መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ምክር ለሰሚው » ምክር ለሰሚው /33

የትምህርቱ ርዕስ | ምክር ለሰሚው /33

ወዳጄ ሆይ !

ጥበብ ስትጠራህ አትዘግይ ፤ ዕድል ከጊዜ ጋር በማይፈታ ቋጠሮ ታስሯል ። ያልያዝከውን ለመጨበጥ ፣ የጨበጥከውን መልቀቅ አስፈላጊ የሆንበት ጊዜ አለ ። የማያዩ የሚያዩትን ፣ አላዋቂዎች አዋቂዎችን ሲተቹ ያ ዘመን ግልብጥ ዘመን ነው ። ጥሩ ሥራን ለሕሊና ምግብነቱ እንጂ ለሰማይ ሽልማቱ ብቻ አትሥራው ። የመልካም ነገር ዋጋ ከፋይ እግዚአብሔር መኖሩንም እመን ። ሁለት ጊዜ ደውለህ ፣ ሦስት ጊዜ ፈልገህ ሊያገኝህ ያልፈለገውን ሰው ፍላጎቱን አክብርለት።

ወዳጄ ሆይ !

ወንድምህ ሲጠቃ ቀጥሎ አንተም ተጠቂ ነህና በወንድምህ ክፉ ቀን ለራስህ ጩኽ ። ልጅህን በመንፈሳዊ ድፍረት ፣ በእውቀትና በእግዚአብሔር በመተማመን አንጸው ። መስበክ ማለት ወደ እሳት እየጨፈሩ የሚሄዱትን መመለስ ፣ ቀድሞ አይቶ ሰውን ማስጠንቀቅ ነው ፤ ስብከት እስትንፋስ ነው ። በመንፈሳዊ አንድነት ያለውን ክፍተት ቶሎ ካልዘጋኸው ፣ እንደ ሁለት የሸለቆ ግድግዳ እየተያዩ እንደማይገናኙ መሆን ነው ። ወደ ኋላ ያለውን ሰው ወደፊት አምጥተህ አለማምደው ። ጊዜና መድረክ የተሰወረ ጥበብን ይገልጻሉ ።

ወዳጄ ሆይ !

የተቀበለችህ አገር ላይ የአደጋ ስጋት አትሁን ። በብዙ መገኘት ቢያቅትህ ለወዳጅህ በጥቂቱ እንኳ ድረስለት ። መስጠት ባትችል አብረኸው መቆም ትልቅ ዋጋ አለው ። ሞልቶ የተረፈውን ክብርህን በሆዳምነትህ አታጕድለው ። ያለፈውን ጊዜ ለትምህርት ብቻ አስታውሰው ። ባለፈው ሲጸጸቱ መኖር መመጻደቅ ፣ ባለፈው መልካም ነገር ብቻ መኩራት መኖርን ማቆም ነው ።

ወዳጄ ሆይ !

አንተም አንድ ቀን በሌላው አገርና ቤት እንግዳ ትሆናለህና ለእንግዶች ቅድሚያ ስጥ ። ንግግርህ ካስናቀህ ዝምታን ገንዘብ አድርግ ። ብዙዎችን ከማሸነፍ ራስን ማሸነፍ ይበልጣል ። ላንተ ቦታ የሌላቸውን ሰዎች ስታሳድድ አክባሪዎችህን እንዳታጣ ተጠንቀቅ ። ዱር የሚያስፈራህ ሰዎች ስለሌሉበት ነው ። ሰው የሌለበት ከተማ ከሲዖል በላይ ያስጨንቃል ። ስለ ጎረቤቶችህና ስለ ከተማው ሰው እግዚአብሔርን አመስግን ። ይህ ሁሉ ወገን የማትከፍለው ጠባቂህ ነው ።

ምክር ለሰሚው 33

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ሰኔ 14 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም