መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ማርያም » ቅድስት ማርያም ሆይ !

የትምህርቱ ርዕስ | ቅድስት ማርያም ሆይ !

የሚራዳሽን ጠራቢውን ዮሴፍን በዓይኖችሽ እያየሽ ፣ በማኅፀንሽ ያደረውን ፣ ዓለምን ያለ መዶሻ ያነጸውን ጌታ ባሰብሽ ጊዜ ድንግል ሆይ ምን አልሽ ! ሰማይና ምድር የማይችሉት አምላክ በጠባብ ማኅፀንሽ ባደረ ጊዜ ከስፋቱ ሳይሰበሰብ ፣ ከምልአቱ ሳይጎድል ሥጋን መዋሐዱ አልገረመሽም ወይ ? ከላይ ከመንበረ ሥላሴ ሳይቀንስ ወረደ ፣ ከታች ሳይጨምር ተወለደ ። ድንግል ሆይ እርሱ ሳይሰማ እርስ በርሳችን እስቲ እናውራ ። እግዚአብሔር ሰው የሆነው ፈርቶ ነው ወይ ? ሁሉ እያለው እንደሌለው የሆነው ድህነትን ልለማመድ ብሎ ነው ወይ? በጉልበት ማስገበር ሲችል እርሱ ግን የባሪያን መልክ ይዞ መምጣቱ ተጨንቆ ነው ወይ ? አብዝተው ሲርቁት አብዝቶ የሚቀርበው መላ አጥቶ ነው ወይ ? እኛ መንግሥቱን ካጣን ገሀነመ እሳት እንኳ የእኛ ባለመሆኑ የምንገባው በደባልነት ነው ። ሰይጣን ባልበላውም ጭሬ ልበትነው ብሎ በተነሣ ጊዜ ሰው ክብሩን አጣ ። ሰው እግዚአብሔርን ሲያጣ ገሀነመ እሳት እንኳ የእርሱ ያልሆነች የስቃይ ስፍራው ናት ። ድንግል ሆይ ሌላ ፍጥረት አይፈጥርም ወይ ? እርሱ ደክሞ ነቢያቱንም የሚያደክመው ለምንድነው ? ይህን ዓመፀኛ ዓለም መደምሰስ አቅቶት ነው ወይ ሰባኪዎችን የሚያደክመው ? ይህንን ያወራነው ዘመዳችን ስለሆንሽ ነው ።

እርሱ እንዳይሰማን አደራ !! ወዳጁን የማያውቅ ጠላቱንም አያውቅም ። ስለዚህ ሰው የሰይጣን አሽከር ለመሆን ወስኗል ። ታዲያ እንዲህ ከሆነ ለምን አይተወንም ። ሲጠሉት አያውቅም ወይ ? የሚወደን መጥላት ስለማይችል ነው ወይ ? እባክሽን ድንግልናዊ ሀሊብን/ወተትን ስትሰጪው ጠይቂው ። ዓለምን እያስተዳደረ ፣ ደግሞ ከሕፃናት መካከል ሲሯሯጥ ጠርተሽ “ለጠላት ይህ ሁሉ ይደረጋል ወይ ?” ብለሽ ጠይቂው ። እርሱ በሰው አንደበት ቃልን ያስቀመጠ ፣ በይሁን አዋጅም ዓለምን የፈጠረ ሳለ በክንዶችሽ አፍ ያልፈታ ዲዳ ሕፃን መሆኑ ይገርማል !! ይህን ሁሉ የመከርነው በዘመድነትሽ ነውና እርሱ እንዳይሰማን አደራ ። ድንግል ሆይ ተዪው ። እርሱ ለካ ሰው ሁኗል ። የእኛን ምሥጢር ለማወቅ ለካ ሰው ሆኗል ። በአምላክነቱ ሁሉን ማወቁ አይጠረጠርም ። ግን የእኛን ምሥጢር ለማወቅ ሰው ሆነ ። “ምን እያደረጉ ነው ?” የሚለውን ለማወቅ ሳይሆን ሁሉን ሊያደርግልን ሰው ሆነ ።

አዎ ትዝ አለኝ ሰው የሆነው የሰውን ምሥጢር ለማወቅ ነው ። ጠባዩ የታወቀ ነው ፣ ምሥጢራችንን አይቶ ለመሸፈን ሰው ሆነ ። የመበደል አቅማችን የመጽደቅ አቅም ሊሆነን አልቻለምና ምሥጢራችንን አውቆ ምሥጢሩን ሰጠን ። በጥምቀት ልጅነትን ፣ በሜሮን ማኅተመ መንፈስ ቅዱስን ፣ በንስሐ ስርየትን ፣ በክህነት አገልግሎትን ፣ በተክሊል አንድነትን የምናገኝበትን ምሥጢሩን አደለን ። ምሥጢር አውቆ ምሥጢር የሚሰጠውን ልጅሽን ወደድነው ። ሌላ ፍጡር ቢፈጥርስ ብለን ነበር ። እርሱ ግን ሰይጣንን እንኳ መደምሰስ አልፈለገም ። የስድስቱ ቀን ፍጥረት ረግቶ እንዲኖር መለኮት ወሰነ ። ተበላሸ ብሎ የማይጥል ፣ ወደቀ ብሎ የማይረሳ ፣ እልፍ አለኝ ብሎ በአንዲቱ መጥፋት የሚቆጭ መሆኑን ተረዳን ። በገሊላና በይሁዳ ከተሞች የፈረሰን አድሳለሁ ፣ የሞተን አድናለሁ እያለ ዞረ ። ሐኪሙም መድኃኒቱም እርሱ መሆኑ ተገለጠ ።

አዎ ምሥጢራችንን ለመሸፈን ምሥጢር ሰጠን ። ትዳሩ አውጥቶ የጣለውን ፣ ችግሩ አደባባይ ያወጣውን ፣ ዘመድ ምቀኛ የሆነበትን ፣ ወዳጆች የከሰሱትን ፣ ልጁ ያዋረደውን ሊሸፍን እርሱ ሰው ሆነ ። የእኛን ክፉ ዜና ወስዶ የእርሱን መልካም ዝና ሰጠን ። ዕራቁቱን የቆመውን ሊጋርድ ፣ ዘመን የካደውን ዘመን ሊሰጠው ሰው ሆነ ። በእንግዶች ማደሪያ ስፍራ ያልተገኘለት ፣ ገና በፅንስ የተገፋው ኢየሱስ ፣ በጠዋቱ ለተጠሉት ቤዛ ሆናቸው ። ቅድስት ማርያም ሆይ ነፍሳችን የተገፋውን ልጅሽን ባሰበች ጊዜ በመገፋትዋ ደስ አላት ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 29 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም