የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

መልካም ሥራ

 “ማንም ኤጲስ ቆጶስነትን ቢፈልግ መልካምን ሥራ ይመኛል የሚለው ቃል የታመነ ነው ።” 1ጢሞ. 3፡1
ጌታችን የእርሱ የሆኑትን ሲጠራ ስለሚጠብቃቸው ክብር ሳይሆን ስለሚገጥማቸው መከራ በመጀመሪያ ተናግሯል ። ክርስትና ራስን ካልካድን እግዚአብሔርን ማመን እንደማንችል ያስረግጥልናል ። ማመን በውስጡ ክህደት አለው ። እግዚአብሔርን ስናምን ራሳችንን ክደናል ማለት ነው ። ራሱንም የሚያምን እግዚአብሔርን ይክዳል ። የክርስትናው መርሕ ከዓለም ይለያል ። ዓለም ለማግኘት ማግኘት የሚል መርሕ አለው ፤ ክርስትና ግን ለማግኘት ማጣት ግዴታ ነው ። አምላካችን በነፍሳችን እንጂ በጊዜያችን ተወራርደን የምናመልከው አይደለም ። ስለ እርሱ የሚጎዳንን ኃጢአት ሳይሆን የሚጠቅመንን ነገር ካልተውን ገና አልወደድነውም ማለት ነው ። ወደ እርሱ የሚመጡ ራሳቸውን መካድና መስቀሉን ለመሸከም ትከሻውን ማስፋት ይኖርባቸዋል ። ራሱን ላልካደ ሰው መስቀል ከባድ ነው ። ራሱን ያልካደ ሰው የስሙ ነገር ያስጨንቀዋል ፣ መስቀል ደግሞ ስምን ማጣት ነው ። ራሱን ያልካደ ሰው ከሰው ማነስ ይጨንቀዋል ፣ መስቀል ደግሞ ውርደትን መታገሥ ነው ። ራሱን ያልካደ ሰው ለሰው መኖር ይከብደዋል ፣ መስቀል ደግሞ ስለ ሌሎች ራስን መስጠት ነው ። ራሱን ያልካደ ወገናዊነትን ማሸነፍ ይሳነዋል ፣ መስቀል ደግሞ ሁሉንም በእግዚአብሔር ዓይን ማየት ነው ። ራሱን ያልካደ ምን አገኛለሁ ? ይላል ፣ መስቀል ደግሞ ምን አጣለሁ ? ይላል ። ራሱን ያልካደ ሌሎችን ማገልገል ጥያቄ ይሆንበታል ፣ መስቀል ደግሞ ለሁሉ ሎሌ ሁን ይላል ።

የአገልግሎት ሕይወት ለሚቀልዱና አማራጭ ላጡ ሰዎች በጣም ቀላል ነው ።በእውነት ለሚያገለግሉ ግን ራስን መካድና መስቀሉን መሸከም የሚጠይቅ ነው ። ክርስቶስ መስቀልና ክብር ነው ። በቀራንዮ ካልገባን የጎልጎታን ክብር ማግኘት አንችልም ። ወራሽ የሚወርሰው ትርፍን ብቻ ሳይሆን ዕዳንም ነው ። ከክርስቶስ የምንወርሰውም ክብርን ብቻ ሳይሆን መከራንም ነው ። ስለ ድኅነት ያለውን ሙሉ ዋጋ ክርስቶስ ከፍሏል ፣ ስለ ወንጌል የሚከፈለው ዋጋ ግን ገና ይቀራል ። ወንጌል የማትታሰር ብትሆንም ልጆቿን ግን ለእስራት ታበቃለች ። ብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ “ወዳጄ ልቤ” በሚለው መጽሐፋቸው ስለ ወንጌል እንዳሉት፡-
ይዤሽ ወደ ሰማይ ፣
ይዤሽ ወደ ላይ ፣
አንቺ አጋዳይ ።
ሌላው ሰው ሙያቸው ተወድዶ በወንጌል ማመናቸው ተጠልቶ ወኅኒ በወረዱ ጊዜ፡-
“ለፍቼም አልቀረሁ እንደ አገልግሎቴ ፣
ግምጃ ሱሪ እግረ ሙቅ ፣ ወኅኒ ቤት ግዛቴ” ብለዋል ። እኚህ ሰው በሞቱ ጊዜም እህታቸው፡-
“ገዝግዘው ነዝንዘው ጣሉት እንደ ዝኆን ፣
ያው ወደቀላቸው ይበሉት እንደሆን ፤”
በማለት የኀዘን ቅኔ ተቀኝተዋል ።
በዚያ ዘመን ኤጲስ ቆጶስ ለመሆን የሚፈልግ ይሾም ነበር ። ቤተ ክርስቲያን ከክርስቶስ ዘመን ጀምሮ እስከ 313 ዓ.ም. ድረስ በታላቅ መከራ ውስጥ ነበረች ። መከራው ሲመጣ መጀመሪያ ሰማዕት የሚሆነው ኤጲስ ቆጶሱ ነበር ። ስለዚህ ብዙዎች ይህን መዓርግ ይሸሹ ነበረ ። በዚህ ምክንያት ሐዋርያው “ማንም ኤጲስ ቆጶስነትን ቢፈልግ” አለ ። የፈለገ ሁሉ ግን አይሾምም ነበረ ። ሐዋርያው መስፈርቱን ቀጥሎ ይዘረዝራል ። ቆስጠንጢኖስ የሃይማኖትን ነጻነት ካወጀ በኋላ ብዙም ሳይርቅ መናፍቃን በቤተ ክርስቲያን መፍላት ጀመሩ ። መናፍቅነት በተቦጨቀ ጥቅስ ቢመጣም ሁለት ነገሮችን መጠማትም ያመጣዋል ። የመጀመሪያው የክብር ጥማት ሲሆን ሁለተኛው የገንዘብ ጥማት ነው ። ከነጻነት ዘመን በኋላም ጵጵስና እንደ መኳንንት የሚፈርዱበት ፣ እንደ መሳፍንት ጌታ የሚሆኑበት የምድራዊ ሥልጣንና ገንዘብ መንገድ እየሆነ መጣ ። ብዙ ቡሩካን አባቶች ቢነሡም በተቃራኒው ወደ ኑፋቄና ወደ መሳፍንትነት ያደሉ ብዙዎች ነበሩ ። በመከራው ዘመን ያልነበሩ መናፍቃን በደንብ መፍላት የጀመሩት መከራው ሲያልፍ ነው ። መከራውን ሲሸሹ የነበሩ አሁን ነጻነት ሲመጣ ጳጳስ ለመሆን የሚፈልጉ ሆነ ። ጣልያን አምስቱን ዓመታት በኢትዮጵያውያን ላይ የመከራ እሳት ሲያዘንብ የሚበዛው ሸሽቶና ባንዳ ሁኖ ነበር ። ነጻነት ሲመለስ ሁሉም አለሁ ብሎ መጣ ። በዚህ ጊዜ ቀኝ ጌታ ዮፍታሔ ንጉሤ እንዲህ ብለው ገጠሙ፡-
የጌሾው ወቀጣ ማንም ሰው ሳይመጣ ፣
የመጠጡ ለታ ከየጎራው ወጣ ፤
ዛሬ ጵጵስና የሚፈልግ ቢባል የማይፈልግ የለም ። ያለው መከራ ሳይሆን ምቾት ነውና ። መስቀል ወዳጆቹ ትንሽ ናቸው ፣ ምቾት ግን የሚበዙ ወዳጆች አሉት ። የቤተ ክርስቲያንን ሹመት ለማግኘት ዛሬ ታላቅ ተጋድሎ አለ ። በኢትዮጵያ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን አንድ ሰው ለጵጵስና ታጩ ይባላል ። መታጨታቸውን አንድ ሰው ሲነግራቸው ጠጅ ማስጣል ጀመሩ ። ጉዳዩ ቫቲካን ሲሰማ “ሳይሾም ጠጅ ያስጣለ ቢሾም ምን ሊያደርግ ነው?” ተብሎ ሹመቱ ቀረ ። በእኛም ገና መሾማቸውን ሳያውቁት ቆብ ሲያሰፉ የኖሩ ብዙ ጊዜም የተበላሸባቸው አሉ ። ሹሙኝ ብሎ የሚሾም በቅን ሊፈርድ አይችልም ። እበቃለሁ ብሎ ማሰብም ትዕቢት ነው ። የእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን 59ኛው ሊቀ ጳጳሳት አባ መቃርስ መንኵሶ ወደ እናቱ ሲመጣ እናቱ በታላቅ እልልታ ተቀበለችው ። ጳጳስ ሁኖ ሲመጣ ግን በልቅሶ ተቀበለችው ። “ምነው እናቴ” ብሎ ቢጠይቃት፡- “እስከ ዛሬ ትጠየቅ የነበረው ስለ ራስህ ኃጢአት ነበር ፣ አሁን ግን የብዙዎች ዕዳ በእጅህ አለ” አለችው ይባላል ። ጵጵስና ተጠያቂነት ያለበት አደራም ክብርም ነው ። ሹሙኝ ብለው ጉቦ የሚሰጡ ፣ ለእጅ አውጪዎች የሚያጎርሱ እሳት እንደሚሸከሙ ቢያውቁ አያደርጉትም ነበር ። ሹመት ከእግዚአብሔር ተቆርጦ ከመጣ የምንቀበለው እንጂ ለምነን የምንገባበት ሊሆን አይገባም ።
ጳጳስ ወይም ኤጲስ ቆጶስ ተመሳሳይ ትርጉም ሲኖረው የቤተ ክርስቲያን ጠባቂ ማለት ነው ። ቄሱ አጥቢያ ሲያስተዳድር ጳጳሱ ደግሞ አውራጃን ያስተዳድራል ። ቤተ ክርስቲያን አዳጊ የሆኑ የክህነት መዓርጋት አሏት ። መዓርጋት መኖራቸው ብስለትና መሠረት እየያዙ ለማደግ በጣም ይጠቅማል ። ቤተ ክርስቲያንንም ለሁለት ሺህ ዓመታት ይዞ የቆየው ይህ በየዕድሜውና ብስለቱ የሚሰጠው መዓርግ ነው ። በቤተ ክርስቲያን ሰባት መዓርጋት አሉ፡-
1-  ሊቃነ ጳጳሳት
2-  ጳጳሳት
3-  ኤጲስ ቆጶሳት
4-  ቀሳውስት
5-  ዲያቆናት
6-  አናጉንስጢስ /አንባቢዎች/
7-  መዘምራን ይባላሉ ።
“ማንም ኤጲስ ቆጶስነትን ቢፈልግ መልካምን ሥራ ይመኛል የሚለው ቃል የታመነ ነው ።” /1ጢሞ. 3፡1 ።/ “የሚለው ቃል የታመነ ነው” ይላል ። ይህ ቃል በሌላ ስፍራ አልተጻፈም ። ልክ እንደዚህ ቃል፡- ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብፁዕ ነው እንዳለ የጌታን የኢየሱስን ቃል ልታስቡ ይገባችሁ ዘንድ በሁሉ አሳየኋችሁ” የሚለውም ቃል በወንጌል አልተገለጠም ። /የሐዋ. 20፡35 ።/ ይህ የሚያሳየን ያልተጻፈልን ብዙ የጌታ ትምህርት እንዳለ ነው ። ለመዳናችን የሚበቃው ግን ተጽፏል ። መልካምን ሥራ ይመኛል ይላል ። የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔርን ማገልገል ትልቅ ሥራ ነው ። ምናልባት አገልጋይ ነኝ ፣ ዲያቆን ነኝ ለማለት ካፈርን ትልቅ ሥራ መሆኑን መረዳት አለብን ። ነቢዩ ዮናስ በዚያች ጭንቅ ሰዓት ሥራህ ምንድነው ? ሲሉት ባሕርና የብሱን የፈጠረውን እግዚአብሔርን አመልካለሁ ነው ብሏል ። /ዮናስ 1፡9 ።/
ሳይገባን እናገለግልህ ዘንድ የመረጥከን ጌታ ስምህ ይቀደስ ።
1ጢሞቴዎስ 32
ጥር 4 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ