የትምህርቱ ርዕስ | ሳልሄድ

“ወደማልመለስበት ሳልሄድ ዐረፍ ዘንድ ተወኝ” መዝ. 38፡13 ።

ስወለድ ለራሴ አልቅሼአለሁ ፣ ስሞት ደግሞ ሰዎች ለእኔ ያለቅሳሉ ። በልቅሶ የጀመርኩትን ዓለም በልቅሶ እጨርሳለሁ ። ስወለድ በደመ ነፍስ ፣ ዓለም ክፉ መሆኑን አውቄ ለራሴ አለቀስኩ ፣ ስሞት ዓለም የቀረብኝ መስሎአቸው ሰዎች ባለማወቅ ያለቅሳሉ ። የሕፃንነቴ እውቀት ፣ የአዋቂዎችን ማስተዋል በለጠ ። እንባ ማጠራቀሚያ ቢኖረው እስከ ዛሬ የፈሰሰው የዘረ አዳም ልቅሶ ውቅያኖስ በሆነ ነበር ። ጌታ ሆይ ! ያልከፋውና ያላዘነ ማነው ? ካንተ በቀርስ እንባን የሚያብስ ፣ የራቀውን ደስታ የሚያቀርብ ማነው ? አሳባችን አሳባችን ላይ ያስለቅሰናል ። “እንዴት እኔ ይህን አስባለሁ?” የሚለው ሙግት ያናውጠናል ። የማይታየውን ልባችንን እያየህ ሳትገልጠን ታልፈናለህ ። ልባችን ላይ የሌለውን ደግነት በአፋችን ስናንጸባርቅ ትገረማለህ ። ልባችን ላይ ክፋት ሳይኖር በአፋችን ስናበላሸው ታዝንልናለህ ። ደግ እንዳንባል ክፉ ፣ ክፉ እንዳንባል ደግ ሁነን ሚና የለሽነታችን ያሳዝንሃል ።

እውቀት የሌለበት ጉዞአችን ክለሳ እያበዛ ዕድሜአችንን በላብን ። የክፋት ሥራችን መልሶ እኛን እየጎዳን እግራችንን በእሾህ አደማብን ። ብንራመድም የምናነክስ ፣ ብንጎርስም የማንጠግብ ነን ። የተለወጠ ጉዳይ እንጂ ጉዳይ ያልቀረልን ተወዛዋዥ ሬሳ ነን ። ስንቱን ቀረብን ፣ ስንቱን ራቅነው ። ለማይሞላ ኑሮ ስንቱን ሆንነው ። ተመልሰን ወደዚህ ምድር አንመጣም ። ያበላሸነውን ለማረም ፣ የምንወዳቸውን ለማግኘት አንመለስም ። መንገዱ አንድ ነው ። መሄጃ እንጂ መመለሻ የለውም ።
ሞትም የሰው ልጅ ዕጣ ሁኗል ። ያልሞቱት ሄኖክ ኤልያስም ሊሞቱ ይመጣሉ ። አንተ መድኃኔ ዓለምም ሥጋ ለብሰህ ሞተሃል ። እኮ ማን ይቀራል? እባክህን ወደማንመለስበት ሳንሄድ ፣ የሞት ጉዞን ሳንጀምር እናርፍ ዘንድ ተወን ። በማኅፀን እያለን የምንሰማው የጥይት ድምፅ ሸብተንም እንሰማዋለን ። ሰንሰለታማው ችግር ፣ በራስ ወገን ሲገረፉ መኖር ደክሞናል ፤ እባክህ ወደማንመለስበት ሳንሄድ እናርፍ ዘንድ ፍቀድልን ። የዓመት ፈቃድ ሳይሆን የዕድሜ ፈቃድ ስጠንና አሳራፊው ሆይ እባክህ አሳርፈን ! አሜን ጽናትህን ደጅ እንጠናለን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 16 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም