የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ሖረ ኢየሱስ – ኢየሱስ ሄደ

ጌታችን ሄደ ። የሄደው ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ነው ። የሄደው ወደ ዮሐንስ ነው (ማቴ. 3 ፡ 13) ። ገሊላ ልምላሜ የማይለያት ፣ ጠለ በረከት የሚያረሰርሳት ውብ አውራጃ ናት ። ጌታችን ከዚህች ለምለምና ነፋሻ ግዛት ወደ ዮርዳኖስ ሄደ ። ዮርዳኖስ ከላይ ከገሊላ ከአርሞን ተራራ ተነሥቶ በሙት ባሕር ጉዞውን የሚፈጽም ወንዝ ነው ። ጌታችን ጥብርያዶስ ካለው ጅረት አልተጠመቀም ። የምድር ዝቅተኛ ስፍራ በሆነው በአሞንና በእስራኤል ድንበር ላይ ባለው በዮርዳኖስ ጅረት ተጠመቀ ። እስራኤል በተሻገሩበት ፣ የተስፋውን ምድር በወረሱበት በዮርዳኖስ ተጠመቀ ። መናኙ ዮሐንስ በሚያጠምቅበት ፣ ዓለምን የናቁ ሰዎች በሚመጡበት በዮርዳኖስ ተጠመቀ ። አሞን ያልነው ዛሬ የጆርዳን ግዛት ነዋሪዎች ናቸው ። የዮርዳኖስ ወንዝ ሁለቱን አገሮች የሚለይ ተፈጥሮአዊ ድንበር ነው ። የዮርዳኖስን ወንዝ መሐሉን በገመድ ተካፍለው ይጠቀሙበታል ። ጌታችን የሚመሠርተው ጥምቀት ከሥጋዊ ልደት አውጥቶ መንፈሳዊ ልደት የሚሰጥ ነውና መንፈሳዊ ድንበር ነው ። የተጠመቀ ሰው አሮጌውን ቤተሰብ ትቶ አዲሱን ቤተሰብ ይቀላቀላል ። ይህም የማይጠፋ ዘር ተብሎ ተጠርቷል (1ጴጥ. 1 ፡ 23) ። በሚጠፋ ዘር ሲሟገት የሚውል ወደ ጥምቀት ጸጋው መመለስ አለበት ። የማይጠፋውን ዘር የተቀበለ ክርስቲያን ፣ በሚጠፋ ዘር ራሱን አያቧድንም ።

ጌታችን እስራኤል በተሻገሩበት ወንዝ ተጠመቀ (ኢያ. 3 ፡ 1) ። የግብጽ ኑሮ ማብቂያ ፣ የከነዓን ኑሮ መጀመሪያ ነበር ። አገር ያልነበራቸው ለመጀመሪያ ጊዜ ባለ አገር የሆኑት ዮርዳኖስን ሲሻገሩ ነው ። ጥምቀት መሻገር ነው ። መሻገር ለጨለማው ኑሮ ጀርባ እየሰጡ ፣ ለብርሃን ዓለም ፊትን መስጠት ነው ። መሻገር ኃጢአትንና ግፍን መተው ፣ ከወንድነት አማኝነትን ማዳበር ነው ። መሻገር የትላንቱ ትላንት አልፏል ብሎ ከአጉል ጸጸት መውጣት ፣ ይቅርታንም መለማመድ ነው ። ጥምቀትን ስናከብር ተሻግሬአለሁ ወይ ? ብለን መጠየቅ ያስፈልጋል ። ከሱስ ፣ ከዝሙት ተሻግሬአለሁ ወይ ? ብለን ራሳችንን መጠየቅ ያስፈልጋል ።

ጌታችን መናኙ ዮሐንስ በሚያጠምቅበት በዮርዳኖስ ወንዝ ፣ በጌልጌላ ሸለቆ ተገኘ ። ጌልጌላ ሸለፈት የተወገደባት ፣ አዲስ ትውልድ የተገዘረባት ስፍራ ናት (ኢያ. 5 ፡ 2) ። ግዝረት የጥምቀት ምሳሌ ነበር ። በግዝረት ውስጥ የአካል መቆረጥ ፣ የደም መፍሰስ አለ ። ግዝረት ትንሽ ሞት ነው ። ጥምቀትም ከክርስቶስ ሞት ጋር መተባበር ነው (ሮሜ. 6 ፡ 4) ። ውኃው ውስጥ ጠልቀን ስንወጣ ሞትን ለቅጽበት እናየዋለን ። ጌታችን ምሳሌው ጌልጌላ ማዶ እየታየው በዮርዳኖስ ተጠመቀ ፣ ጥምቀታችንን ባረከ ። ንጉሥ መንገዱን መርቆ ሲከፍት ከዚያ በኋላ አእላፋት ያልፉበታል ። በጥምቀት መንገድ ከሁለት ሺህ ዓመታት በኋላ እያለፍን ነው ። ዮሐንስ መናኔ ንብረት ነበር ። በበረሃ ንስሐን የሚሰብክ ነበር ። ጌታችን ወደ ዮሐንስ በመሄድ ምናኔን አከበረ ። መናኝም እንደሚወድድ ገለጠ ። የከተማው መናኝ ፣ የበረሃውን መናኝ ጎበኘ ።

ሖረ ኢየሱስ – ኢየሱስ ሄደ ። መሄድ ያስፈልጋል ። ንጉሥ አማጺ እስኪመጣ አልሄድም ይላል ። ባል ሚስቴ ይቅርታ እስክትጠይቀኝ አልሔድም ይላል ። ለበጎ ነገር ቀዳሚ መሆን ፣ በተሰማን ሰዓት መልካሙን ማድረግ ለዓለም ዕረፍት ያመጣል ። የጥምቀት ዝማሬ ትልቅ መልእክት አለው ። ወረደ ወልድ – ወልድ ከሰማያት ወረደ የሚል አንዱ ነው ። መውረድ ያስፈልጋል ። ከሰማያት ርቀት እርሱ ከወረደ ፣ ከሹመት ወንበር ወረድ ብሎ ሕዝብን ማየት ይገባል ። ሕዝብን ማየት የመጡበትን ስፍራ ፣ የትላንት ማንነታችንን ማየት ነው ። መሪ ከሕዝብ እንጂ ሕዝብ ከመሪ አይወጣምና ። ሁሉም ተፈራርቶ ከተቀመጠ ፣ ካልመጣ አልሄድም ካለ ተቆራርጠን መቅረታችን ነው ። ሰይጣን ከሁሉም በላይ አጀንዳው የሚፈጸምለት በሰዎች መለያየት ነው ። ጥምቀት አንድነት ነው ። አንድነትም በመሄድ የሚገኝ ነው ። ይህንን መሄድ ለመግለጥ ነው ታቦታት ከመንበረ ክብራቸው ወደ ባሕረ ጥምቀት የሚጓዙት ። ወልድ ከመንበሩ ወርዶ ወደ ዮርዳኖስ መሄዱን ለማሳየት ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ትተጋለች ። መልእክቱ እናንተም ሂዱ የሚል ነው።

የጥምቀት በዓልን ባየሁ ጊዜ ተዋሕዶ ሃይማኖታችንን ያጽናልን ፣ ወንጌልን በእጅ ለመዳሰስ ያበቃችንን ፣ የነገረ መለኮት ማማ የሆነችውን ቤተ ክርስቲያን ፣ ማንነቴ የተዋቀረባትን ቤተ ልሔም ይጠብቅልን ብዬ ሽቅብ ለመመረቅ ፈለግሁ !

አግዙኝ !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 13 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ