መግቢያ » ከመጻሕፍት » ረቡኒ » ረቡኒ / 7

የትምህርቱ ርዕስ | ረቡኒ / 7

 መግደላዊት ማርያም ሙሉ ፍቅር ነበራት ። ለዚህም ሽቱ ይዛ ወደ መቃብሩ ወርዳለች ። ሙሉ እምነት ግን አልነበራትም ። ለሙታን የሚሆን ሽቱ ይዛ ሂዳለችና ። በሰማይ  ያለውን ልዕልናውን የሚያውቁ ቅዱሳን መላእክት ሰው በመሆንና በሰው እጅ መከራ በመቀበል ያሳየውን ትሕትና ባሰቡ ጊዜ ከአእምሮ በላይ ሆኖባቸዋል ። ክርስቶስ በበረት ሲወለድ ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም በማለት ቅዱሳን መላእክት አመሰገኑ ። በምድርማ ለእግዚአብሔር የተለቀቀለት የከብቶች በረት ነበረ ። ልዕልናው በሚታወቅባት አርያም ክብር ይሁንለት ማለታቸው ነው ። እኛ ባናከብረው መላእክቱ ያከብሩታል ፣ መላእክት ባያከብሩት ባሕርዩ ባሕርዩን ያከብረዋል ። እርሱ በነገሥታት ቤተ መንግሥት መወለድ አልፈለገም ፣ እረኞች ሊያዩት መሄድ አይችሉምና ። ነገሥታት ዝቅ ማለትን ይማሩ ዘንድ በበረት ተወለደ ። የምሥራቅ ነገሥታትም በበረት ሰገዱለት ። በትክክል ካለን ትዕቢተኛ አንሆንም ። ትዕቢትን የሚወለደው የሚታበዩበት ነገር ሲያጠራጥር ነው ። ሌሎች የላቸውም እንዳይሉን በትዕቢት ፣ በቍጣና በጩኸት ለመሸፈን የሚደረግ ሙከራ ነው ። ጌታችን ወደ ግብጽ ሲሰደድ መላእክት አልተለዩም ። እንዲራዱ አልፈቀደላቸውም ፣ እርሱ መከራ ለመቀበል ፈቅዷልና ። በገዳመ ቆሮንቶስ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ሲጦምና ሲፈተንም መላእክት በአንክሮ ያዩ ነበር ። በለበሰው ሥጋ ፈታኙን ድል ከነሣልን በኋላ ቀርበው አገለገሉት ። በመስቀል ሲሰቀልም ከአቅማቸው በላይ ሆነ ። ሲነሣም ትንሣኤውን ከሰው አለማመን ጋር እየታገሉ ሰበኩ ።

ትንሣኤ ለሐዋርያው ጴጥሮስ ንስሐ ክብር የሰጠ ነው ። ባለመውደቅ እግዚአብሔርን ብናከብረው ምንኛ መልካም ነበር ። ወድቀን በመነሣት እንድናከብረው እግዚአብሔር ንስሐን አዘጋጀ ። ሰውን ሰው ያደረገው ሥራ ሳይሆን ንስሐ ነው ። ሐዋርያው ጴጥሮስ ለዚህ ምስክር ነው ። እንደ ጴጥሮስ በአፋችን ባንክድም በሥራችን ክደነዋል ። እግዚአብሔር የለም ማለትና እግዚአብሔር እንደ ሌለ መኖር ሁለቱም አንድ ዓይነት ነው ። እየሰበኩን በክርስቶስ የማያምኑ አሉ ። ስብከት የአማርኛ መለማመጃ የሆነባቸው የእምነት ልብ የሌላቸው ብዙ የኢየሱስ የአፍ ወዳጆች አሉ ። አልካድነውም ብለን አንኮራም ።
ጌታችን ከሥቃዩ በላይ የጴጥሮስ የልብ ኀዘን ይሰማው ነበር ። ከመስቀል ጣሩ በላይ የጠላቶቹ መጥፋት ያሳዝነው ነበር ። ጠላቶቹ ይቅርታውን ሳይሰሙ እንዳይሄዱ የመጀመሪያውን የመስቀል ቃል የተናገረው ለእነርሱ ነው ። ቃሉም፡- “አባት ሆይ ፣ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው” የሚል ነው ። አሁንም ትንሣኤውን ለጴጥሮስ አስቀድማችሁ ንገሩልኝ ማለቱ ንስሐው ተቀባይነት ማግኘቱን ለመግለጥ ነው ። የክርስቶስ መነሣት ጴጥሮስን እንደገና ቀና ያደረገ ነው ። ሐዋርያው ጴጥሮስ በዶሮ ተሰብኮ ንስሐ የገባ ፣ በመግደላዊት ማርያም ተሰብኮ ትንሣኤን ያረጋገጠ ነው ። ልቡ ቅርብ ነውና እግዚአብሔር ተቀብሎታል ። አንዳንድ ልቦች የመንፈቅ መንገድ ብንጓዝም አንደርስባቸውም ። በልባችን ያሳዘነውን ያህል በእጃችን አንክሰውም ። ክፉ ልብ በእግዚአብሔር የተጠላ ነው ። እኛ ስንቀየም የተቀየምነውን ሰው ስሙን አንጠራም ። የጴጥሮስ ስም መጠቀሱ ግን ዛሬም እንደሚወደው ማረጋገጫ ነው ። ጴጥሮስ የሚለውን ስም መላእክትም ያውቁት ነበር ። ቅድሚያ ለተነሣሕያን/ለንስሐ ገቢዎች ነው ። በዚህም ጴጥሮስ ይቅር እንደ ተባለ አወቀ ።
መላእክት መሄጃ አጥተው በሰማይ የቀሩ አይደሉም ። ነጻ ፈቃድ ያላቸው ሲሆኑ ሥላሴን መርጠው በክብሩ የተጠለሉ ናቸው ። ከወገናቸው አንደኛው ነገድ ክዶ ሰይጣን ሁኗል ። አዳምም ነጻ ፈቃዱን ተጠቅሞ ቅጠል በልቷል ። እነዚህ መላእክት ግን አንድ ቀን ያላስቀየሙት ወዳጆቹ ናቸው ። እነርሱን በዱር ትቶ የጠፋነውን ፍለጋ የመጣ አምላክ ስሙ ይባረክ ። እኛን የፈለገን የወዳጅ ረሀብ ኖሮበት አይደለም ። ከቍጥር ውጭ የሆኑ ብዙ መላእክት አሉት ። ዕለት ዕለት የመላእክት ወዳጅነት ሊታሰበን ይገባል ። በቀንና በሌሊት እኛን የሚጠብቁን መላእክት አሉና ። እነዚህ መላእክት ለሴራ እየሄድን እያዘኑም ቢሆን ስለ እግዚአብሔር ብለው ይጠብቁናል ። ስለ ወዳጅ እሬት ይላሳልና ። መላእክት ወዳጆቻችን ናቸው ። የእግዚአብሔር ፈቃድ ሙሉ የሆነው በሰማይ ወይም በማኅበረ መላእክት ነው ። ጌታችን ትንሣኤውን በመላእክት አስነገረ ። እጅግ ኃያላን የሆኑ መላእክትና ዓለም ያደከማት መግደላዊት ማርያም ትንሣኤውን ይናገራሉ ። ጌታ ደግሞ በጊዜው ይገለጣል ። መላእክት ፣ መግደላዊት ማርያም ጌታን የሚያብራሩ እንጂ የሚሸፍኑ አይደሉም ።
ጌታችን እስከ ሆሳዕና አገልግሎቱ በገሊላ አውራጃ ነበር ። የመጨረሻ ሳምንት አገልግሎቱ ግን በኢየሩሳሌም ሆነ ። በገሊላ እቀድማችኋለሁ አላቸው ። የሞተው ጌታ ያልሞቱትን እቀድማችኋለሁ አለ ። ማንም አይቀድመውምና ። እርሱን የሚቀድም ሯጭ ፣ እርሱን የሚያስከትልም ፊታውራሪ የለም ። ገሊላ መታየቱ ገሊላ ደስ እንዲላት ፣ ትንሣኤው እርግጥ መሆኑን ለማሳየት ፣ እስከ ገሊላ ድረስ በመታየት ኢየሩሳሌም እንደማትይዘው ለመግለጥ ነው ። በገሊላ እቀድማችኋለሁ በማለት የተናገረው ወደ አባቴም ዐርጋለሁ አለ ።
ልብ በኀዘን ሲሞላ የምሥራችን መስማት ፣ ዓይን በእንባ ሲሸፈን የቆመውን ጌታ ማየት ይቸገራል ። ደቀ መዛሙርቱ በኀዘነተኛ ልብ የምሥራቹን መቀበል አቃታቸው ፣ መግደላዊት ማርያምም በእንባ በተሸፈነ ዓይን ጌታን መለየት አቃታት ። ቤተ ክርስያን ስለ ክርስቶስ ሞት በዘመናት አልቅሳለች ። ስለ መሰረቁ ግን አላለቀሰችም ። መሰረቁን ማመን ትንሣኤን አለመቀበል ነውና ። ብዙ ሰዎች ጌታዬን ከልቤ ውስደውታል በማለት በሰዎች ያሳብባሉ ። በዓመፀኛ ሰባክያን ፣ በጨካኝ አገልጋዮች ምክንያት ጌታዬ ከልቤ ተወስዷል የሚሉ አሉ ። በተለያዩ ገጠመኞች እያሳበቡ ፣ ይልቁንም በወንጌል በሚመጣ መከራ እያጠጋጉ ጌታዬን ከልቤ ወስደውታል ይላሉ ። ወስደውታል ክስ ነው ። ጌታ ግን ተነሥቷል ። ማንም እጁን ላይጭንበት ፣ ማንም ላይወስድብን ከፍ ከፍ ብሏል ።
ሰማያውያን መላእክት ድንጋይ ሲፈነቅሉ ፣ ባዶ መቃብር ሲያስጎበኙ ከሰው ጋር ቃል ለቃል ሲነጋገሩ ማስታወስ ይገባናል ። ትንሣኤ ምድራውያንና ሰማያውያን ኅብረት የፈጸሙበት ነው ። ከመቃብሩ ድንጋይ በላይ የሰውን ጥርጣሬ ማንከባለል መላእክትን ከበዳቸው ። ጌታ በፊታቸው ቆሞ ብቻዬን ነኝ የሚሉ ፣ እየተናገራቸው ተስፋ የሚቆርጡ ብዙ ማርያሞች አሉ ። ኀዘን የምናስበውን እንድንሰማ እንጂ እውነቱን እንድንቀበል አያደርገንም ። ኀዘን ዓይንና ጆሮን በመያዝ የታወቀ ነው ።
ለአገልጋዮቹ ስላቃተች ራሱ ጌታ ወደ መግደላዊት ማርያም መጣ ። ባሮቹን ሲገፉ ወራሹ እንደመጣ አሁንም በአትክልት ስፍራ ውስጥ ጌታ ተገለጠ ። ጌታዋን ማንም አልወሰደባትም ፣ አለማመን ግን ወስዶባታል ። ጌታ የተሰረቀው ከልቧ እንጂ ከመቃብሩ አልነበረም ። የቅርቡን ሩቅ ፈለገችው ። ሕያውን ሙት አደረገችው ። ኢየሱስም፦ አንቺ ሴት፥ ስለ ምን ታለቅሻለሽ? ማንንስ ትፈልጊያለሽ? አላት።” /ዮሐ. 20፡15 ።/ ለምን እንደምታለቅስ ያውቃል ፣ የምታለቅሰው ግን ጌታ ተሰረቀ ብላ ነው ፤ እርሱ ግን አልተወሰደምና ልቅሶዋ ትክክል አይደለም ። ብዙ ሰዎች በእንባ ሐሰትን እውነት ለማድረግ ጥረት ያደርጋሉ ። የምትፈልገው አጠገቧ ቆሟል ። ካልተደሰተች የምትፈልገውን አታውቅም ማለት ነው ። ጌታ የአትክልት ጠባቂ መሰላት ። አካባቢው ሊሰጣት የሚችለው ምክንያት ይህ ነው ። ወስደኸው እንደሆነ ንገረኝ ብላ ስታለቅስ፡- “ኢየሱስም፦ ማርያም አላት፡- እርስዋ ዘወር ብላ በዕብራይስጥ፡- ረቡኒ አለችው ፤ ትርጓሜውም፡- መምህር ሆይ ማለት ነው ።”
“ኢየሱስም፦ ገና ወደ አባቴ አላረግሁምና አትንኪኝ ፤ ነገር ግን ወደ ወንድሞቼ ሄደሽ፡- እኔ ወደ አባቴና ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ ዓርጋለሁ ብለሽ ንገሪአቸው አላት ።” ተሰርቋል ሲትይኝ ገና ዐርጋለሁ ፣ በጥርጣሬ ልብሽ ሕያውን ሙት እያልሽ አትንኪኝ እያላት ነው ። መነካትን የከለከለው መሰናበት አሁን እንዳልሆነ ሊነግራት ፣ እንዳይሄድባት ልትይዘው ስትል ተይ ሊላት ፣ ከሁሉ በላይ ባለማመኗ ሊገሥጻት ነው ።
ረቡኒ አለችው ። አንተ ፈራጅ ብትሆንም አትፈርድብንም ገና ታስተምረናለህ ። ገድለንህ በሦስተኛውም ቀን ትወደናለህ ። አንተ የነፍስ ረቡኒ ፣ የአገር መምህር ፣ የትውልድ አቅኚ ነህ ። ረቡኒ እኛን ማሳመን የማይደክምህ ፣ በተራራ በሸለቆ የማትለየን ፣ ሁሉን ለትምህርታችን የምታደርግልን ነህ ። ረቡኒ መባል ካንተ ለተማረች ፣ ፍቅርን ለቀመሰች ነፍስ ተገቢዋ ነው ። ረቡኒ የአሳብ ምርኮኛውን የምታነጻ ፣ ካለማመኑ ጋር የተወዳጀውን የምትገሥጽ ፣ ሰባራውን የምትጠግን ረቢኒ አንተ ነህ ፣ የሕይወት መምህር።
የሆንከውና የሆንነው ፣ የምትፈልገውና የምናቀርበው ቢለያይም ፣ እየተናገርከን ተስፋ ብንቆርጥ ፣ እያየንህ ባናይህም ፣ ብርሃን ለብሰህ ሳለ አትክልት ጠባቂ ብናደርግህም አንተ ግን ሳትቀየም አንተን ወደ ማመን አድርሰን ። ዓለም ከማታሞጋግሰን አንተ ገሥጸን ። አትንኩኝ በለንና በልባችን እደር ። ለእጃችን ከልክለኸን ሥጋና ደምህን ለመብላት አብቃን ። በዙሪያችን ማማተር ትተን በልባችን እንድንሸከምህ እርዳን ። በማይሰለቸው መምህርነትህ ለዘላለሙ አሜን ።
ረቡኒ ተፈጸመ
የመስቀሉ ገጽ  8 ሰ
ሚያዝያ 27 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም