የትምህርቱ ርዕስ | ቃለ ጽድቅ

“እናንተም ደግሞ የእውነትን ቃል ፥ ይኸውም የመዳናችሁን ወንጌል ፥ ሰምታችሁ ደግሞም በክርስቶስ አምናችሁ ፥ በተስፋው መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ ታተማችሁ ፤ እርሱም የርስታችን መያዣ ነው ፥ ለእግዚአብሔር ያለውን ሁሉ እስኪዋጅ ድረስ ፥ ይህም ለክብሩ ምስጋና ይሆናል ።” ኤፌ. 1፡13-14።

የኤፌሶን ሰዎች የእውነትን ቃል ይኸውም የመዳናቸውን ወንጌል ሰምተው በክርስቶስ አምነዋል ። በዋዜማው የደከሙ ሰዎች ብዙ ጊዜ በበዓሉ ድግስ ላይ አይገኙም ። ከልፋቱ እንጂ ከበረከቱ አይታደሙም ። የኤፌሶን ሰዎች ግን ከዋዜማው አልነበሩም ። በመሥዋዕተ ኦሪት አልተለማመኑም ፣ በተስፋ አበው አልጸኑም ፣ በትንቢተ ነቢያት አንጋጠው/አሻግረው አላዩም ፣ በምሳሌ በጥላ አልታመኑም ፣ በሱባዔ አልቆጠሩም ፤ በሌሎች ድካም ግን ገቡ ። በሰኔው አዝመራ ሳይገኙ ፣ በትሣሡ አጨዳ ታደሙ ። እስራኤል ወጥተው እነዚህ መግባታቸው እግዚአብሔር በዓላማው ጨካኝ መሆኑን ያሳያል ። ደግሞም ሁሉን ለእኔ የሚልን ብሉይም ሐዲስም ከእኛ ውጭ ለሌላ አይገባም በሚሉ አይደሰትም ፤ እርሱ የአጽናፈ ዓለም ጌታ ሳለ የአጥቢያ ንጉሥ እንዲያደርጉት ባሕርዩ አይፈቅድም ። ደግሞም እስራኤል እግዚአብሔር ካደረገላቸው እነርሱ ለእግዚአብሔር ያደረጉለት በዝቶ ታይቷቸዋልና አሕዛብን በማየት እንዲሁ ወገን በሚያደርገው ጸጋው እንዲማሩ ለማድረግ ነው ። አሕዛብም እስራኤል እንኳ ወድቀዋልና እኛማ ምን ቦታ አለን ብለው ትሑት እንዲሆኑ ነው ። እግዚአብሔር በአጥፊው ጠፊውን ፣ በጠፊው አጥፊውን ያስተምራል ። አንዱን በትምህርት ፣ አንዱን በፍርድ ያሰለጥናል ።

ያመኑት በእውነት ቃል ፣ በመዳን ወንጌል ፣ በክርስቶስ ነው ። ሁሉም በጠቅላይ ቃል ሲገለጡ በክርስቶስ አምነዋል ። ለማመን ዋዜማው የእውነት ቃል ነው ። ሰው የእውነትን ቃል ሳይሰማ ቢያምንም እምነቱ በድቡሽት መሬት ወይም በአሸዋ ላይ የተመሠረተ ነው ። እግዚአብሔር የሚገለጠው በእግዚአብሔር ቃል ነው ። ስለ እግዚአብሔር ያወቅነው በልቡና ተመርኆ ብቻ ሳይሆን በተገለጠው ቃልም ነው ። የእግዚአብሔር ቃል መገለጥ ከሆነ ከምድር አይደለም ማለታችን ነው ። የመገለጥን ቃል የምንረዳው በመገለጥ ነውና ጸሎትና ትሕትና ትልቁ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ነው ። የእውነትን ቃል የመስማታችን ዓላማው እኛን የአጠቃላይ እውቀት ባለቤት ማድረግ አይደለም ። ፖለቲከኞች የእግዚአብሔርን ቃል ስለ ተናገሩ የእግዚአብሔር ሰዎች ላይሆኑ ይችላሉ ። የእግዚአብሔር ቃል ንግግር ማሳመሪያ ፣ ሰውን መቆጣጠሪያ ሳይሆን ዓላማው ግለሰቡን ማዳን ነው ። መዳን ትልቅ ትርጉም ያለው ነው ። ቤተ ክርስቲያን ጉዞዋን በተስፋ ጀምራ ፣ በመዳን ፈጽማለች ። ሥጋ ወደሙ የድኅነት ማዕድ ነው ። ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ከድኅነት ጋር የተያያዙ ናቸው ። “በስንቱ ነው የሚዳነው  በጥምቀት ወይስ በቍርባን ግራ ገባን” የሚሉ አጉል ቅንጡዎች ፣ የአይስክሬም ተማሪዎች ይኖራሉ ። ለመኖር ግን እንጀራም ፣ አየርም ፣ ብርሃንም ያስፈልገናል በስንቱ ነው የምንኖረው  ተብሎ ግን አይጠየቅም ። እስላሞች “ከአላህ የለሽ ፣ ወይ ከነቢ” እንዲሉ ከሁሉ የሌሉ ሰዎች ያሳዝናሉ ። ከእውቀቱም ፣ ከእምነቱም አለመሆን ከባድ ነው ።

የወደቀበትን ገደል ያየ መትረፉ ሲገርመው ይኖራል ። አደጋ ስለ መትረፋቸው በየዓመቱ እየደገሱ የሚያበሉ ፣ የሚያዘክሩ ሰዎች አሉ ። የዳኑት አንድ ጊዜ ነው የሚያዘክሩት ግን ዕድሜ ልካቸውን ነው ። ምስጋናቸውን ብቻቸውን መዝለቅ ስላቃታቸው አእላፋትን ሰብስበው ያበላሉ ፣ አመስግኑልኝ ይላሉ ። የዳኑት ግን ከጊዜያዊና ከማይቀረው ሞት ነው ። ከዘላለም ሞት የዳኑ ሰዎች ከብዙዎች ጋር ማመስገን ይገባቸው ነበር ፣ ነገር ግን ሰው ድኅነቱን ማቃለሉ ያሳዝናል ። ሳይንስን ከፍለው የሚማሩ ቃለ እግዚአብሔርን በነጻ መማር አልቻሉም ፣ ሥጋዊ ፈውስን የሚያሳድዱ ድኅነተ ነፍስን ከምንም አይቆጥሩትም ። “ጽድቅና ኵነኔ ቢኖርም ባይኖርም ፣ ከክፋት ደግነት ሳይሻል አይቀርም” የከበደ ሚካኤል ግጥም እንጂ የእግዚአብሔር ቃል አይደለም ። ጽድቅና ኵነኔ በርግጥ አሉ ። ቤተ ክርስቲያን ሃያ አራት ሰዓት የምትደክመው ይህን አምና ነው ። ብዙዎች ጨዋ ክርስቲያን እንጂ አማኝ መሆን አይፈልጉም ። ምክንያቱም ጽድቅና ኵነኔ ቢኖርም ባይኖርም በሚል አሳብ የሚመሩ ስለሆኑ ነው ።

ዜና ክርስቶስ የእውነት ቃል ፣ የመዳን ወንጌል ነው ። ይህ የእውነት ቃል አስቀድሞ በሐዋርያት በቃል የተሰበከ ለእኛ በመጽሐፍ የደረሰ ነው ። ያመኑበት ሁሉ አያድንም ። የሚያድነው በሚያድነው ማመን ነው ። እርሱም ክርስቶስ ነው ። ወንጌል የእውነት ቃል ነው ። እውነት ስለሆነው ስለ ክርስቶስ ይናገራልና ። እውነት ጸንታ ትኖራለች ። ዛሬ በችሎት ብትገፋ ነገ በሚፈርዱት ላይ የምትፈርድ እውነት ናት ። እውነት ጊዜዋን ጠብቃ ትወጣለች ። በዓለም ላይ ኃያላንና እናውቃለን ባዮች መቅበር ያልቻሉት እውነትን ነው ። ሃያና ሠላሳ ዓመት ታስረው ነጻ ናችሁ ሲባሉ የሚደሰቱት ከእስራቱ በላይ እውነት ተሸሽጋባቸው በመኖራቸው ነው ። ሬሳቸው ሳይቀር ነጻ የሚወጣ ብዙ ንጹሕ ሰዎች አሉ ። ከሞቱ ከብዙ ዘመናት በኋላ ንጹሕ ነበሩ ተብሎ የሚነገርላቸውን ስንሰማ እውነትን መቃብር እንደማይችላት ፣ ደግሞም ነጻ እንደምታወጣ ፣ በሌለንበትም እውነት ስለ እኛ እንደምትመሰክር ያሳየናል ። እኛ ዛሬ ለክርስቶስ እንመሰክራለን ፣ ፣ ነገ ክርስቶስ ለእኛ ይመሰክራል ።

የኤፌሶን መልእክት ትርጓሜ /23

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 13 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም