ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ከመስቀል አውርደው ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እያሉ የገነዙት ሁለት ሰዎች ናቸው ። የአርማትያሱ ዮሴፍና የማታው ተማሪ ኒቆዲሞስ ናቸው ። በስውር ተምረው በግልጥ መሰከሩ ። ዛሬ አሥር ሰዎች ብቻ ስለ ተገኙበት ቀብር በታላቅ ኀዘን እንሰማለን ። ሟች ወገናችንን አሥር ሰው ስለ ቀበረው ውስጣችን ያዝናል ። ጌታችን ግን ሁለት ሰዎች ገንዘው ቀብረውታል ። ይህንን ስሜታችንን እርሱ አስቀድሞ ተቤዥቶታል ። በሕይወቱ ከአምስት ገበያ የሚበልጥ ሕዝብ የተከተለው በሞቱ ሁለት ሰዎች ብቻ ገነዙት ። ከብዙዎች ጋር ኖረው ብቻቸውን ለሚሞቱት ድፍረት ለመሆን ይህ እንዲሆንበት ፈቀደ ። እንጀራ አበርክቶ ሲያበላ አምስት ሺህ ሰዎች ነበሩ ፣ ራሱን ለዓለም ሲሠዋ ግን ዮሐንስና እመቤታችን ብቻ ነበሩ ። ለሰላማዊ ሰልፍ ስሜት እንጂ እውነት አያስፈልግም ። እውነቱ ያለው ሰልፉን የሚመሩት ጋ ነው ። ለሚጮኽለት ሰዎች ይጮኻሉ ፣ የተከበበን ሰዎች ከበው ይዘፍኑለታል ። ብቸኛ የሚባለው ግን በሰው ጠኔ ይሞታል ። ለእንጀራ አቤት የሚለው ዓለም ለሕይወት ዲዳ ይሆናል ።
በመከራ ሰዓት ሁለት ወዳጆች ፣ በቀብራችን ሰዓት ሁለት ቀባሪዎች ካገኘን ጌታን መሰልን ማለት ነው ። በመከራ ሰዓት የሚገኙ ሁለት ወዳጆች ከሺህ ወረተኞች ይበልጣሉ ፤ በቀብር ሰዓት የሚገኙ ደቀ መዛሙርቶች ከሚሊዮን ደጋፊ ይልቃሉ ። ከሕይወት አልፈን የቀብራችን ሥነ ሥርዓት ያስጨንቀናል ። በትክክል ያልኖረ ሰው በትክክል ስለ መቀበር ያስባል ። ሥራውን ያልጨረሰ ሞትን ይፈራል ፣ እያጉረመረመም ይህችን ዓለም ይለቃል ። የምንሞተው ሞትን ስለምንወደው ሳይሆን ሞት ስለሚወደን ነው ። የማይቀበር ሥራ መሥራት ግን ከመኖር ይበልጣል ። ሥራውን የጨረሰ በሰላም በአልጋው ላይ ያርፋል ። ሲኦል ማለት ያልጨረስናቸው መልካም ነገሮች ከፊታችን ላይ ሲደቀኑ የሚሰማን ስቃይ ነው ። ሰው ማለት ከሞት ባሻገር ስላለው ሕይወት የሚያስብ እንጂ በቀብሩ ላይ ስለሚኖረው ሥነ ሥርዓት የሚናዘዝ ፣ ባላየውም የሕዝብ ጎርፍ ይገኝልኝ የሚል አይደለም ። ብዙ ሰዎች የሚኖሩት ለቀብራቸው ነው ። ለቀብራችን መኖር ስንጀምር ለእውነት መሞት እናቆማለን ።
በእኩለ ቀን ደቀ መዛሙርት ሲበተኑ ፣ በእኩለ ሌሊት ቅዱሳን ሴቶች ደፈሩ ። ወንዶች በቀን ፈሩ ፣ ሴቶች በሌሊት ደፈሩ ። ያልተለመዱ ነገሮች በመስቀሉ ዙሪያ ይሆናሉ ። መስቀሉ ሰው ልኩ የሚመዘንበት መለኮታዊ መለኪያ ነው ። ሞት ለሦስት ቀን ነው ። ለሦስት ቀንም የሞተው በፈቃዱ እንጂ ገዳዮች መግደል ስለ ቻሉ አይደለም ። መከራችንም ለአጭር ጊዜ ነው ፣ ይህ ሁሉ የሚሆነው ጠላት ስለ ቻለ ሳይሆን በዚህ ውስጥ አልፈን የምንማረው ነገር ስላለ ነው ። አንዳንዴም እግዚአብሔር እኛን አስችሎ ሌሎችን ያስተምራል ። ትንሣኤ ግን ለዘላለም ነው ። ለሚያልፍ ቀን ይሁዳ ሠያጤ እግዚእ/ጌታን ሻጭ ሆነ ። ጴጥሮስ ፈሪዋን ፈርቶ ካደ ። ደቀ መዛሙርት ያለ አባራሪ ሸሹ ። የዛሬው መዋረድ ፣ የዛሬው ሰው አልባ መሆን ፣ የዛሬው የስድብ መለማመጃ መሆን ፣ የዛሬው አለመደመጥ ፣ የዛሬው መገፋት ፣ የዛሬው ስሜት እንደሌለው ሰው በጦር መወጋት ፣ የዛሬው ተሰናባች መብዛት ያበቃል ። እግዚአብሔር ቀኝ ኋላ ዙር ሲል የመጨረሻው የመጀመሪያ ይሆናል ። ዮሴፍን የሸጡት ዮሴፍን እህል ሊለምኑ መጡ ። እነርሱ ያኔ መሸጥ ይችላሉ ፣ እርሱ ዛሬ ፈርዶ መግደል ይችላል ። የምንገፋቸው በበለጠ ኃይል ይጠብቁናል ። ዮሴፍ የሚችለውን ክፉ አላደረገም ፣ ዮሴፍ መብቱንም አላስከበረም ። የሚችሉት ሁሉ አይደረግም ። የሚችሉት መልካም ነገር ሁሉ አይቀርም ። ዛሬ ገሸሽ ያልናቸው ፣ በማጣታቸው ንግግራቸው እሬት የሆነብን ፣ በሐሰት መስክረን ያስፈረድንባቸው ፣ በብቸኝነታቸው አጥራቸውን ያፈረስንባቸው ፣ ስማቸውን ሽረን ሥራቸውን የቀማናቸው ታላቅ ይሆናሉ ፤ እኛም እንደ ዮሴፍ ወንድሞች እግራቸው ሥር ዝቅ እንላለን ። ዮሴፍ ተለውጦ ስለነበር ወንድሞቹ አላወቁትም ፣ እርሱ ግን አወቃቸው ። በክፉዎች ሰፈር ለውጥ የለም ፣ ደጎች ግን ይለወጣሉና የቀድሞ መልካቸው ይሰወራል ። መግደላዊት ማርያም በዚያች ሌሊት ስትገሰግስ የእግዚአብሔር እንጂ የጊዜ ሎሌ ስላልነበረች ነው ።
የኢየሩሳሌም ቆነጃጅት ደረታቸውን እየደቁ ያለቀሱለት መስቀል ተሸካሚው የምድርን መሠረት እያናጋ ተነሣ ። እናቱ ትንሣኤውን እያወቀች ያለቀሰችለት እርሱ የብዙዎችን እንባ ሊጠርግ ተነሣ ። ጭፍሮች ከበው የደበደቡት የኃይሉን ምስጋና ከመላእክት ተቀበለ ። ርኩስ ምራቅ የተተፋበት ዛሬ በግርማው ሲነሣ የታጠቁና የሰለጠኑ ወታደሮች ባፍጢማቸው ተደፉ ። እግዚአብሔር ሲነሣ እንኳን ለክንዱ ለጣቱ የሚሆን አቅም የለንም ። ልብሱን ገፍፈው የተዘባበቱበት የማይወልቅ የብርሃን ልብስ ለበሰ ። ስምዖን የቀሬናው መስቀል ያገዘው መከራችንን ሊያቀል በጎልጎታ ተነሣ ። ተራራ የተጫነውን ማንም አያወጣውም ፣ ሞትና መቃብር ከተራራ በላይ ናቸው ። የሞትን ተራራ በትንሣኤው አንከባለለ ። እስከ ዛሬ በትምህርቱ ረቡኒ ፣ በተአምራቱ ድንቅ አድራጊ ይባል የነበረው አሁን በትንሣኤው የኃያላን ኃያል ተባለ ። ኃያላን ሁሉ ኃያል የተባሉት ራሳቸውን ከሞት አድነው ሳይሆን ገድለው ነው ። እርሱ ሞትን እንደ ባለጌ የገሠጸ ኃያል ነው ። ማታ የተኛ ጠዋት እንገናኝ እንደሚል ሞትን እንደ እንቅልፍ ቆጥሮ በገሊላ እቀድማችኋለሁ ያለ ነው ። ከሞት በኋላ ቀጠሮ የሰጠ እርሱ ብቻ ነው ።
አልዓዛር ቢነሣ በክርስቶስ ሥልጣን ተነሣ ፣ ክርስቶስ ግን በራሱ ሥልጣን ተነሣ ። አልዓዛር ቢነሣ በአሮጌው ሥጋ ተነሣ ፣ ክርስቶስ ግን በአዲሱ የትንሣኤ አካል ተነሣ ። በዚህም የትንሣኤ በኩር ተባለ ። ዛሬ በንስሐ ትንሣኤ ልቡናን ፣ በምጽአት ትንሣኤ ሥጋን የሚሰጠን እርሱ ተነሣ ። የመቃብሩ ጠባቂዎች በእምነት ትንሣኤውን ባያወሩም በድንጋጤ ስካር ግን መሰከሩ ። በዚያች ሌሊት ከተማውን የሞላው ዜና መግደላዊት ማርያም ጋ አልደረሰም ነበር ። በታላቅ ኀዘን ውስጥ ያሉ የእግዚአብሔርን መነሣት አይሰሙም ። የድንጋጤው ስካር ወታደሮችን ጊዜያዊ ሰባኪ አደረጋቸው ። በርግጥ ሞቷል ተብሎ በሕግ አስፈጻሚዎች ተረጋገጠ ፣ አሁንም ትንሣኤው በሕግ ተረጋገጠ ።
የካህናት አለቆቹም የወታደሮቹን ስብከት በሰሙ ጊዜ ደንግጠው፡- “እኛ ተኝተን ሳለን ደቀ መዛሙርቱ በሌሊት መጥተው ሰረቁት በሉ” አሏቸው ። ከተኙ ሊያውቁ አይችሉም ። እንዲጠብቅ የተመደበ ወታደር ቢተኛ ፍርዱ ሞት ነው ። ደቀ መዛሙርቱ ይህ አቅም ካላቸው ዓርብ ዕለት የማስለቀቅ ሙከራ ያደርጉ ነበር ። ወታደሮች ተዘናግተው ደቀ መዛሙርት ከሰረቁ ደግሞ ፍርድ ቤት መቅረብ አለባቸው ። የካህናት አለቆች ማግባቢያ አደረጉ ። ለምን ተኛችሁ ካለ ገዥው እኛ እናስረዳዋለን አሉ ። ጲላጦስ ግን ወታደሮቹን ጠርቶ ነገሩን ተረዳ ። ክርስቶስ መነሣቱን አመነ ። የመሰከሩለት ወታደሮች ግን ገንዘብ ተቀብለው ተሰረቀ እያሉ ማውራቱን ቀጠሉ ። የሰበከው ካደ ፣ የተሰበከው አመነ ። ጲላጦስም ልቡ ኀዘነተኛ ነበር ፣ አምኖበት ሳይሆን ሰው ላለማጣት ክርስቶስን ሰቅሎት ነበር ። ለገደለው ጌታ ሰማዕት ሆነ ።
የካህናት አለቆች ዛሬም በክፋታቸው ተስፋ አልቆረጡም ። ሰው ለፍቅር እንዲህ በማይታመንበት ዓለም ለቅናታቸው ታማኝ ሆኑ ። ገንዘብ ሲናገር ፍትሕ ጸጥ ይላል እንደሚባለው ወታደሮቹም ትንሣኤውን ለማሳበል በገንዘብ ኃይል መለፍለፍ ጀመሩ ። ሰይጣን ወታደር አስቆመ ፣… ብዙ ነገር አደረገ ። የተሳካላት ግን በገንዘብ የገዛቸው የሐሰት ምስክሮች ነበሩ ። ዛሬም በብዙ ነገር እጅ ያልሰጡ በገንዘብ እጅ የሰጡ ብዙዎች ናቸው ። ክርስቶስ ተነሥቷል የገንዘብ ሎሌ መሆን አይገባም ።
የትንሣኤ ጌታ ወደ ኋላ የሚጎትተኝን የዚህን ዓለም ማሰሪያ ቍረጥልኝ ።
ይቀጥላል
የመስቀሉ ገጽ 8ሐ
ሚያዝያ 22 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን