መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ሥጋዊ አሳቤ

የትምህርቱ ርዕስ | ሥጋዊ አሳቤ

 እንደ ሰላይ ወዳጅ መስሎ አቅሜን ይለካኛል ። አብሮኝ እየተጋበዘ መድከሜን ለጠላቴ ሰይጣን ያሳብቅብኛል ። የውጭውን ጠላት ስታገል በውስጤ ሥጋዊ አሳቤ ያደባብኛል ። ስቆጣ ሎሌ ፣ ስበርድ ጌታ እየሆነ ይመጣብኛል ። ክረምት ከበጋ ይተጋብኛል ፣ እኔ ተኝቼ ሥጋዊ አሳቤ ከተማ ያስሳል ። ለማመስገን ስነሣ ጉድለቴን ይቆጥርብኛል ። ለመንፈሳዊ ነገር ስታጠቅ በከንቱ ነገሮች ጊዜዬን ይበላል ። ሥጋዊ አሳቤ እንደ ክፉ ጎረቤት ይነዘንዘኛል ። አብረን ማርጀታችን ፣ ስንጣላ ስንታረቅ ዘመን ማሳለፋችን ይደንቀኛል ። ሥጋዊ አሳቤ አካሌ ደክሞ ሳለ ነፍሴን አባብሎ ይወስድብኛል ። ልብ አይሞትምና ነፍሴ ማድረግ ቢያቅታት በአሳብ ስትዘምት ትውላለች ። ነፍሴ በተመስጦ ወደ ሰማይ ስትሄድ ሥጋዬን ይሻረክብኛል ። ሥጋዬ አገሯ መሬት ነውና ከመሬት ስበት ጋር ወደ ታች ትጎትተኛለች ።
በሁለት አሳብ በደግነትና በክፋት ስንገላታ ሥጋዊ አሳቤ ብዙ መረጃዎችን እየጠቀሰ ክፋት ያስከብርሃል ይለኛል ። ነፍሴም መረጃ ከእምነት አይበልጥም ትለኛለች ። አስታራቂ መስሎ ሥራውን የሚሠራ ፣ ለደግነት ትቶ ለክፋት የሚያደላ ሥጋዊ አሳቤ እርሱ ይሞግተኛል ። መቅዘፊያዋን እንደ ጣለች ጀልባ አቅጣጫ እያሳተ ፣ የአሳብ ሰይፍ ፣ የበቀል ስለት እያስጨበጠ ሥጋዊ አሳቤ በቂም ያዘምተኛል ። ከክርስቶስ መከራ ያንተ ይበልጣል እያለ ያስታብየኛል ። ሥጋዊ አሳቤ ገላጋይ መስሎ የሚያስደበድበኝ ፣ ጠበቃ መስሎ የሚያስረታኝ ፣ ወዳጅ መስሎ ወደ ገደል የሚገፈትረኝ እርሱ ነው ። በዝማሬ ውዬ በልቅሶ እንዳድር ፣ በፍቅር ውዬ በቂም እንድሰክር የሚያደርገኝ ፣ አንዱን ቀን ሁለት የሚያደርግብኝ ሥጋዊ አሳቤ እርሱ ነው ።
እንደ ማጥ ጉዞ ወጣሁ ስል የሚይዘኝ ፣ ጨረስሁ ስል የሚያስጀምረኝ ፣ ሸመገልሁ ስል ልጅ የሚያደርገኝ ፣ ታጠብሁ ስል መልሶ የሚያቆሽሸኝ ፣ ተፋሁ ስል እንደ ውሻ የሚያስልሰኝ ሥጋዊ አሳቤ በክለሳ ኑሮ የሚያደክመኝ እርሱ ነው ። በእምነት ሰላሜን አገኘሁ ስል በአዳዲስ ጉድ የሚያናውጠኝ ፣ እጆቼን ፣ ዓይኖቼን ፣ ጆሮዎቼን እየኮረኮረ ክፉ ወሬ የሚያስቃኘኝ ሥጋዊ አሳቤ እርሱ ነው ። አዳም ሲወድቅ ውስጤ የገባው ረቂቅ መንግሥት ሥጋዊ አሳቤ ነው ። ሳላውቀው ከእኔ ጋር የኖረው ፣ ተገላገልሁት ለማለት የማልደፍረው ጠላቴ ሥጋዊ አሳቤ እርሱ ነው ። አገሬ በሰማይ ነው ስል ጎሣ የሚያስቆጥረኝ ፣ ተበደልሁ እንጂ በደልሁ የማያሰኘኝ ፣ መንግሥተ ሰማያት ላያስገባኝ ትክክል ነህ እያለ የሚያጸድቀኝ ሥጋዊ አሳቤ እርሱ ነው ። አገልግሎት ሕይወትህ ነው እያለ ከሰው የሚያጋድለኝ ፣ ሕይወት ክርስቶስ መሆኑን በዘዴ የሚያስጥለኝ ፤ ከመድረክ አትጉደል እያለኝ ከጽሞና የሚያጎድለኝ ፣ በዘዴ የጠለፈኝ ሥጋዊ አሳቤ እርሱ ነው ።
ኃጢአትን ጽድቅ ለማድረግ ሱባዔ የሚያስገባኝ ፣ ሃይማኖቴን ለመለወጥ የሚያጸልየኝ ሥጋዊ አሳቤ እርሱ ነው ። እንደ አቡን ሥልጣነ ክህነት የሚሰጠኝ ፣ ሳልሾም የተሾሙትን የሚያስንቀኝ ፣ የሕልም ዓለም የሚያወርሰኝ ሥጋዊ አሳቤ እርሱ ነውና በቁም የሚያቃዠኝ ። ሚስቴን አመንዝራ ፣ ወዳጄን ጉድጓድ ማሽ አድርጎ የሚስልብኝ አእምሮዬን የሚያቆሽሸው ፣ ባልተጨበጠ ነገር የተጨበጠ ጦርነት የሚሰጠኝ ሥጋዊ አሳቤ እርሱ ነው ።በስግብግብነት ከተማውን ካልገዛህ የሚለኝ ፣ አልጠግብ ብዬ ስተፋ የሚያሳድረኝ ፣ የኪስ ጣዖት የሆነውን ገንዘብ የሚያሳየኝ እርሱ ሥጋዊ አሳቤ ነው ። በአሥራት ታማኝ አድርጎ ለድሀ የሚያስጨክነኝ ፣ ሬሳ እየተራመድሁ እንዳልፍ የሚያደርገኝ እርሱ ነው ፤ ሌላ ጊዜም ለድሀ ቸር አድርጎኝ የእግዚአብሔር ሥራ እንዲበደል አሥራቴን የሚያሰርቀኝ ሥጋዊ አሳቤ ነው ፣ ጎዶሎ ጽድቅ ውስጥ የሚያስዋኘኝ ። ከሥጋው ጦመኛ ነኝ ፣ ከመረቁ አውጡልኝ የሚያሰኘኝ ፣ ከወገብ በላይ ታቦት ፣ ከወገብ በታች ጣዖት የሚያደርገኝ ሥጋዊ አሳቤ እርሱ ነው በሁለት ማንነት የሚያኖረኝ ።
ካድሁ እንዳልል በሃይማኖታዊ ፉከራ እየጠመደኝ ፣ ቀጥሎ ሁሉን የሚያስረሳኝ ፣ በስሜት እሳት የሚያሟሙቀኝ ሥጋዊ አሳቤ እርሱ ነው እኔን ለእኔ ያስጠፋኝ ። እያደባ የሚይዘኝ አውሬ ፣ እንደ እባብ ለመንደፍ የሚለሰልሰኝ ጠላቴ እርሱ ሥጋዊ አሳቤ ነው ። ሁሉም ሰው ኀጥእ ነው ብሎ ኃጢአት አሠርቶኝ ፣ ቀጥሎ አንተማ ከእንግዲህ ክርስቲያን አይደለህም የሚለኝ ፣ አሳስቶ የሚከሰኝ ሥጋዊ አሳቤ እርሱ ነው ። የሰይጣን ቆንሲል ሁኖ በውስጥ የሚዋጋኝ ሥጋዊ አሳቤ እርሱ ነው ። እንደ ክፉ ጎረቤት የሚነዘንዘኝ ፣ እንደማይሸጡት ልጅ መላቀቂያ ያሳጣኝ ሥጋዊ አሳቤ እርሱ ነው ። እንደ ባሕር ንውጽውጽታ የማያጣው ሥጋዊ አሳቤ እርሱ ነው ። የዘመኑ ሰማዕትነት ሥጋዊ አሳብን ማሸነፍ ነው ። እባክህ ጌታዬ ሥጋዊ አሳቤን አሸንፌ መንፈሳዊ እንድሆን ፣ የጨለማን አሳብ ጥላቻን ድል ነሥቼ ውሉደ ብርሃን እንድሆን እርዳኝ ። ክፉ ከሆንሁት ከራሴ አድነኝ ። ለዘላለሙ አሜን ።
ሐምሌ 20 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም