መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » አዲስ ኪዳን » የማቴዎስ ወንጌል » ሕዝቡን የሚጠብቅ መስፍን

የትምህርቱ ርዕስ | ሕዝቡን የሚጠብቅ መስፍን

“እነርሱም፦ አንቺ ቤተ ልሔም ፥ የይሁዳ ምድር ፥ ከይሁዳ ገዢዎች ከቶ አታንሽም ፤ ሕዝቤን እስራኤልን የሚጠብቅ መስፍን ከአንቺ ይወጣልና ተብሎ በነቢይ እንዲህ ተጽፎአልና በይሁዳ ቤተ ልሔም ነው አሉት ።” ማቴ. 2፡5-6 ።
ይህንን ድንቅ ትንቢት የተናገረው ነቢዩ ሚክያስ ነው ። ይህ ትንቢት የተናገረው ከክርስቶስ ልደት 700 ዓመት ቀደም ብሎ ነው ። 700 ዓመታትን ወደፊት አሻግሮ በመንፈስ መነጽር የቤተ ልሔሙን ሕፃን ተመለከተ ። እጅ ነሣ ፣ ሰገደለት ። የክርስቶስ ልደት የአካል ብቻ ሳይሆን የተስፋ እድምተኞች ነበሩት ። ሚክያስ ሰባት መቶ ዓመት ወደፊት አሻግሮ ያየውን የክርስቶስን ልደት እኛም ሁለት ሺህ ዓመት ወደ ኋላ ተመልሰን ብናየው ለሚያነክሰው ሕይወታችን ብርታት የሚሰጥ ነው ። ትንቢት ከሰው የአእምሮ ብቃት ባሻገር በመንፈስ ቅዱስ የሚታይ የእግዚአብሔር እቅድ መግለጫ ነው ። እግዚአብሔር ከሰባት መቶ ዓመታት በኋላ ለሰው የሚያደርገውን ታላቅ ፍቅርና ትሕትና ለነቢዩ ገለጠ ። ነቢዩም ከሰባት መቶ ዓመታት በኋላ ስለሚደረገው የእግዚአብሔር የምሕረት ተግባር ተደሰተ ። እኛ ግን ነቢዩ የሚያምነውን አምላክ እያመንን ነገ አልታይ ብሎን እንጨነቃለን ። ይህን ትንቢት ከተናገረ በኋላ የባቢሎን ምርኮ አርባ ዓመት ሳይቆይ መጥቷል ። ለ500 ዓመታት ያህልም እስራኤል መሪ አጥታ ኑራለች ። በትንቢቱና በፍጻሜው መካከል ብዙ የመከራ ገደል ቢኖርም የእግዚአብሔር ሰው የፍጻሜውን እንጂ የመሐሉን አያይም ።
ይህ ትንቢት ለ700 ዓመታት የእስራኤል ልብ የጠገነ ፣ ጨለማውን የገፈፈ ፣ ተስፋንም ያበሰረ ነው ። ዛሬ ንጉሥ ባይኖረንም ትልቅ መስፍን ይነሣልናል ብለው ይጠብቁ ነበር ። የሚጠብቅ መኖር ይፈልጋል ። ነቢዩ ይህን ትንቢት የተናገረው ቤተ ልሔምን እያያት ነው ። ከተማይቱን እያዋራት ነው ። ጌታችን ከደብረ ዘይት ቁልቁል ወደ ኢየሩሳሌም ሲወርድ ኢየሩሳሌም እንዳናገራት ነቢዩም ቤተ ልሔምን አነጋገራት ። /ሉቃ. 19፡41-44/ ቤተ ልሔም እንኳን ድሮ ዛሬም ጎስቋላ ናት ። በእስራኤል ምድር ከሚታዩ ቦታዎች ቤተ ልሔም የተጎዳች ናት ። መልክአ ምድሯም ወጣ ገባ በመሆኑ ለእይታ የምትማርክ አይደለችም ። ይህችን ቤተ ልሔም ማነሷን የሚቀይር አንድ በረከት ይመጣል ። ማነሷም የሚወገደው መልክአ ምድሯ ተስተካክሎ ፣ ቤቶቿ እንደገና ተገንብተው አይደለም ። በዓይን የሚታየው ያው ነው ። የመንፈስ ልዕልናዋ ግን ከሁሉ የሚበልጥ ነው ። ይኸውም እግዚአብሔር የማዳን ጉዞውን በዚህች በቤተ ልሔም ጀመረ ። ሰው ክርስቶስን ሲያገኝ የሚታይ ኑሮው ባይለወጥም መንፈሳዊ ክብርና ሞገስ ግን ያገኛል ። ቤተ ልሔም የስሟ ትርጓሜ ቤተ ኅብስት ወይም የእንጀራ ቤት ማለት ነው ። ለዘመናት የስሟን ትርጓሜ አላገኘችም ። እነ ኑኃሚን ወደ ሞዓብ የተሰደዱት በቤተ ልሔም ራብ ተነሥቶ ነው ። /ሩት 1፡1/ አሁን ግን ዓለሙን ያጠገበው ኅብስተ ሕይወት ክርስቶስ በቤተ ልሔም ተወለደ ።
ቤተ ልሔም የተወዳጆች ከተማ ናት ። ራሔል የተቀበረችው በዚህች በኤፍራታ ቤተ ልሔም ነው ። ዘፍ. 35፡19 ። ዳዊት የተወለደው በቤተ ልሔም ነው ። የዳዊት ልጅ ክርስቶስም የተወለደው በቤተ ልሔም ነው ። ከትንሸዋ ከተማ ትልቅና ተወዳጅ ታሪክ ፈለቀ ። ትንንሾች ትልቅ አምላክ አላቸው ። ሁሉም ሰው ማነስን አይፈልግም ። ትልቁ ልዕልና ወይም ከፍታ ግን ክርስቶስ በነፍሳችን እንዲወለድ መፍቀድ ነው ።
ሕዝቤን እስራኤልን የሚጠብቅ መስፍን ካንቺ ይወጣል አላት ። ነገሥታት በጠፉበት ከ500 ዓመታት በላይ መሪ ባልነበረበት አገር ይህ መስፍን የሚጠበቅ ነው ። እግዚአብሔር ለጨለማ ዓመታት የሚልከው ቃሉን ነው ። ይህ መስፍን የሚጠብቅ ስለሆነ እረኛም ነው ። መሳፍንት ሁሉ ሰራዊት ይጠብቃቸዋል ። ይህ መስፍን ግን ሕዝቡን የሚጠብቅ ነው ።
ዛሬም ኑሮዬ ቁልቁለት ሆነ ፣ ከአብሮ አደጎቼ የምከጅል ሰው ሆንሁ እያልን የምንተክዝ ፣ በማነሳችን የምናዝን ካለን ክርስቶስ በክብር በውስጣችን እንዲወለድ እንለምን ፣ ያን ጊዜ የመንፈስ ልዕልናን እናገኛለን ። አገሬ ከሁሉ አገር አነሰች ፣ የውርደቷም ማቅ ተቀዶ አላልቅ አለ የምትሉ ክርስቶስ በሰላም በውስጥዋ እንዲወለድ ጸልዩ ። ቤተ ልሔም ያነሰች የይሁዳ አንድ ክፍል ብትሆንም ጌታ ሲወለድባት ግን እስራኤልን የሚጠብቅ ፣ ከጠላት ፍርሃት የሚያድን መስፍን ወጣባት ። እግዚአብሔር ሕይወታችንን ሲባርከው ከእኛ ለብዙዎች ፣ ከአገራችን ለዓለም የሚተርፍ ነገር ይወጣል ።
ወዳጄ ሆይ አንሰህ አትቀርም ። እግዚአብሔር ከፍ ያደርግሃል ። በንስሐ በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ቅረብ ። እህቴ ሆይ አንሰሽ አትቀሪም ካንቺ ለብዙዎች የሚሆን ብርሃን ይወጣል ። በንስሐ በጸሎት ጠብቂ ። አገሬ ሆይ አንሰሽ አትቀሪም ካንቺ ለዓለም የሚሆን መፍትሔ ይወጣል ። በንስሐ በጸሎት ወደ አምላክሽ ተመለሺ ።
የምትጠብቀን ገዥ ፣ የእስራኤል መስፍን ፣ የሕዝብህ እረኛ እባክህ ተነሣ  !!
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም