መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ምስጋና ቢስነት

የትምህርቱ ርዕስ | ምስጋና ቢስነት

በቅበላ ዋዜማ ምግቡ እንዳይበላሽ እየተባለ ይበላል ። ሰውዬው “ብላ ነገ ጾም ስለሆነ ምግቡ ይበላሻል” እያሉ ብዙ ሲያበሉት፡- “እኔ ቀድሜ ልበላሽ ነው” አለ ይባላል ። ሕፃን ልጅ በቃኝን ስለማያውቅ ያለ ልክ በልቶ ይታመማል ። “አልጠግብ ባይ ሲተፋ ያድራል” ይባላል ። ምግብን በልክ ያልበላ ሌሊቱን በሙሉ ሲጨነቅ ያድራል ። የሰው ልጅ ዕድገቱም ክብረቱም ይበቃኛል ሲል ነው ። ከብቶች እንኳ አተላ ጠጥተው ሲጠግቡ ጥለው ይሄዳሉ ፣ አልኮል መጠጥ እየጠጣ እያጋባ ተመልሶ የሚጠጣው ሰው ብቻ ነው ። አንበሳ የሚበቃውን ከበላ በኋላ ለሦስት ቀናት ያህል ዕረፍት ያደርጋል ። የተሰጡን አካላት ዕረፍት ይፈልጋሉ ። ጾም ሰማያዊ በረከት ከመስጠቱም በላይ የአካል ሠራተኞችም እንዲያርፉ ያደርጋቸዋልን ። በማረፍ ውስጥ ራሳቸውን ያፀዳሉ ። ለመኪናው ሰርቪስ የሚያስበው ሾፌር እኔም ማረፍና መጠገን አለብኝ ብሎ አያስብም ። ሰዎችን ለማስደሰት ሲሮጥ የሚኖረው አሁን ደግሞ ራሴን ላዳምጥ ብሎ የራሱ የደቂቃ ዕድሜ አይሰጥም ። አንዳንድ ሰዎች በገዛ ቤታቸው ምግብ እየበሉ ሰው ሲመጣባቸው ይደነግጣሉ ። ብቻውን መብላትም የመስረቅ ያህል የሚያሳፍረው ሰው አለ ። ብዙ ብኩኖች ዘመናትን በሩጫ ያሳልፋሉ ፣ ትርፍና ኪሣራቸውን መተመን ግን አልቻሉም ።

በሕይወት ውስጥ ይበቃኛል ማለት ትልቅ እርካታ ነው ። ሰው ሁሉን መያዝ አይችልምና ሁሉን ልጨብጥ ማለትን ፤ ሁሉን አዋቂ አይደለምና ሁሉን ልናገር ማለትን ማቆም አለበት ። ሀብቱም ፣ ሥልጣኑም ፣ ዓለሙም ገዳሙም አይቅርብኝ ማለት ከግምት ላይ ይጥላል ። ሁለት እግር አለኝ ተብሎ ሁለት ዛፍ አይወጣም ። ሁለት አባራሪም አንድ አይዝም ። ይበቃኛል ስንል እርካታን እናገኛለን ። የረካ ያመሰግናል ። ምስጋና ቢስነት ልክን ባለማወቅ የሚመጣ ነው ። ለመሰንበቻው ዓለም ፣ ጠዋት ለማታ ለማያስተማምነው ዕድሜ ያለን በቂ ነው ። ስለ ዕለት ማሰባችን ጤነኛነት ነው ፣ ስለ ዓመት መጨነቃችን ግን የተሸከምነውን ኃላፊ ማንነት አለመገንዘብ ነው ።

ሁልጊዜ የበላያቸውን የሚያዩ ሰዎች ምስጋና ቢስ ይሆናሉ ። ለሁሉም በልኩ እንደሚሰጠው እየረሱ እንደ እገሌ ካልሆንሁ የሚል ውድድር ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች ደስታ ይርቃቸዋል ። እነርሱ አንድ ናቸው ፣ መሆን የሚፈልጉት ግን እንደ ብዙዎቹ ነው ። ያልተሰጣቸውን ሲፈልጉ የተሰጣቸውንም ያጡታል ። ሰውዬው፡- “እግር የሌለው እስካይ ድረስ ጫማ የለኝም ብዬ አዝን ነበር” ብሏል ። የበታቾችን ስናይ እናመሰግናለን ። “እኔ ምን ሆንኩ (” ብለን ራሳችንን እንገሥጻለን ።

የአሁኑንና የበፊቱን ኑሮአቸውን የሚያወዳድሩ ሰዎች ምስጋና ቢስ ይሆናሉ ። የሚገርመው የድሮ ኑሮአቸው ቀኑ በመርዘሙ ምክንያት ረስተውት እንጂ መልካም አልነበረም ። ዛሬን ለማክፋፋት ፣ በዛሬው ሁነት ላለማመስገን ትላንትናን ቆንጆ ማድረግ ይፈልጋሉ ። በዚህ ምክንያት ከእውነትና ከቅን ፍርድ እየተለያዩ ይመጣሉ ። እስራኤል ስለ መናው ላለማመስገን የግብጽን ሽንኩርት ያደንቁ ነበር ። ግብጻውያን ሥጋ ሲበሉ እነርሱ ሥጋ የበሉ እንዲመስላቸው ሽንኩርት ጠብሰው ይበሉ ነበር ። ይህንን ኑሮ አሁን ካለው ከመናው ጋር አነጻጸሩት ። በርግጥ በዓለም ላይ ነገሮች እየባሱ ፣ አገዛዞች እየጠነከሩ በመምጣታቸው ያለፈውን ማመስገን እየበዛ ነው ።

ያምናን ቀን አማሁት ላፌ ልጓም የለው ፣
መጣ የዘንድሮው እጅ እግር የሌለው ።

ያምናን ሰው አማሁት ላፌ ለከት የለው ፣
የዘንድሮው መጣ እግር እጅ የሌለው ።

ምስጋና ቢስነት ከከንቱ ውድድር ፣ ከእውቀት አልባ ንጽጽር የሚመጣ ነው ። ምስጋና ቢስ ሁሉም ነገር የማይጥመው ፣ ሁልጊዜ ለእኔ ብቻ ይደረግ ባይ ፣ የሚፈልገውን በትክክል የማያውቅ ፣ በአሉታዊ ነገር የተሞላ ፣ ቅንነቱን የተሰረቀ ፣ የተደረገለትን ሳይቀበል ሌላ የሚፈልግ ፣ ለእኔ ትንሹ ተሰጠኝ ብሎ የሚቀና ሰው ማንነት ነው ። ምስጋና ቢስ ነጥቆ በረር ነው ። እግዚአብሔርም ሰዎችም አድርገውለት ለምስጋና የማይመለስ ነው ። አምላካቸውን ተመስገን ፣ ሰዎችን እግዚአብሔር ይስጥልኝ የማይሉ ወገኖች ጉዶች ናቸው ። በብዙ መንገድ የምስጋና ዕዳ አለብን ። ለዛሬው ማንነታችን አስተዋጽኦ የነበራቸውን ረስተናል ። በምርኵዝ የነበረ ሲበረታ ምርኵዙን ጥሎ ይረሳዋል ። ምርኵዝ የሆኑን ሰዎች ግን የሚረሱ አይደሉም ። በዓለም ላይ የመጨረሻው ውሸታም ከሰዎች ምንም አልተቀበልኩም ባይ ነው ።

ምስጋና ቢስነት ደስታን ያሳጣል ። ሰዎች እንዲጨክኑብን ያደርጋል ። ቆሻሻ ነገር ዝንብ እንደሚሰበስብ ምስጋና ቢስነት አጋንንትን ይሰበስባል ። ለሁሉ የሚሰጥ አንድ እግዚአብሔር ፣ በፈቃዱ የሚያኖረን አምላክ አለ ። የተሰጠንን መሆን ጸጋ ነው ። በተሰጠን መደሰት ብልሃት ነው ። ምስጋና ከፈጠረን ጋር የሚያገናኘን ድልድይ ነው ። ምስጋና ቢስነት ድልድዩን ይሰብረዋል ። ስለዚህ ዓለም ገዥዎች ፣ ስለ ፖለቲከኞች ከመጠን በላይ ማሰብ ብስጩና አማራሪ ያደርጋል ። ሁሉን ሊለውጥ ሥልጣን ላለው ቀኑንና አገሩን መስጠት ያሳርፋል ። እስትንፋሳችን በአፍንጫችን ካደረች ተመስገን ማለት አለብን ። ስለ መኖራችን እግዚአብሔር ይመስገን ።

ምስጋና ቢስነት እስራት ነው ። እግዚአብሔር ይፈታል ። እንዲህ ተብሎ እንደ ተጻፈ፡- “እግዚአብሔር የታሰሩትን ይፈታል ።” (መዝ. 145 ፡ 7) ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 11 ቀን 2017 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም