መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ስጦታን ሰጠ

የትምህርቱ ርዕስ | ስጦታን ሰጠ

 
“ስለዚህ፦ ወደ ላይ በወጣ ጊዜ ምርኮን ማረከ ለሰዎችም ስጦታን ሰጠ ይላል ።” ኤፌ. 4 ፡ 8 ። 
 
ጌታችን ወደ ምድር ወረደ ። ከምድር ሳይለይ ወደ ምድር መጣ ። ምድርን ሳይተዋት ወደ ላይ ዐረገ ። ከሰማይ ሥጋን ይዞ አልመጣም ፣ ወደ ሰማይ ሲወጣም በመለኮትነቱ ብቻ አልወጣም ። ሥጋን ይዞ አልመጣም ፣ ሥጋንም ጥሎ አልወጣም ። ወደ ምድር በመምጣቱ አምላክ ሰው ሆነ ። ሥጋም ከመለኮት ጋር ቢዋሐድ ሰው አምላክ ሆነ ። የሰው ርስት የሆነውን በረትን የወረሰ አምላክ ፣ የመለኮት ርስት የሆነውን ዙፋንን ለሥጋ ሰጠ ። ከላይ ወደ ታች ሲወርድ ከሦስትነቱ አልጎደለም ። ወደ ላይ ሰያርግም በሦስትነቱ ላይ አራትነትን አልጨመረም ። ከላይ ሳይጎድል ፣ ከሥር ሳይጨመር አምላክ ሰው ሆነ ። ፈጣሪ ፣ አምላክ ፣ ያህዌ ፣ አዶናይ ፣ ኤልሻዳይ የተባለው  በለበሰው ሥጋ ኢየሱስ ፣ አማኑኤል ፣ ክርስቶስ ፣ የሰው ልጅ ተባለ ። ወደ ላይ ወጣ መባሉ ሥጋ መልበሱን ያሳያል ። መለኮት ወጣ ወረደ የማይባል ሁሉ በሁሉ ነውና ። እርሱ ወደ ላይ ለመውጣት እስከ መቃብር እስከ ሲኦል መውረድ ነበረበት ። ለእኛም ከፍ የማለት ምሥጢሩ እጅግ ዝቅ ማለት መሆኑን አስተማረን ። ከሕመሙ ፈውስን ፣ ከስብራቱ ጠገንን የሚጠብቀው ዓለም ከሞት ትንሣኤን መጠበቅ ተስኖት ነበረ ። ጌታችን ወደ ላይ በማረጉ ግን ከዝቅታው ከፍታው እንደሚበልጥ አበሰረን ። በርግጥም ከተዋረድነው የምንከብረው ፣ ካጣነው የምናገኘው ይበልጣል ። ወደ ላይ ለመውጣት ግን ወደ ታች መውረድ ሕጉ ነው ። ክብርን አስደሳች የሚያደርገው የተዋረዱበት መጠን ነው ። ሕይወት አንድ መልክ ብቻ ቢኖራት ትሰለች ነበር ። ብርሃንና ጨለማ ናት ። ከጨለማው በኋላ ብርሃን ይከተላል ። 
 
ብዙዎች ወደ ላይ ለመውጣት እልፎችን ረግጠዋል ። የቆሙትም በሌሎች ጀርባ ላይ ነው ። ወደ ላይ ከወጡ በኋላም የጨበጡትን መሰላል ይረግጡታል ፣ ሲከፋም ይገፈትሩታል  ። መሰላል በመጀመሪያ በእጅ ይጨብጡታል ። ከፍ ሲሉ በእግር ይረግጡታል ። መጨረሻ ላይ ጥለውት ይሄዳሉ ። የሚያስታውሱት ለመውረድ ሲቃረቡ ነው ። እየጨበጡ ያለፉትን ሕዝብ የረገጡ ፣ ወተት በቧንቧ እናቀርባለን ብለው ደም በቧንቧ ያቀረቡ ብዙ የዓለም መሪዎች ነበሩ ፣ አሉ ። ያከበራቸውን ሕዝብ የረሱ ፣ በብዙኃን ጀርባ ላይ ወጥተው ብዙኃኑን ትተው ከጥቂቶች ጋር የጨፈሩ አያሌ ናቸው ። ለሞት የፈለጉትን ሕዝብ ለማዕድ ያልጋበዙት ፣ ረስተውት ኖረው መጨረሻቸው ሲቃረብ እንደገና ድረስልን ያሉት ብዙ ናቸው ። “ከታሪክ የተማርኩት ሰው ከታሪክ እንደማይማር ነው” ያለው ሰውዬ እውነቱን ነው ። 
 
ምርኮ የጦርነት መጠናቀቅን የሚያበስር ነው ። ምርኮ ከፊቱ ጦርነትና ድል አለው ። ምርኮ ቀጣዩን ዘመን የሚያበሥር ነው ። ምርኮ ተዋጊዎችና ደጀን ሕዝብ ስጦታን የሚከፋፈሉበት ፣ በጠላት እጅ የነበረውን በራሳቸው እጅ አድርገው ባለጠጋ የሚሆኑበት ነው ። ምርኮ በአንድ ዓይን እያለቀሱ በአንድ ዓይን የሚስቁበት ነው ። በአንድ ዓይን ማለቀሳቸው የተከፈለውን መሥዋዕት ብርቱ መሆኑን ፣ በአንድ ዓይን መሳቃቸው ስጦታውና በረከቱ መብዛቱ ነው ። ያለ ጦርነት ግን ድል የለም ። ጦርነቱ በቀራንዮ ፣ ድሉ በጎልጎታ ፣ ምርኮው በደብረ ዘይት ሽቅብ ወደ ላይ ሲያርግ ነው ። በምርኮ ጠላትን አሰልፈው ይነዱታል ። ጠላት የነበሩትን የአዳምን ልጆች በትከሻው ተሸክሞ ባሕረ ሞትን ያሻገረው ፣ ጠላት የሆነውን የአዳምን ባሕርይ ባሕርዩ ያደረገው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለዘላለም ድንቅ ነው ። እርሱ የተዋጋው ከዘላለማዊ ጠላቶቻችን ከሲኦል አበጋዞች ጋር ነው ። ምርኮ ለተዋጉት ወታደሮች ነው ። ጌታችን ግን ብቻውን ስለ እኛ ሞተ ። የሞቱ ፍሬ የሆነውን ጸጋ መንፈስ ቅዱስን የሰጠው ለተዋጉት ሳይሆን ለተማረኩት ለሰው ልጆች ነው ። 
 
የማረከው የሰው ልጆችን ሲሆን ስጦታውም የተሰጠው ለሰው ልጆች ነው ። እነግሥ ብሎ ያልሞተ ፣ እከብር ብሎ ያልተዋጋ አምላክ ቡሩክ ነው ። ጌታችን ስለ እኛ ተዋጋ ፣ አሸነፈ ፣ ምርኮን ማርኮ ሲኦልን በዘበዘ ። ጸጋ መንፈስ ቅዱስንም ሰጠ ። ስጦታንም የሰጠው ለሰዎች ነው ። ይህም ሁለት ፍቺ አለው ። የመጀመሪያው ለሰው ዘር ሁሉ ነው ። በስጦታው አድልኦ የለበትም ። ሁለተኛው ለሰዎች ሰጠ ። ይኸውም በግብራቸው እንስሳት ፣ አራዊትና ውሉደ ዲያብሎስ የሆኑ አሉ ። እርሱ ለሰዎች ስጦታን ሰጠ ። ስጦታን ለመቀበል ሰው መሆን ያሻል ። ጸጋ መንፈስ ቅዱስን ያገኘነው እርሱ በሞተበት ሥጋ ወደ ላይ ሲያርግ ፣ የተቸነከረ እጆቹንና እግሮቹን እያሳየ በዙፋኑ ሲቀመጥ ነው ። በክብር ዙፋኑ ሲቀመጥ ስጦታ በዛ ። የሰው ኃጢአት ወልድን ሰው አደረገው ፣ የወልድ መክበር ጸጋ መንፈስ ቅዱስን አጎረፈው ። ጸጋ መንፈስ ቅዱስ እንዲለቀቅልን ክርስቶስ በልባችን ዙፋን መቀመጥ አለበት ። 
 
ሁልጊዜ መስጠት ልማዱ ነው ። ሙሉ አካልን የሰጠ ፣ ለዓይን ማየትን የፈቀደ ፣ ከእናት ከአባት በፊት አይቶን በማኅፀን የመገበን ፣ የዛሬዋን ብሩህ ቀን ያደለን ፣ በቀራንዮ ነፍሱን የሰጠን አሁን ደግሞ ባረገ ጊዜ ስጦታን ሰጠን ። በዓለ ሃምሳ ይህን ስጦታ የተቀበልንበት ፣ የቤተ ክርስቲያን ልደት የተከበረበት ቀን ነው ። በበዓለ ሃምሳ የወረደው መንፈስ ቅዱስ ዛሬም በቤተ ክርስቲያን አለ ። በቃለ እግዚአብሔር በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ፣ በመምህራን እረኝነት በኩል ዘወትር ይባርከናል ። ለበጉ ሰርግም ያቆነጀናል ። 
 
ወደ ላይ የወጣው ኢየሱስ ይመለሳል ። ምን ይዘን እንቀበለዋለን ? እርሱ ሌላም አይሻም ፣ የሰርግ ልብሳችንን ለብሰን እንጠብቀው ። ሰርግ ልብስ ቢለብሱት ክብሩ ለራስ ነው ። ለራሳችን ብሎ ትእዛዙን የሰጠን ቡሩክ ነው ። 
 
በበረከት ዋሉ !
 
 ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
 ነሐሴ 27 ቀን 2013 ዓ.ም.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም