የትምህርቱ ርዕስ | መጠጊያችን

“አምላካችን መጠጊያችንና ኃይላችን ፥ ባገኘን በታላቅ መከራም ረዳታችን ነው።” (መዝ. 45፡1።)

ዓለም ከመቼውም ጊዜ ይልቅ የኃይል ጥገኛ ሆናለች ። ትልልቅ ማሽኖችን ፣ ግዙፍ ፋብሪካዎችን ለማንቀሳቀስ ኃይል አስፈላጊ ሆኗል ። ብዙ አምራች ድርጅቶች በኃይል አቅርቦት እጥረት ምክንያት ሥራ ያቆማሉ ፣ ሠራተኛ ይበትናሉ ። ደኖች በመመናመናቸው ፣ ቢኖሩም የሰውን የኃይል ፍላጎት ለማሟላት በቂ ባለመሆናቸው እያንዳንዱ ቤተሰብና ግለሰብ የኃይል ጥገኛ ሆኗል ። በእጃችን ላይ የያዝናት ትንሽ ተንቀሳቃሽ ስልክ ኃይልን ካልተሞላች አትሠራም ። ኃይል ለእያንዳንዱ ቤት የብርሃን ፍላጎት ወሳኝ ነው ። የዕለት ምግባችንን ለማብሰል የመንግሥታትና የባለጠጎች የኃይል ጥገኛ ከሆንን ሰንብተናል ። ኃይል እጅ መጠምዘዣ እየሆነባቸው የተቸገሩ አገራት የኃይል አማራጭን ያስጠናሉ ። እያንዳንዱ አገር የራሱ የሆነ ውድ ነገር ፣ ተፈላጊ የሆነበት ጸጋ ቢኖረውም ሁሉም አገር በተመሳሳይ መንገድ የኃይል ተጠቃሚ ነው ። ኃይል ብርሃን ለማግኘት ፣ ለመጓጓዝ ፣ በኮምፒውተር የሚሠሩ ነገሮችን ለመጠቀም ፣ ምግብ ለማብሰል ፣ በስልክ ለመገናኘት አስፈላጊ ሆኗል ። መንግሥታት መሠረታዊ ነገሮችን ካሟሉ ከተሞች በዜጋው ይመሠረታሉ ። ከእነዚህ መሠረታዊ ነገሮች ውስጥ መንገድ ፣ ውኃ ፣ መብራት ቀዳሚ ናቸው ። እነዚህን አንድ በረሃ ላይ ያሟላ መንግሥት ደርሶ ሲመለስ የሞቀ ከተማ ያገኛል ።

የኃይል አሰላለፍ እየተባለ የሚወራ ነገር አለ ። የምዕራብና የምሥራቅ አገራት በተሸከሙት አጥፊ መሣሪያ ፣ በኒውክለር ኃይል ጭምር ይፎካከራሉ ። የጦር ቃል ኪዳን ማኅበር ይመሠርታሉ ። ኃይል የምዕራብና የምሥራቅ ተፎካካሪ አገራትን ፈጥሯል ። ኃይል ዓለምን አንድ የሚያደርግ ወይም የሚያጠፋ ሊሆን ይችላል ። በቆዳ ስፋታቸው ፣ በሕዝብ ብዛታቸው አነስተኛ የሆኑ አገራት ከኃያላን መንግሥታት ጋር መጣበቅ ፣ የደኅንነት ዋስትና መጠየቅ አስፈላጊያቸው ይሆናል ። ኃያላን መንግሥታት የሚባሉት የስማቸውን ቅጽል ያመጣላቸው አንደኛው ኃይል ነው ። ኃይል የዓለምን ፖለቲካና ኢኮኖሚ ይዘውራል ።

ፍትሕን ከዓለም የሚጠብቁ የሚኖሩባትን ዓለም የማያውቁ ሞኞች ናቸው ። ዓለም ወላዋይ ፣ ዓለም ዋሾ ናት ። ዓለም ካሸነፈው ጋር የምትሰለፍ አድር ባይ ናት ። ሁለቱንም ተፋላሚ በርቱ እያለች ፣ እያጫረሰች ዜና የምትሠራ ናት ። ምንም እውነተኛ ቢሆን ደካማው የሚጮህለት የለም ። በኃይል የተካከሉ አገራት ሲጣሉ ሁሉም ገላጋይ ይሆናል ። ህንድና ፓኪስታን ሁለቱም የኒውክለር ባለቤቶች በመሆናቸው ጠባቸው ፈጣን ገላጋይ አለው ። ኒውክለር ዘመድ አያውቅምና ። ኃይል ለዓላማችንና ለዘመናችን ትልቅ ርእስ ነው ። እነዚህ ሁሉ ኃይላት አንድ ቀን የነበሩ እስከማይመስል ድረስ ይጠፋሉ ። ይደመሰሳሉ ። አንድ ኃይል ግን አለ ።

ሃይማኖት የለሾች፡- “አንድ ኃይል አለ ይላሉ” እየተባለ ይነገራል ። ለእግዚአብሔር የሰጡት ስም “አንድ ኃይል” የሚል ነው ። እውነተኛው ኃያል እርሱ ብቻ ነው ። የአንድ ዘመን ኃያላንን ዓለም ለማግኘት አልተቸገረችም ። ፈርዖንም ፣ ናቡከደነጾርም ፣ ቄሣርም ፣ ናፖሊዮንም የጊዜአቸው ጀግኖች ነበሩ ። ታላቁ እስክንድር ታሪኩ እንጂ አስፈሪነቱ ዛሬ የለም ። ኃያላን በድካም ፣ ባለጠጎች ቁራሽ በመለመን የሚጨርሱበት ዓለም ናት ። እግዚአብሔር ግን እውነተኛው ኃይላችን ነው ። ተናግሮ የሚረታልን ፣ ታግሎ የሚጥልልን ኃይል እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ዘላለማዊ ብርሃንን ያገኘንበት ፣ በእባቡ ራስ ላይ ቆመን የፎከርንበት ኃይላችን እግዚአብሔር ነው ። የጦር ሠራዊት የነበረው ዝነኛው ንጉሥ ዳዊት “ኃይላችን እግዚአብሔር ነው” ማለቱ ድንቅ ምስክርነት ነው ። በዐፄ ምኒልክ ጎራዴ ላይ የተጻፈው ጽሑፍ እንዲህ የሚል ነው፡- “የምኒልክ ተስፋው እግዚአብሔር ነው ።”

እግዚአብሔር የኃይልን መንፈስ የሚሰጥ አምላክ ነው ። በማይታየውና በሚታየው ትግል ኃይላችን እግዚአብሔር ነው ። በመንፈሳዊ ዓለም ኃይል የሚፈልጉ ነገሮች አሉ ። የመጀመሪያው ፍቅር ነው ። ሁሉን በእኩል ለመውደድ ፣ ሰውን እንደ ራስ ለማፍቀር ኃይል ይፈልጋል ። ሁለተኛው ይቅር ለማለት ኃይል ያስፈልጋል ። በእርቅና ፍትሕ አፈላላጊ ኮሚቴ ፊት ተበዳዮች ሲሰድቧቸው ፣ እየከፈሉ እንደሆነ ስለሚሰማቸው በዳዮች ጠንከር ይላሉ ። “ይቅር ብዬሃለሁ” ሲባሉ ግን መቋቋም አቅቷቸው ይወድቃሉ ። ሦስተኛው ኃይል ፈላጊ አገልግሎት ነው ። የሚፈልገውን የማያውቅ ማኅበረሰብን ፣ ለነፍሱ ጉዳይ መጥቶ ሥጋዊ ጦርነት የሚከፍት ትውልድን ፣ በአጋንንት እስራት ተይዞ የሚወደውን የሚጠላ ወገንን ማገልገል አቅም ይፈልጋል ። በምድር ላይ በኃይለ መንፈስ ቅዱስ ካልሆነ በቀር ማገልገል ከባድ ነው ። አባቶች በምናኔና በምንኵስና ሕይወት ማገልገልን የፈለጉት አገልግሎት ትጥቅን አጠር ማድረግ የሚፈልግ ፣ እኔ ብሞት ማንንም አልጎዳም የሚል ቆራጥ ሰውን የሚሻ ስለሆነ ነው ። አገልጋዮች የሚከፍሉልንን ዋጋ ብናውቅ ሽቅብ መገላመጥ ባልደፈርን ነበር ።

እግዚአብሔር ለማፍቀር ፣ ይቅር ለማለት ፣ ለማገልገል ኃይላችን ነው ። አሜን!

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ኅዳር 25 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም