መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ቅዱስ ገብርኤል ሆይ!

የትምህርቱ ርዕስ | ቅዱስ ገብርኤል ሆይ!

እግዚአብሔርን እጅግ በመውደድ የታወቅህ ቅዱስ ገብርኤል ሆይ ፣ ሰውን እጅግ ትወደዋለህ ። የሰባ ዓመት የእስራኤል ግዞት ዓለመ መላእክትን አሳዝኗል ። ለኢየሩሳሌም የምሕረት ጊዜዋን ናፍቋል (ዘካ. 1 ፡ 12)። ከሥጋ ባርነት የነፍስ ባርነት ይጸናል ። የሰባ ዓመት ግዞት ካሳዘነ ፣ 5500 ዘመን በነፍስ ባርነት ላሉ የሰው ልጆች እጅግ ታዝናለህ ። ቅዱስ ገብርኤል ሆይ በሥላሴ መንበር ፊት ስትጠራ ለዳንኤል የነገርከው ሱባዔው መፈጸሙን አስታውሰህ ቀርበሃል ። ትንቢቱን ያመጣ ፣ ሱባዔውን የገለጠ ፍጻሜውንም ያበሥራል ብለህ ጠብቀህ ነበር ወይ ? በታላቁ ዙፋን ከስድስት ወር በፊት ለዘካርያስ የምሥራች ስትቀበል የድኅነት ዋዜማ ላይ እንደሆንን አውቀህ ነበር ወይ ? መልእክተኛው ከመጣ ንጉሡ ይከተላል ። በርግጥም አውቀሃል ። አንተ ቅዱስ መልአክ የ5500 ዘመን የኃጢአት ጅረት የሚቆምበትን ብሥራት እንደምትናገር አላሰብህ ይሆናል ። ታላቁ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል ሳይሆን አንተ ይህን የምሥራች ትናገር ዘንድ ተመረጥህ ። እርሱ በሰማይ ትልቅ ውጊያ ያካሂዳል ። የምሥራች እንዳይመጣ ፣ መርዶ ብቻ እንዲሆን የሚሠሩትን ፣ አማንያንን ተስፋ ለማስቆረጥ ፣ በሱባዔ ደጅ የሚጠኑትን “ከንቱ ደከማችሁ” ለማለት የተነሣሡትን ርኵሳን መናፍስትን ይፋለማል ። እርሱ መጋቤ ብሉይ ሁኖ እስራኤል ዘሥጋን ረድቷል ። አንተ መጋቤ ሐዲስ ሁነህ የምሥራችን ለማምጣት ተልከሃል ።

ቡሩክ መልአክ ገብርኤል ሆይ ፣ የዮሐንስ መጥምቅ መወለድ ደስ አሰኝቶሃል ። ደስ ያላለው የደስታ መልእክት ይዞ ሊሄድ አይችልምና ። ከዮሐንስ የሚበልጠው የእግዚአብሔር ልጅ ፣ የሰው ልጅ የሚሆንበት ዜና እጅግ ደስ አሰኝቶሃል ። የዮሐንስን መወለድ ለመናገር ወደ ኤልሳቤጥ ሳይሆን ወደ ዘካርያስ ሄድህ ። ክርስቶስ ግን ያለ ወንድ ዘር ይወለዳልና ወደ ድንግል ማርያም ተላክህ ።

ጨለማው ሰልጥኖ ፣ የሰው ልጅ ሁለት ጊዜ ሞቶ ፣ አንደኛው ሞት በፍርሃት ሁለተኛው ሞት በመቃብር ተጭኖት ነበረ ። ሙሉ ብርሃን ካለበት ሰማይ ላይ የምሥራቹን ፣ የወልድን ሰው መሆን ስትቀበል ነጥቀህ ለመሮጥ ፣ በመለከት ለማወጅ አልጓጓህም ወይ ? ድምፁን ስትሰማ ፣ በሥላሴ መንግሥት የተወሰነውን ስታደምጥ፡- “ተስፋውን የማያጥፍ ፣ ቀጠሮውን የማይሰርዝ” ብለህ እግዚአብሔርን ማመስገን አልጀመርህም ወይ ? በእርሱ ዘንድ ሺህ ዓመት እንደ አንድ ቀን ነው ። አምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመንም እንደ አምስት ቀን ተኩል ነው ። ከአምስት ቀን ተኩል በፊት ያለውን እኔም አስታውሳለሁ ። ጌታዬ ግን 5500 ዓመት የዘመን ርቀት ተስፋውን አላዘናጋውም ። ቅዱስ መልአክ ሆይ ታጥቀህ ቆመህ ፣ እጅ ነሥተህ ትእዛዝ ስትቀበል እግዚአብሔር ሰውን እንዴት ወደደው ? ብለህ አልተገረምህም ወይ ? በተደላደለው ሰማይ ብትኖርም በተጎሳቆለው ምድር ላለው ለሰው ልጅ ታዝናለህ ። ፍቅር ያለው የራሱን ምቾት አያስብም ። እኔ ገብቻለሁ ፣ ስለወጣው አልጨነቅም አይልም ።

ቅዱስ መልአክ ሆይ በሰማይ “አዳምን እንፍጠር” ሲባልና “እናድነው” ሲባል ታላላቅ ሁነቶችን ሰምተሃል ። በመልኩ የፈጠረው በወደቀ ጊዜ አሁን ደግሞ ሰው ሆኜ ላድነው አለ ። እግዚአብሔር መልኩን በተፈጥሮ ልኮ ፣ በተዋሕዶ መልኩን ለበሰው ። የንጉሥ ፎቶ መሬት ወድቆ አይቀርም ። ንጉሡ የራሱን መልክ ከመሬት አነሣው ። ትእዛዝ በትእዛዝ ይሻራል ። ተዋሕዶ ግን በመከፈል አይለያይም ። ስለዚህም አንተን የተዋሕዶ ምስክር አደረገህ ። ገብርኤል ሆይ ያንተ ወገን የነበረው መልአክ ወድቋል ። ለእርሱ ሳይሆን ለወደቀው አዳም የምሥራች ተላከ ። በዚህም ደስተኛ ነህ ። ሰማይ ፈቃደ እግዚአብሔር እንጂ የወገን አሳብ የለም ።

ቅዱስ መልአክ ሆይ ፣ ዓለሙ ሁሉ በታላቅ ፀጥታ ውስጥ ሳለ ፣ የሮማውያን ቤተ መንግሥትን ፣ የልዕልቶችን እልፍኝ አልፈህ ወደ አንዲት ገጠራማና ስም የለሽ መንደር ወደ ናዝሬት መጣህ ። በሥጋ ድሀ ፣ በነፍስ ግን ባለጠጋ የነበረችውን ድንግል አገኘህ ። እርስዋ ከንጉሥ ዘር ተወልዳ አሁን ግን በድህነት አለች ። ከአያቱ ባለጠጋ ያልነበረ ድሀ ፣ ከአያቱ ድሀ ያልነበረ ባለጠጋ የለም ። የዳዊት ልጅ እንዲህ በድህነት ስትኖር ፣ በምስጋና ስትቆም አገኘሃት ። አምላክን ለመውለድ ለምና ሳይሆን እርሱ በፈቀደ ከእርስዋ ሰው ሊሆን ወደደ ። ወልዶ የመከነ ልጄ ይለዋል ። እግዚአብሔር የመካኖችም ልጅ ነው ። እርስዋ ግን በባሕርያዊ ልደት ልጄ የምትለው ፣ በእውነት እናቱ ፣ በእውነት ልጅዋ ሆነ ። ቅዱስ መልአክ ሆይ ካንተ የምሥራች ጋር አብ ሊያጸናት መጣ ። መንፈስ ቅዱስ ተዋሕዶውን ሊያከናውን በማኅፀነ ድንግል ሥራ ጀመረ ። ወልድም ሥጋን ከእርስዋ ለበሰ ። የምሥራቹን በጆሮዋ በሰማች ጊዜ “ይሁንልኝ” ስትል አምላክ የዕለት ፅንስ ሁኖ በማኅፀንዋ አደረ ። አንተ የምትሰግድለትን ፣ በፍርሃት በፊቱ የምትቆምለትን እርስዋ በማኅፀንዋ ተሸከመችው ። እግዚአብሔርን ለመሸከም እግዚአብሔር አጸናት ። ጸጋ የበዛላቸውን እናደንቃለን ፣ ባለጸጋውን የወለደችው ድንግል ማርያም ግን ከሁሉ ፍጥረት ከብራለች ። ቅዱስ መልአክ ሆይ ይህን በማየትህ ሁልጊዜ የዳነው ዓለም ያስብሃል ።

ዓለምን ለወደደ ለእግዚአብሔር አብ ፣ ሰው ሁኖ ላዳነን ለኢየሱስ ክርስቶስ ፣ በጸጋው ሙላት ለጎበኘን ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋናና ክብር ውዳሴ ይሁን አሜን !

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 27 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም