የትምህርቱ ርዕስ | ቃለ ውግዘት

 “ከእነዚያም ፥ እንዳይሳደቡ ይማሩ ዘንድ ለሰይጣን አሳልፌ የሰጠኋቸው ፥ ሄሜኔዎስና እስክንድሮስ ናቸው ።” 1ጢሞ. 1፡20
በሕይወት ውስጥ ትልቁ ጸሎት፡- “ጌታ ሆይ ስቶ ከማሳት ፣ ጠፍቶ ከማጥፋት አድነኝ” የሚለው ነው ። እግዚአብሔር ባለማወቅ የጠፉትን በድፍረት ከጠፉት ለይቶ ያያል ። ምንጊዜም ላልማ ብለው ያጠፉትን ላጥፋ ብለው ካጠፉት ሰዎች ለይቶ ማየት ይገባል ። ሁሉን በአንድ መነጽር ማየት በዓለም ላይ የዘር ማጥፋት ወንጀልን ያመጣል ። በአንድ ክፉ ወንድ ፣ ወንድ ሁሉ ክፉ ነው አይባልም ። በአንዲት የተሳሳተች ሴትም ፣ ሴት ሁሉ መጥፎ ነው አይባልም ። “ዓሣውን ለማጥፋት ባሕሩን ማድረቅ” የሚለው አስተሳሰብ በጣም ጎጂ ነው ። ጠብን በልኩ ካላደረጉት ጉልበት ይጨርሳል ። በዓለም ላይ የተዋረዱ ነገሥታት የሚባሉት ጠብን የማይንቁ ናቸው ። የሰደባቸውን ሁሉ ፈልገው ፣ ያማቸውን ሁሉ አሳድደው የሚጎዱ ክብር ያጣሉ ። አንዳንዱ የሚሳደበው የመጀመሪያውም የመጨረሻውም አቅሙ እርሱ ስለሆነ ነው ። የሚያማውም ፈሪ ስለሆነ ነው ። ጠብን መናቅ የትልልቅ ሰዎች ክብር ነው ። በዚያው ተቃራኒ ደግሞ ክፉ ነገር ትንሽ ቢሆንም የማይናቅና ሳያድግ መፍትሔ ሊበጅለት የሚገባ ነው ። በጣት የሚነቀለው ችግኝ ካደገ በኋላ ለመጥረቢያም ያስቸግራል ።

ሐዋርያው ጳውሎስ ስማቸውን የጠቀሳቸው ሄሜኔዎስና እስክንድሮስ በስህተታቸው የማያፍሩ ወንጌል ትልቅ ናት በምትለዋ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ወንጌል ትንሽ ናት የሚሉ ፤ ክርስቶስን ወልደ እግዚአብሔር ፣ የባሕርይ አምላክ በምትል ማኅበረ ምእመናን ውስጥ ፍጡር ነው እያሉ የሚያስተምሩ ነበሩ ። ሐዋርያው ቃለ ውግዘት ከማስተላለፉ በፊት እንደመከራቸውና ወደ እውነቱ እንዲመለሱ እንደ ደከመላቸው እንረዳለን ። ውግዘት የመጨረሻ ውሳኔ እንጂ የመጀመሪያ ውሳኔ አይደለምና ።
ሠለስቱ ምእት በኒቅያ ጉባዔ የተሰባሰቡት አርዮስን ለማውገዝ ሳይሆን ለመመለስ ነበር ። አርዮስንም፡- “ይህን ነገር አስበኸው ከሆነ አትናገረው ፣ ተናግረህ ከሆነ አትድገመው” በማለት ምክር ሰጥተውታል ። ቢመለስ ብለውም የማሰቢያ ጊዜ እንዲያገኝ አድርገዋል ። ለአርዮስ ማጥፋት ብቻ ሳይሆን ለራሱ መጥፋትም አዝነዋል ። ሠለስቱ ምእት የማሰቢያ ጊዜ መስጠታቸው ፣ ቆስጠንጢኖስ ላግዘው ባለ ጊዜ አይሆንም ማለታቸው መንፈሳዊነታቸውን ያሳያል ። እነዚህ አባቶች በእውቀት ያደጉ ፣ በመንፈሳዊነት የተገለጡ ፣ በሰማዕትነት ውስጥም ያለፉ ናቸው ። አንዳንዶቹም ስለ ክርስቶስ እጅና እግራቸው ተቆርጦ በሸክም የመጡም ነበሩ ። ስለ አንዱ አርዮስ መጥፋት ያሳዝናቸው ነበር ። አርዮስ ግን ይህን ሁሉ ዕድል አግኝቶ በስህተቱ ስለጸና አውግዘው ከማኅበረ ምእመናን ለይተውታል ። ንስሐ ቢገባ ሊቀበሉት በሩንም ክፍት አድርገውለታል ።
በሃይማኖት ህፀፅ የተገኘባቸውን ሰዎች በርኅራኄ ማከም እንጂ በጭካኔ መግፋት የክርስቶስን ደም ከንቱ ማድረግ ነው ። እርሱ የጠፉትን ለማዳን ሰው ሁኗልና ደግሞም በመስቀል ላይ ውሏልና ። ወንድሜ ይዳን ቀርቶ ይጥፋ የሚል የአረሚ መንፈስ የተቆራኘው ሰው ነው ። እንደ እኔ ካላመንህ ብሎ በሰይፍ የሚቀላ ፣ በድንጋይ የሚያናግር አረሚ ነውና ። ሰዎች ሁሉ አውቀው የጠፉ አይደሉም ፣ የብዙዎች መጥፋት እውቀት ከማጣት የተነሣ ነው ። ይህም በነቢይ ቃል ተነግሯል፡- ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሣ ጠፍቶአል/ሆሴ. 4፡6 / ። የአባቶች ተግባር አስተምሮ ማሳመን እንጂ አውግዞ መለየት አይደለም ። ውግዘት የቤተ ክርስቲያን የመጨረሻ አማራጭ ነው ። “ከሣር ክዳን ቤት አንድ ቢመዘዝ አያፈስም” የሚሉ ወጣቶች ስንቱን ሰው ከቤተ ክርስቲያን ገፍተው አስወጥተውታል ። ባለፉት ሃያ አምስት ዓመታት ቤተ ክርስቲያን ከሃያ ሚሊየን በላይ ምእመን አጥታለች ። ሃያ ሚሊየን ሕዝብ አንድ ሣር ነው ብሎ ማሰብ በጣም የሚገርም አረማዊ መንፈስ ነው ። በስህተት ትምህርት ውስጥ ያለ ሰውን በጣም ታላቅ በሆነ ርኅራኄ መጀመሪያ ለብቻ ማናገር ይገባል ። ከዚያ እንደ ጌታችን ቃል ሁለትና ሦስት ሁነው ሊያናግሩት ይገባል ። ይህን ሁሉ ሂደት አልቀበልም ካለ ለቤተ ክርስቲያን ጉባዔ ወይም ለሲኖዶስ ማቅረብ ይገባል ። ከዚህ በኋላ ውግዘት ይደረጋል ። /ማቴ. 18፡15-17/ ። ዛሬ ግን ውግዘት በፖስታ ይላካል ። ለማስተማር የሰነፉ ለማውገዝ የበረቱ እንዳንባል አምላክ ይጠብቀን ። ሳናስተምር ያወገዝነው እርሱም በመሃይም ቃሉ ያወግዘናል ። ውግዘት አባታዊ ቅጣት እንጂ የጠላት በትር አይደለም ።
ቆስጠንጢኖስ ንጉሣዊ ሥልጣኑን መከታ አድርጎ አርዮስን ወደ ግዞት ልስደደው ባለ ጊዜ አባቶች ከልክለዋል ። ምክንያቱም ማመን አምላክ የሰጠው ነጻነት ነውና ። በመጨረሻ ግን ቆስጠንጢኖስ  በአርዮስ አሳብ ተስቦ ነበር ። ይህ የሚያሳየን መፍረድ ፣ ዘራፍ ማለት ፣ ሰውን በሃይማኖት ስም ልቅጣህ ብሎ መነሣት በመጨረሻ እዚያ ስህተት ላይ ይጥላል ። አትፍረድ ይፈረድብሃል የሚለው ለዚህ ነው ።
ከኖኅ መርከብ ውጭ ያለው ጥፋት ብቻ ነበር ። እንዲሁም ከቤተ ክርስቲያን ውጭ ያለው ጥፋት ነው ። ሐዋርያው ጳውሎስ፡- “ከእነዚያም ፥ እንዳይሳደቡ ይማሩ ዘንድ ለሰይጣን አሳልፌ የሰጠኋቸው ፥ ሄሜኔዎስና እስክንድሮስ ናቸው” ይላል ። ስድብ የተባለው በአምላክና በአምላክ ቃል ላይ ያደረጉት ንቀት ነው ። ለሰይጣን አሳልፎ መስጠትም በውግዘት ከቤተ ክርስቲያን መለየት ነው ። ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ ግዛት ናትና ከቤተ ክርስቲያን የተባረረ ወደ ሰይጣን ግዛት መግባቱ ግድ ነው ። ከኢትዮጵያ የተባረረ የኬንያ ግዛት ውስጥ ይገባል ። ነጻ የሆነ ዓለም የለምና ። አንድ ሰው ከቤተ ክርስቲያን ሲባረር ማኅደረ መንፈስ ቅዱስ መሆኑ ይቀራል ። ስለዚህ ማኅደረ ሰይጣን ሁኗልና ለሰይጣን ተላልፎ ተሰጠ ይባላል ። ከኖኅ መርከብ የወጣ ጥፋት ብቻ እንደሚያገኘው ከክርስቲያን ማኅበር የተለየም ጥፋት ይገጥመዋል ። ትልቁ ቅጣትም በቃሉ አማካይነት የሚገኘውን የመንፈስ ቅዱስ መጽናናትና የወንድሞችን ፍቅር ማጣት ነው ።
ውግዘት በተለያየ መንገድ ሊከናወን ይችላል ። ዳኞች ጉቦ በልተው ፍርድ እንደሚያጣምሙ እንዲሁም ለሰው ያደሩ ሰዎች ሰውን እንደ ቀላል ሊያወግዙ ይችላሉ ። ነገሥታት የጠሉትን የሚያወግዙ ለቤተ መንግሥት ያደሩ መለካውያንም አሉ ። መለካዊ ማለት ሰማያዊውን መንግሥት በምድራዊ መንግሥት የለወጠ ማለት ነው ። እውነተኛ ውግዘት ግን ያስራል ፣ መንፈስ ቅዱስን ያርቃል ። ሂደቱን ያልጠበቀ ውግዘት ግን አውጋዡን ያስራል ።
ሐዋርያው እነዚህን ሰዎች ያወገዘው ከቅጣቱ የተነሣ ተምረው ለንስሐ እንዲበቁና ነፍሳቸው እንድትድን ነው ። /1ቆሮ. 5፡5/ ። በየትኛው ዘመን የቤተ ክርስቲያንን መድረክ የያዙ ሁሉ አማኞች ፣ የተገፉ ሁሉ ሐሰተኞች አይደሉም ። እውነተኛውንና የራሱ የሆኑትን ጌታ ያውቃል ። ዓለም ግን በሐሰተኛ ፍርድ ተሞልቷል ።
ፍርድ በቀል አይደለም ፣ ፍርድ ትምህርት ነው ። ውግዘትም በቀል ሳይሆን ትምህርት ነው ።
ቤዛ ኩሉ ዓለም ክርስቶስ ራሳችንን ለማየት ብርሃኑን ይላክልን ።
1ጢሞቴዎስ /22/
ታኅሣሥ 14 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም