መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ሲመሽ ይመጣል

የትምህርቱ ርዕስ | ሲመሽ ይመጣል

ዮሐንስ የተወለደው የዘካርያስና የኤልሳቤጥ ጸሎት መልስ ሆኖ ነው ። አንዳንድ ሰው ለሌላው ጥያቄ ፣ ሌላ ሰው ደግሞ ለሌላው መልስ ይሆናል ። ስንፈጠር ግን ለሌሎች ጥያቄ መልስ ሆነን ተፈጥረናል ። እኛ የሥላሴ ዕቅድ ፣ እኛ የጸሎት መልስ ነን ። በዋጋ ተፈጥረን ያለ ዋጋ መኖርን ማራቅ አለብን ። ዮሐንስ እንደ ተወለደ ወላጆቹ በሕይወት አልቆዩም ። እግዚአብሔር ወደዚህ ዓለም ያመጣን ወላጆቻችንን ተማምኖ ሳይሆን የእርሱን የሚያኖር ክንድ ተማምኖ ነው ። በበረሃም በከተማም መመገብ እርሱ ይችላል ። እስራኤልን አርባ ዓመት በበረሃ የመገበ ፣ ዮሐንስን ሠላሳ ዓመት በበረሃ መገበው ። እርሱ በዘመናት ሥራውን የማይዘነጋ ፣ በራሱ መላ የሚያኖር ነው ። መኖር ምሥጢር ነው ። በማይዘራበት ምድረ በዳ የበሰለ ምግብ ፣ ወጪ በበዛበት ቤት ያለ ገቢ ያኖራል ። ከባለጠጎች ይልቅ ድሆችና ካህናተ እግዚአብሔር በተአምራት እንዴት እንደሚያኖር ያውቁታል ።

የእግዚአብሔርን እጁን ያዩ በክፉ ቀን አይሰጉም ። ትላንትን በጉልበቱ እንደ ኖረ ዛሬን ለመኖር ክብደታቸውን አይመዝኑም ። መኖር በእግዚአብሔር እጅ እንጂ በኪስ አይደለም ። ሄሮድስ በላዔ ሕፃናት ነበር ። የተወለደን የሚያንቅ ፣ የሩቁን እያየ የሚነጥቅ ነበር ። ራስ ወዳድነት ከተወለደ ሕፃን ጋር ያጣላል ። ያልበደሉንን እንድንበድል ፣ ሥጋ የለበሱ መላእክትን እንድንጠላ ያደርገናል ። ጥላቻ ስለበቀለብን ነው ወይስ ሰዎቹ ስለሚጠሉ ነው የጠላናቸው ? ብለን ራሳችንን መጠየቅ አለብን ።

ሄሮድስ እንዳይገድለው ሊያተርፉት ዘካርያስና ኤልሳቤጥ ወደ በረሃ ይዘውት ሄዱ ። በአገራችን ሕፃናት ሳይቀር ያለቁበት ጥቁር ታሪኮች አሉን ። ልጄ ባደገልኝ ሳይሆን ልጄ አደገብኝ ብለው የሚፈሩ እናቶችን አይተናል ። በላዔ ሕፃናት የሆኑ ጨካኝ ገዥዎችን አስተናግደናል ። ገዳይም ሟችም ኢትዮጵያዊ የሆነው ታሪክ የሚያኮራ አይደለም ። ወንድማማች ተጋድለው በመጨረሻ የሚነገር ድል የለም ። ዮሐንስ በእግዚአብሔር ጥበቃ አደገ ። ለእርሱ መሞት የሰጉት ወላጆቹ ሞቱ ። እርሱ ግን አደገ ።

እስቲ አንተ ታውቃለህ የምንከርምበቱን፣
ሰው ኑሮውን እንጂ አያስብም ሞቱን ።

ዘካርያስና ኤልሳቤጥ ልጅን ለእግዚአብሔር ዓላማ ወለዱ ። አስቀድሞ መጥቶ ቢሆን ይጦረናል ፣ ይቀብረናል ብለው ተስፋ ሊያደርጉ ፣ እንደ አብርሃም በልጅ ትምክሕት ሊወድቁ ይችላሉ ። “ልጅህን ሠዋልኝ” ሳይባሉ በሰላም አለፉ ፣ ዐረፉ ። ከነሃይማኖቱ የሞተ ክቡር ነው ። ዮሐንስ ለምን ተወለደ ? ካልን ለወላጆቹ እግዚአብሔር ከሀሊነቱን ሊያሳያቸው ፣ ጸሎታቸው ያኔ መሰማቱን ሊገልጥላቸው ነው ። ዛሬ በምሽት ያገኙት መልስ ገና በተጋቡ ቀን የጸለዩት ልመና መልስ ነው ። የዘመናት ርዝማኔ ጸሎታችንን የማያስረሳው አምላክ ነው ። የሚጦርም የሚቀብርም እግዚአብሔር ነው ። በእግዚአብሔር ሰፊውን ዘመን ኖሮ ለጡረታና ለቀብር መጨነቅ ከንቱ ነው ። ጉልበት በነበረን ጊዜም የኖርነው በራሳችን ሳይሆን በእግዚአብሔር ነው ። ያለ እግዚአብሔር የዘራ ፣ የዘራውን ያገኘ ፣ የጎረሰ ፣ የጎረሰውን የዋጠ ፣ የበላው የተስማማው ማንም የለም ። ሁሉ በአንተ ነው ….።

ዘካርያስና ኤልሳቤጥ በእግዚአብሔር ያላቸውን ትምክሕት ልጅ አልወሰደባቸውም ። ከልጅ በፊት የሚያውቁትን እግዚአብሔር በልጅ አልለወጡትም ። ልጆች ቢኖረንም ባይኖረንም ፈቃዱ የእርሱ ነው ። ተሰጥተውንም በሞት ሊወሰዱ ይችላሉ ። የሰጠው ከወሰደ ፣ እኛ ባለ አደራዎች እንጂ ባለ መብቶች አይደለንም ። ያስቀመጠውን ንብረት ለምን ወሰደ ? ተብሎ አደራ ሰጪ አይከሰስም ። ከአብርሃምና ከሣራ ጋር የሚመሳሰል ታሪክ በዘካርያስ ቤት ተፈጽሟል ። ጨለማ በእግዚአብሔር ዘንድ እንደማይጨልም ፣ ምሽት እግዚአብሔርን ማየት እንደማይከለክል እናስተውላለን ። እርሱ እንኳ በእርጅናችን በሞታችንም ላይ መሥራት የሚችል ነው ። ከጊዜ ውጭ ነውና የጊዜ ህልፈት አያሰጋውም ። እግዚአብሔርን ስጠኝ በሉት እንጂ ሰዓቱ መርፈዱን አትንገሩት ። ገና በሰማይ ይጋብዘናል እያልን በመሸ ቀን አንጠራጠረውም ። ደግሞም ምሽት ያለው ሕሊና ውስጥ ነው ። “እግዚአብሔር ብርሃኔ ነው” ለሚሉ ምሽት ስጋታቸው አይደለም ። ካልመሸ የእግዚአብሔርን ብርሃንነት አናይምና እንኳን መሸ ። አዳምና ሔዋን በገነት መሸባቸው ፣ በቤተ መንግሥቱ የአትክልት ስፍራ የተደበቀ የመጀመሪያው ንጉሥ አዳም ነው ። ሲመሽ ግን መድኃኔ ዓለም መጣ ። ሲመሽ ይመጣል ፣ ደስ ይበላችሁ !

ገሎ ማሥነሣት ታውቃለህ ፣
ወልድ አብነት አለህ ፤
የሴት ልጅ ነኝ ብለህ ፣
ወልድ በራስህ ተኮራህ ፤
አብ አይበልጥም ወይ አባትህ ?
ተለማኝቱ እናትህ ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 26 ቀን 2016 ዓ. ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም