሰው ነው ። ዓለም የጠፋት ሐቅ ይህ ነው ።
ይቀጥላል