መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ሰማያዊ ወግ » ሰማያዊ ወግ / 7

የትምህርቱ ርዕስ | ሰማያዊ ወግ / 7

የምእመን ድምፅ

ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ !

ጌታዬ ሆይ ሰው የዘጋውን አንተ ትከፍታለህ ። አንተ የዘጋኸውንም አንተው ብቻ ትከፍታለህ ። በሰው ችሎታ አትገመገምም ። በኃያላን ጉልበት አትለካም ። ተራራው ለእኛ ተራራ ፣ ላንተ ትቢያ ነው ። የአሕዛብ ቍጥር ለእኛ እልፍ ፣ ላንተ እፍኝ ነው ። ሰማይ ከፍ ያለ ነው ፣ የሰማዩ ሰማይ ግን አንተ ነህ ። ሰማይን ለማየት ቀና እንላለን ፣ የሰማዩን ሰማይ አንተን ለማየት ግን ዝቅ እንላለን ። ለፍጥረታት እንኳ መግለጫ ተስኖን የአሳብ ልኬቶችና ግምቶች እንሰጣለን ። ፈጣሪው አንተ ግን በምንም አትለካም ። ትንኝ ስለ እኔ አድናቆትን ብታሰማ አይገርመኝም ። እታዘባታለሁ እንጂ ደግሜም አላወራውም ። እኔ ደቃቃ ፍጥረትህ ያንተን ደግነት ፣ ዘላለማዊ ውበት መግለጥ እንደምን ይቻለኛል ! አንተ ግን ከብዙ ምሬት ውስጥ የሚወጣውን ምስጋናዬን አብዝተህ ትቀበለዋለህ ። ርግማን ከበዛበት አፌ የሚወጣውን ልመናዬንም በአፈ ቅዱሳን ትቀበለዋለህ ። ስትወደኝ አንድ ቀን እንኳ እንዳልበደለህ ሰው አድርገህ ነው ። አቤቱ ሆይ! ወደ ልዕልናህ ከፍ አድርገኝ ። ከኋላ እንዳልቀር በፍቅርህ ገመድ ሳበኝ ። የጠላቶቼ ግፊት ወዳንተ አቀረበኝ ፣ የራሴ አለመርካት ግን ካንተ እንዳያርቀኝ እባክህ አማኑኤል ሆይ እርዳኝ !

ጻድቅ ዳኛዬ ሆይ !

የጣለው በረዶ መውጫ ሲያሳጣ ፣ ድፍሮ የረገጠውን አንሥቶ ሲጥል ፤ የወረደው ዶፍ ጣራውን ሲነድል ፣ የዘመናትን ሀብት ጠራርጎ ሲወስድ ፣ ከአንተ በቀር በትከሻው የሚያሳፍር ፣ ሞገደኛ ቀንን የሚያሳልፍ ማንም የለም ። አቤቱ እባክህን በመስማትህ የልቤን ድለቃ ፣ በመናገርህ የነፍሴን ንውጽውጽታ አጽና ። የወገን ዕርቃን አደባባይ ሲወጣ ፣ ገፋፊ እንጂ አልባሽ ሲታጣ፤ በነጠላ ላይ ጋቢ ፣ በጋቢ ላይ ካባ ይደርቡ የነበሩት እነዚያ ደጋጎች ናፈቁኝ ። እኔ ነኝ የበደልሁት ብለው የወንድማቸውን በደል የሚሸከሙት ንጹሐን ውል አሉኝ ። የሰውን ድካም እንደ ተሸከምከው ፣ ክርስቶስ በምድር የሚያሰኙህ ቅዱሳንን አብዛልን ። እንደ ጲላጦስ እጁን ታጥቦ ከሚገድል ሸንጋይ አድነን ። ሲታይ የሚያምረው ቁመናችን ፣ አንተ ስታየው ተበልቶ ካለቀ በእውነት ከንቱ ነን ። ተሸፋፍኖ ከመቃጠል ፣ ተከናንቦ ከመጥፋት አድነን ። አገርም እንደ ሰው ይታመማልና ምድራችንን ፈውስ !

ክርስቶስ መለሰ፡-

ልጄ ሆይ !

ሰውን ወደ እኔ የሚያቀርብ ጠፍቶ የሚያርቅ በበዛበት ዘመን ፣ ያላመነውን ከማሳመን ያመነውን ለማስካድ የሚተጉ በፋነኑበት ወራት አንተ ግን የልቤን ፈለግ ተከተል ። ጥያቄዎችህን አታምልካቸው ፣ መልሶችህን አመስግንባቸው ። እግዚአብሔር በምድር ተገልጦአል ፣ ይኸውም ሰው ሆኜ አንተን መምሰሌ ነው ። ገነት በምድር ግን አትገለጥም ። እውነትን ለመቀበል ልብህን ጨካኝ አድርግ ። በመቀበል ከግማሽ በላይ እፎይታ ታገኛለህ ። ዳዊት በበገና ጭንቀትን ያክም ነበረ ። አንተም ማዜምና የዜማ ዕቃ መጫወትን ስትወድ ከስቃይ ስሜት ትወጣለህ ። የራቀውን አቅርቤ እሰጥሃለሁ እንጂ ላንተ ፍላጎት የምፈጥረው አዲስ ነገር የለም ። መልስህ ሩቅ አይደለም ።

ልጄ ሆይ !

እኔ ስላንተ ታምቻለሁ ። የቀራጭና የኀጥእ ወዳጅ ተብያለሁ ። አንተም ስለ እኔ መታማትን አትፍራ ። ስምህን ሲያጠፉህ ደስ ይበልህ ። በምድር ስምህ ካልጠፋ በሰማይ አይጻፍም ። ሁለት መታወቂያ የያዘ ወንጀለኛ እንደሆነ እወቅ ። ሰውን ባየህ ጊዜ ከእኔ ደም ጋር አብረህ እየው ። ያን ጊዜ ከድካሙ ይልቅ ፍቅርን ትሰጠዋለህ ። የማይቻሉ ነገሮች የሚቻሉት ፣ የሚቻሉ ነገሮች ሲሠሩ ነውና የምትችለውን ዛሬ ከውን ። ሥራህን ሁሉ ስትሠራ ጌታዬን ያስደስተዋል ወይ ? ብለህ ሥራ ። ያን ጊዜ የእኔ ደስታ ኃይልህ ይሆናል ። ትልቅ ለመሆን አትጣር ፣ ትልቅ ሁነህ እንደ ተፈጠርህ እመን ። አንተ የውበት መደምደሚያዬ ፣ የፍጥረት ጉልላቴ ነህ ። በምሠራበት ቀን አስብሃለሁ ። በበረከት ዋል ። የምወድህ ክርስቶስ ወልደ እግዚአብሔር ።

ሰማያዊ ወግ / 7

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 13 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም