መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » መልክህ እንዳይሰወረኝ

የትምህርቱ ርዕስ | መልክህ እንዳይሰወረኝ

የታመመን አልጋ አንጥፈህለት የምትፈውስ ፣ የሞተን አልቅሰህለት የምታሥነሣ ፣ ያዘነን አጽናንተህ ማቁን የምትቀድ ፣ በጎዳና የወደቀውን አብረህ አድረህ ቤት የምትሰጥ ፣ የፈራውን አይዞህ ብለህ ማዕበሉን የምትገሥጽ ፣  መንገደኛውን አብረህ ተጉዘህ መድረሻው ላይ የምትቀበል ፣ ከታሰረው ጋር አብረህ ታስረህ ወደ ቤተ መንግሥት የምትወስድ ፤ ርኅራኄን አስቀድመህ ኃይልህን የምታስከትል አንተ ነህ ። አልጋ አንጣፊዬ ፣ አላቃሼ ፣ አጽናኜ ፣ የበረሃ ጓዴ ፣ ያስፈራኝን ያስፈራኸው ፣ የእስር ቤት ዘመዴ አንተ ነህ ። አልጋ ሳታነጥፍ እንኳን አልፈወስከኝ ። ሳታለቅስልኝ እንኳን አላሥነሣኸኝ ። አብረኸኝ ከምኩራብ ሳትወጣ እንኳን አልመለስከኝ ። ቀኑም ያንተ ነው ፤ ሌሊቱም ያንተ ነው እናመሰግንሃለን ።
ወደ ጥፋት የተሳበውን ተላላ የምትመክር ፣ ወደ ዓመፅ የሚያዘግመውን ሞኝ ቀጥተህ የምትመልስ ፣ ወደ ሞት የሚበረውን መንገድ ዘግተህ የምታቆም ፣ ወደ ሲዖል የሚፋጠነውን በሽታ ሰጥተህ የምታሳርፍ አንተ ነህ ። ዛሬ የታሰረው ወገን ሞት በእስር እንደ ተለወጠለት ምነው ባወቀ ! የታመመው ሲዖል በሕመም እንደተቀየረለት ምነው በገባው ! አንተ በምሕረቱ ብቻ ሳይሆን በመዓቱም ትምርበታለህ ። የእኔ የድሀው ወዳጅ ሌሊትን ቀን ማድረግ ልማድህ የሆነ በእኔ ትዕግሥት የዘገየህ ቢመስለኝም ባንተ ሰዓት ግን አላረፈድክም ። ባላይህም ታየኛለህ ። በስውር እጅህ ትመግበኛለህ ። ጽርሐ አርያም ሳስስህ ቤቴን ሞልተሃል ። በሩቅ ስፈልግህ በልቤ ተገኝተሃል ። ሁሉ በሁሉ ነህ ምስጋና ይገባሃል ።
የተራራቁትን የምታገናኝ ድልድይ ፣ ግንቡን አፍርሰህ ሰላምን የምትሰጥ መሰላል አንተ ነህ ። ሰማይና ምድር ተጣልተው አንዱን ለመሸምገል ሲሄዱ ከአንዱ ይርቃሉ ። ሰማይና ምድርን በአንዴ ያገናኘህ መሰላል የሥጋዌው ባለ ምሥጢር መድኃኔ ዓለም እናመሰግንሃለን ። እኔ አንዴ ሰጥቼ ሁለተኛ ለመስጠት እቸገራለሁ ። አንተ ግን ይህን ሁሉ ወፈ ሰማይ ሳትደክም ትመግበዋለህ ። እኔ አንድን ሰው ለመሸከም አቅም የለኝም ፤ አንተ ግን ሁሉን በትዕግሥትህ ታሳድረዋለህ ። የከደንከውን ማን ይከፍተዋል ? የከፈትከውንስ ማን ይዘጋዋል ?
ባለ ዝናው ፣ ስመ ጥር ጌታዬ በጉድለቴ ላይ ገናንነትህ ይገለጥ ። ያንተ የፍቅር ነጋሪት ሲሰማ ሥጋ ለባሽ ፀጥ ይበል ፣ የሞት ማስደንገጥም ይወገድ ፣ የበሽታ ጉልበትም ይሰበር ፣ የተደባለቀ የሰው ቋንቋ ይጥራ ። ተስፋ ቆርጦ የሚመለሰው ባለበት ይቁም ።
ጌታዬ ሆይ በማጣቴ ላመሰግንህ ገና ነኝ ፤ በማግኘቴ እንዳመሰግንህ እርዳኝ ። ጠላቴን ለመውደድ አልለምንህም ። ወዳጄን እንድወደው እርዳኝ ። በበረትም በዙፋንም አንተ ፣ አንተ ነህ ። ሰማይና ምድር የማይችሉህ በድንግል እናትህ ማኅፀን የተወሰንክም አንተ ነህ ። ነውሬን ልትከድን በመስቀል የተራቆትህ ፣ የተራቆትከውም የምታለብሰውም አንተ ነህ ። አንተ ራስህም የጽድቅ ሸማ ነህ ። ባለጠጋ ቢያለብስ ደግ ይባላል ። አንተ ግን ከደግ በላይ ልብስ ነህ ። እስክመጣ ምስጋናዬን ልላክልህ ። ይህን ትመስላለህ እያልሁ በቃላት ሥዕል መሳሌ እንዳያደክመኝ ፣ ከናፍቆት ብዛትም መልክ እንዳይሰወረኝ እባክህ ቶሎ ናልኝ ። ልመናዬን በብሩህ ገጽ ፣ በብርሃን ፊት ተቀበልልኝ ።
የነግህ ምስጋና /10
መጋቢት 2 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም