የትምህርቱ ርዕስ | መካሪ አታሳጣን

“ገላጋይ አጥቼ ግልገሌን በላኋት ።”

ሕይወትን ወደ ኋላ ዞር ብለን ስንመለከት ሁለተኛ ዕድል የሚሰጥ እግዚአብሔር ብቻ እንደሆነ እንገነዘባለን ። እርሱን የበደልነውን ያህል ሰዎችን ብንበድል ኖሮ ገሃነመ እሳትን ቢሰጡን እንኳ አይረኩም ነበር ። ብዙ ፍቅር ሰጥተናቸው ፣ ብዙ መልካም ነገር አብረናቸው አሳልፈን በአንድ ንግግር የሚለዩን ይኖራሉ ። ብዙ ዓመት ስቀንላቸው አንድ ቀን በራሳችን ጉዳይ ስናኮርፍ “የሰው ፊት እሳት ነው” ብለው ሊሸሹን ይችላሉ ። እግዚአብሔር ግን ያለማቋረጥ እያሳዘነው ያለማቋረጥ ይወደናል ። ችግራችንን ሳይሆን ችግራችን የመጣበትን ችግር እያየ ይራራልናል ። ሁልጊዜም ተስፋ ያደርገናል ። በእኛም ደስ ይለዋል ። ትእዛዙንም የሰጠን ስለሚተማመንብን ነውና ያከብረናል ። ዛሬን የመጨረሻ ግንኙነት በማለት አይጠራውም ፣ ስህተትን ዘላቂ ጠባያችን አድርጎ አይመለከተውም ። እርሱ የማያቋርጥ ዕድልን በመስጠት የታወቀ ነው ። ታዲያ በዚህ ጥቅጥቅ ባለው የሕይወት ደን ውስጥ የሚታወሱን ጸጸቶች አሉ ። ለምን እንዲያ ሆነ ? ለምን እንዲህ አደረግሁ ? የምንልባቸው ነገሮች አሉ ።

ወዳጆቻችን በየዘመናቱ የፈኩ ከዋክብት ናቸው ። ድንገት ጭልም የሚሉት ግን በእነርሱ ደካማነት ብቻ ሳይሆን በእኛም ትዕግሥት ማጣት ነው ። ወዳጆች የመጀመሪያ ቀን ያሳየናቸውን ሁልጊዜ ይፈልጉታል ። “አታስለምድ አታስቀር” ይባላል ። ካስለመዱ መቀጠል ይገባል ። ካስቀሩ ቅሬታ ያመጣል ። በዓይናችን የምናያቸውን ወዳጆች በጆሮአችን መገምገም አይገባንም ። ከጆሮ ዓይን ይበልጣል ። እነርሱ ፈቅደው ውስጣቸውን ካልገለጡልን በቀር ስለ እነርሱ ጥልቅ ጥናት ማድረግ አስፈላጊ አይደለም ። እግዚአብሔር የሰጠን አቅም የሌሎችን ጓዳ ለመሰርሰር የማይተርፍ ነው ። ዘላቂ ግንኙነት ደስ ይላል ። ፍቅር ግን የጋራ በመሆኑ ልሂድ ያለውን ማቆም አይቻልም ። ደግሞም በልቡ ሂዶ በአካል ከቀረ ሰው ጋር መኖር ሬሳ ታቅፎ እንደ መኖር ነው ። አንዳንድ ወዳጆቻችን በጣም ቀናዎች ነበሩ ። ፍጹምነትን ስንፈልግባቸው መልካምነታቸውን እንደ ክፋት አየነው ። በዚህ ምክንያት ገፋናቸው ። አንዳንድ የትዳር አጋሮች በጣም መልካሞች ነበሩ ። በሰው ወሬ ፣ ትዳራችንን ከጎረቤት ትዳር ጋር በማነጻጸር ቤታችንን አፈረስነው ። አለመውለዳችንን እንደ ርግማን ፣ ሀብት አለመያዛችንን እንደ ትዳር ውድቀት አየነው ። ያወሩልን ምነው ባስታረቁን ፣ ሰብቅ የነገሩን ምነው ዝም ባሉን ኖሮ ብለን ዛሬ ላይ እንቆጫለን ። ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታ ሳሉ የወንድና የሴት ችሎታ አደረግናቸው ። የሀብት ጥያቄም ፍቅርን ካፈረሰ ትዳሩ ሸቀጥ እንጂ ትዳር አልነበረም ። ቢሆንም ምነው ዘመዶቼ ተዉ ፣ ተዪ ባሉኝ እንላለን ። ምነው የሃይማኖት አባቶቼ በገሠጹኝ ኖሮ ብለን እንቆጫለን ።

ወታደር የሚማርክ ነገር አለው ። ዋስትና የሚፈልጉ ወታደር ማግባትን ይወዳሉ ። ወታደር ሥነ ሥርዓቱ ፣ ለአለቃው መገዛቱ ፣ ሕይወቱን ለአገር መስጠቱ ፣ ቆራጥነቱ ደስ ይላል ። ዘላለም ሞልቃቃ ሁኖ ከመኖር እንደ ወታደር ለአንድ ቀን ቆራጥ መሆን ብዙ ታሪክ ይለውጣል ። ደስታንም ይሰጣል ። ልጅን ለወታደርነት ማብቃት ይቻላል ። እንደ ወታደር አድርጎ ማሳደግ ግን አይቻልም ። ምክንያቱም ወታደርነት ምርጫም ፈቃድም ነው ። ልጅ መሳሳቱ ትምህርት ቤቱም ነው ። ቆሞ ከመሄዱ በፊት ብዙ ሺህ ጊዜዎች ይወድቃል ። ትክክል ከማሰቡ በፊት ብዙ የስህተት አሳቦችን ያስባል ። መሳሳት ካልተፈቀደለት ልጅ ሊታነጽ አይችልም ። ልጆቻችን እንደ ራሳቸው እያደጉ ሳለ የአገሩን ልጆች በማየት ጭቆና ማድረግ ፣ በዱላም ትክክለኛውን መንገድ አሳያለሁ ብሎ መነሣት ፣ የግል ንዴታችንን ልጆቻችን ላይ መወጣት ተገቢ አይደለም ። ከልክ በላይም ማድረግ ፣ ከልክ በታችም መጨቆን በልጆች ላይ የምንፈጽመው በደል ነው ። መውለድን ስናስብ ኃላፊነትንም አብሮ ማሰብ ይገባል ። በዕድሜ የገፉት ልጅ ስንወልድ ከአያያዝ ፣ ከአስተጣጠብ ጀምሮ ያሰለጥኑናል ። ስለ አስተዳደግም መጠየቅ ያስፈልገናል ።

“ገላጋይ አጥቼ ግልገሌን በላኋት” ይባላል ። ገላጋይ አስፈላጊ ነው ። አንድ ቀን የእብድ ሥራ መሥራታችን የማይቀር ነውና ገላጋይ ያስፈልገናል ። ለገላጋዩም አንድ ቀን ገላጋይ እንሆንለታለን ። ዛሬ ብንታመም አስታማሚ እናገኛለን ፣ አስታማሚአችንን አንድ ቀን እናስታምመዋለን ። በየተራ እንድንቸገር አድርጎ ሕይወትን ያዋቀረ እጅ ቡሩክ ነው ። ሁሉም በአንድ ጊዜ ሲቸገር ከባድ ነው ። ግልግልን አርዶ መብላት ሥጋው ለስላሳ ነው ። አንድ ቤተሰብን ግን የማያጠግብ ነው ። ለዕለት ከፊል ደስታን ይሰጣል ። ነገን ያለማየት ውጤት እንደሆነ ግን አዋቂ ሁሉ ይረዳዋል ። ግልገልን ለማረድ ቢላዋ ሲስል ገላጋይ ከመጣ ይገሥጸዋል ። ያቺ ግልገል ብታድግ ነገ ሙክት ትሆናለች ፣ እናት ሁናም ብዙ በጎችን ትወልዳለች ። ከአንድዋ ብዙ ይገኛል ። በማረድ ውስጥ አንድ መቶ ብር የሚያተርፈው ሰውዬ ፣ ገላጋይ ቢያገኝ ግን የማይቆጠሩ ሺህ ብሮች ወደፊት ያገኛል ። ግልገሏን ቢተዋት በባንክ ገንዘብ እንዳስቀመጠ ይቆጠርለታል ። እየወለደ ይመግበዋል ።

ብዙ ግልገሎቻችንን ገላጋይ አጥተን አርደናቸዋል ። ራእያችንን ለእልህ አርደነዋል ። ወዳጆቻችንን ለወረት አድልተን ገፍተናቸዋል ። ንብረታችንን በስሜት አብደን ሸጠናል ። የምንሰጥ የነበርን ተቀባይ የሆነው ምናልባት ግልገላችንን አርደን ነው ። አዲስ ትውልዶችን የቀጨነው ፣ የማይረካው ፍላጎታችን መጠቀሚያ ያደረግናቸው ገላጋይ አጥተን ነው ። ገላጋይ የሚገላግለው በፍቅር እጅ ፣ በምክር ፣ በጸሎት ነው ። ቢላዋ የያዘውን እብድ እጁን የሚይዘው ገላጋይ ነው ። “ተው ታገሥ” እያለ በምክር የሚያበርደው ገላጋይ ነው ። “በስመ አብ በል ሰይጣንን ገሥጸው” እያለ የሚጸልየው ገላጋይ ነው ። ገላጋይ የመሥዋዕትነት ልብ ፣ የምክር ሀብት ፣ የጸሎት ኃይል ያስፈልገዋል ። ገላጋይን ለመስማት አክብሮትን ማዳበር ይገባል ። አግም አደግ ስንሆን ምክርን መስማት ያቅተናል ። ሁሉን በማስተዋሌ ልፍታው ስንል ጸሎትን እናቆማለን ። ሕይወት ያለ ገላጋይ ብዙ ግልገሎቻችንን የምናርደባት የጸጸት ኮረብታ ናት ። ነገን የሚያዩልን ገላጋዮች ፣ ወጋገን የሚፈነጥቁልን መካሪዎች ያስፈልጉናል ። “የሚቆጡንን መካሪዎች አታሳጣን” ብሎ መጸለይ ትልቅ ሊጦን/ልመና ነው ። አስታራቂ ያስፈልገናል ። የምንሰማውና የምናከብረው አባት ያሻናል ። ያጠፋናቸው አዋቂዎችና አባቶች ለዛሬው መቅበዝበዛችን ያስፈልጉን ነበር ። “ተራጋሚ ራሱን ደርጋሚ” እንዲሉ አዋቂዎችን ስንጎዳ እኛው እንጎዳለን ። የልጆች ቤት ገላጋይ የለውም ። የበለው ዕድር የቅርጫ ሥጋ ያደርገናል ። ዛሬ የምናርደው ግልገላችን ዕድሜአችን ሲገፋ ያጸጽተናል ።

አቤቱ እግዚአብሔር ሆይ ፣ መካሪ አታሳጣን ። ተመክሮ መመለስን አድለን ።

የብርሃን ጠብታ 23

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ኅዳር 16 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም