መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » መዝሙረ ምእመን » መዝሙረ ምእመን 1

የትምህርቱ ርዕስ | መዝሙረ ምእመን 1

መዝሙረ ዳዊት 1፡1 ላይ የተመሠረተ ምክር

ማባበል ካለበት ፣ “አንተ እኮ ትልቅ ነህ” ከሚለው ፣ አስብቶ ከሚያርደው ፣ በውዳሴ ከንቱ ከሚያሰክረው ፣ ልጅን በአባቱ ላይ ፣ አቤሴሎምን በዳዊት ላይ ከሚያሥነሣው ከአኪጦፌል ምክር ፣ “እኔ የቋጠርሁት አይፈታም” እያለ በኃጢአቱ በሚኮራው ፣ ክፉ ሰው ምክር ካልሄድህ ምስጉን ነህ ። ፈተና ወዳንተ ሳይመጣ ወደ ፈተና መሄድ ፣ መድኃኒት አለና ብሎ በሽታን መዳፈር ፣ በሚያዳልጥ ስፍራ ላይ ቆሞ “አድነኝ” እያልህ መጸለይ ፣ እየጠጣህ ላለመስከር መታገል ፣ ከተቃራኒ ጾታ ጋር በድብቅ ስፍራ ተቀምጠህ እንዳትወድቅ መሞከር ከንቱ ግብዝነት ነው ። ነገር ግን በኃጢአተኛ መንገድ ካልቆምህ ፣ ኃጢአተኞች ሲያልፉ “ና እንሂድ” አይሉህምና ዕድለኛ ነህ ፣ ምስጉን ነህ ። ክፉ ባልንጀርነትን ካላራቅህ ፣ ደግ ባልንጀርነትን ካልፈለግህ የድንገት ፍላጻ ያቆስልሃል ። የዝሙት ፊልም እያየህ ለጸሎት አትነሣሣም ፣ ተውኔት ቤት እየዋልህ ወደ ጉባዔ እግዚአብሔር አትሄድም ። ኃጢአትን ከነምክንያቱ ከተውህ ምስጉን ነህ ።

በዋዛ ፈዛዛ ዘመንህን ካልጨረስህ ፣ “ሳቅ አምጡ” እያልህ አዝማሪ ዘዋሪ ካልጋበዝህ ፣ በመዳን እንጂ በመደንዘዝ ደስታን ካልፈለግህ ብፁዕ ነህ ። ከዘላለም ሕይወትህ ፣ ከምድራዊ ኑሮህ ጋር ምንም ግንኙነት በሌለው ነገር ጊዜህን ካላባከንህ ብፁዕ ነህ ። ሺህ ሰው በአንዴ ሲሞት “የአገሬ ገበሬ ይዋደዳል” ከሚሉ ፣ ሰው አገር ፣ አገርም ሰው መሆኑን ረስተው “አገር ከሚሞት ሰው ይሙት” ከሚሉ ፣ የራሳቸው ላብ እያስጨነቃቸው በሰው ደም ከሚቀልዱ ፣ እነርሱ እየሸሹ “ደም ሳይፈስስ ስርየት የለም” ከሚሉ ፣ “ያለ ምንም ደም ኢትዮጵያ ትቅደም” እያሉ በደም ጎርፍ ከሚታጠቡ ፣ ሺህዎችን ሸኝተው ምንም እንዳልተፈጠረ ከሚያፈጥጡ ፣ የልጃቸውን ከባድ እንቅልፍ እየፈሩ በሰው ልጅ ሞት ከሚነግዱ ከዋዘኞች ወንበር ካልተቀመጥህ ብፁዕ ነህ ።

ወደ ገደል እየመራ ስትወድቅ ከሚስቀው ከክፉዎች ምክር ፣ በቃሉ ነው ነው የምትድነው ። ለውድቀት ከሚያጋልጡ ቦታዎች ፣ ሁኔታዎች የምትርቀው ያለማቋረጥ ነገረ መለኮትን ስታስስ ነው ። ክፉ ባልንጀርነትን ፣ የመብል ማኅበርን የምታመልጠው በቅዱሳን ኅብረት ፣ በምእመናን አንድነት ነው ። ገዳይ ጨካኝ ነው ፣ ዋዘኛ ግን በሬሳ ላይ ሳቅና ቅኔ የሚያመርት ነው ። በምድር ላይ የጭካኔ ጥጉ ዋዘኝነት ነው ። ዋዘኝነት እውነታን አለመቀበል ፣ ፣ ደምን ዝናብ ነው ፣ ሞትን ልደት ነው ብሎ መሳለቅ ነው ። በዚህ ወንበር ያልተቀመጠ ፣ መቼም ዋዘኛ አይራመድምና የሚራመዱትንም ይተቻልና ፤ በዚህ የስላቅ መደብ ካልተቀመጥህ ብፁዕ ነህ ።

አቤቱ ቃልህን እወደው ዘንድ በመልካም አስበኝ !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ተጻፈ ሐምሌ 23 ቀን 2015 ዓ.ም

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም