መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የደስታ ቋጠሮ » በረከት በማክበር ይገኛል

የትምህርቱ ርዕስ | በረከት በማክበር ይገኛል

መልካም ጎረቤትህን አክብረው ። “ከሩቅ ዘመድ የቅርብ ጎረቤት” የተባለውን አትርሳ ። ክፉ ጎረቤትህንም ውደደው ፣ ዕቃ አያውስህምና ዕቃ ያስገዛሃል ። እጅግ የተዋበች ጽጌረዳ እጅግ የከፋ እሾህ አላት ። ዓለምም የሚያምርና የሚያደማ ነገር የያዘ ነው ። አበባውን ብቻ ስታይ እሾሁ ያነቃሃል ፣ እሾሁን ብቻ ስታይ አበባው ያጽናናሃል ። እንዳለ ያለ እግዚአብሔር ብቻ ነውና ፀጉሬ ሸበተ ፣ መልኬ ጠቆረ ፣ ቆዳዬ ተሸበሸበ ፣ እግሬ አነከሰ ፣ እጄ ዛለ ፣ ዓይኔ ደከመ ፣ ደሜ ከፍ አለ ብለህ አትጨነቅ ። ሞትን ብትሸሸውም ያለማቋረጥ የምትጓዘው ወደ እርሱ እንደሆነ እወቅ ። ዛሬ የሌሎችን ሞት ትሰማለህ ፣ ነገ ደግሞ ያንተን ሞት ሌሎች ይሰማሉ ። ከፍታህን ከፍ ባለ ቃል ሳይሆን ከፍ ባለ ኑሮ ግለጠው ። ሕያው መንፈስ አለህና በቁሳቁስ አትመካ ። ወርቁ ይዞ በነሐስ መመካት አለማወቅ ነውና ። አንተ ለእግዚአብሔር ስትኖር ፍጥረት ላንተ ይኖራል ። ጓዳህን ለሁሉ አታሳይ ፣ ምሥጢርህን በአደባባይ አትግለጥ። ድመት ክፉ ትመስላለች ፣ ነገር ግን ሐፍረቷን አታሳይም ። ውሻ ደግ ነው ነገር ግን ሐፍረቱን አይደብቅም ። ዝርክርክ ደግ አትሁን ።
ሁሉም የራሱ ጥያቄ አለውና አንተ ብቻ ሙግት እንዳለብህ አታስብ ። ለአገር የመጣ በአንድነት ቢያዝኑት ይቀላል ። የግልህን ችግር ከአገር ችግር ጋር እኩል አድርገህ አትመልከት ። ለአገርህ ኑር እንጂ አገርህ ላንተ እንድትኖር አትፍቀድ ። “ሰው ቢሞት በአገር ይለቀሳል ፣ አገር ቢሞት በማን ይለቀሳል?” የተባለውን አትርሳ ።
አንድ የሙዚቃ መሳሪያ ማወቅ ፣ አንድ የስፖርት ዓይነት መሥራት ፣ አንድ ማስታወሻ ለትውልድ መጣል ፣ አንድ ችግረኛን ነጻ ማውጣት ፣ አንድ ሃይማኖት መያዝ ፣ አንድ የትዳር ኪዳን ማጽናት አስፈላጊ መሆኑን እወቅ ። እየቻልህ ንፉግ ፣ እያወቅህ እውቀትህን ሰዋሪ አትሁን ። በዓለም ላይ ከዘራፊዎች ይልቅ እያላቸው የሚጨክኑ ቀማኞች ናቸው ። እውቀቱንም የሚሰውር ሌላ ነገር አያውቅም ። ሙሉ በሙሉ የማያውቅ ፣ ሙሉ በሙሉም የሚያውቅ የለም ። አድርጌአለሁ ለማለት ማንኛውንም ነገር ያለ ውስጣዊ ግፊት አታድርግ ። ሐሰት ከእውነት ትይዩ ጎጆ ትቀልሳለች ፣ መኮረጅ ትችላለች ፤ መሆንን ግን አትፈልግም ። “ሰይጣንም ላመሉ መጽሐፍ ቅዱስ ይጠቅሳል” ይባላል ። ሰይጣን ሙሉ እውነትንና ሙሉ ውሸትን አይወድም ።
“ሸንጋዮች ሲገናኙ ሰይጣን እራቱን ሊበላ ይሄዳል” ይላሉ ። በዚህ ዓለም ላይ የሰይጣን ባለ ሙሉ ሥልጣን አምባሳደር አስመሳዮች ናቸው ። ዓይናቸውን በጨው ካጠቡ ፣ የቀኑን ዘፈን ከሚዘፍኑ ፣ ማሊያ እየለወጡ መጫወት ከሚችሉ ተጠንቀቅ ። አሁን የአራዊት ሥጋት የለም ፣ ደኑ አልቋል ። በፎቅ ጫካ ውስጥ ያሉት አራዊቶች እነዚህ ናቸውና ተጠንቀቅ ። እግዚአብሔርን የማይፈራ ሰውንም አያፍርም ። አንተ ያዝረከረከውን ሌላው እንዲሰበስብልህ አትመኝ ። አንተ የጠላኸውን አገርም ማንም ሊወደው አይችልም ።
ክፋት መሥራት የነገ መንገድህን በእሾህ ማጠር ነው ። ኃላፊነትህን እግዚአብሔር ያየኛል ብለህ ተወጣ ። አደራ ከእግዚአብሔር ጋር የሚያገናኝህ መሆኑን አትርሳ ። ነገርን አታጓትት ። ዛሬ ማድረግ ሲቻልህ ለነገ ሥራህን አታስቀምጥ ። አመጋገብህን ልከኛና ጤናህን የማይጎዳ አድርገው ። የሰውን ዕድሜ ከሚያሳጥሩ ነገሮች አንዱ ቅጥ የሌለው አመጋገብ ነው ። ትንንሽ አስተሳሰብ ካላቸው ጋር አትጣላ ፣ ጥሉ ለእነርሱ ክብር ሲሆን ላንተ ግን ውርደት ነው ። ያጋጣሚ ፍቅር መልካም ነው ፣ እስኪበስል መጠበቅ ግን ወሳኝ ነው ። ሰውን ደግም ክፉ ብለህ በአንድ ቀን አትለካው ። በመጀመሪያ ቀን በጣም ጥሩ የመሰሉህ ላይሆኑ ፣ በመጀመሪያው ቀን ክፉ የመሰሉህ ክፉ ላይሆኑ ይችላሉ ። በእርጋታ መጓዝ እርጋታ የሌላቸው የሚያመጡትን አደጋ መቀነስ ነው ። አደጋ ባይቀርም መቀነስ የሚቻለው በጥንቃቄ ነው ።
ግዴታቸውን የማያውቁ መብታቸውንም ማወቅ አይችሉም ። ሦስት ዓይነት ጠባይ ያላቸው ሰዎች አሉ ፡- የመጀመሪያዎቹ ሁሉም የጋራችን ነው ብለው የሚያምኑ ፣ ሁለተኛዎቹ ፡- የእኔ የግሌ የሌላው የጋራችን ነው ብለው የሚያምኑ ፣ ሦስተኛዎቹ፡- የእኔ የሌላው ነው ብለው የሚያምኑ ናቸው ። ሁሉም የጋራችን ነው ብለው የሚያምኑ አብሮ መኖር የሚያውቁ ናቸው ። የእኔ የግሌ የሌላው የጋራችን ነው ብለው የሚያምኑ ያልሰለጡ ሰዎች ናቸው። የእኔ የሌላው ነው የሚሉ መንፈሳውያን ሰዎች ናቸው ።
ክብር በትግል አይገኝም ፣ መፈራትም እውነተኛ ክብርን አያመጣም ። ክብር ከእግዚአብሔር ነው ። ፍቅር የሌለው ክብር ደረቅ ነው ፣ ክብር የሌለው ፍቅርም ዕድሜው ያጠረ ነው ። መጣር መልካም ነው ፣ ቢሳካ ደስታ ባይሳካ ከጸጸት የሚያድን ነው ። እውነትህን እንጂ ስሜትህን አትግለጥ ። ቁጣህን ተቆጣው ። ስስትህን ሰስተው ። ፍቅርህን አፍቅረው ። ክብርህን ግን አታምልከው ። ግምትህን አትመነው ፣ ነገር ግን አትካደው ። ካልሾሙህ በቀር ሹመትን አትመኘው ። ሹመትን ሁለት ነገሮች በጽኑ ያዋርዱታልና ከእነርሱ ተጠንቀቅ ፡- ዝሙትና ፍቅረ ንዋይ ።
እውነተኛ ደስታ ያለው ስታደርግ እንጂ ሲደረግልህ አይደለም ። ደስታ እንደ ምንጭ ነው ፤ ምንጭ ወደ ውጭ ሲፈስስ ይስቃል ። ደስታም ሌላው ሲረካ በማየት የሚመጣ ነው ። እግዚአብሔር አቅምህን በጉልበትህ ውስጥ ሲያስቀምጥ ፣ ደስታህን ግን በሌሎች ጉድለት ውስጥ አስቀምጦታል ። ለወዳጅህ በቁሙ አበባ መስጠት ፍቅርህን መግለጥ ነው ፣ በሞተ ቀን መስጠት ግን ክብርህን መግለጥ ነው ። በሰው ሞት ላይ ክብርህን አታደራጅ። ይመጣል ብለህ የመጣውን አትግፋ ። አይመጣም ብለህ በጭንቀት አትከፋ ። ሁሉም ነገር በእግዚአብሔር መርሐ ግብር በመጓዝ ላይ መሆኑን አትርሳ ። አንተ ስትቆም አምላክህ ይቀጥላል ። በችግርህ አንተ ታዝናለህ ፣ አምላክህ ግን ችግርህን መለወጥ ይችላል ። ራእይን ያለ ችግር ፣ ልጅንም ያለምጥ መውለድ አይቻልም ። ሳትኖር አትሙት ፤ ሳትሞትም ሥራህን ፈጽም ። እውነተኛ ኪዳን በጣት ቀለበት ሳይሆን በልብ ፍቅር የሚገለጥ ነው ። ሰርግ የሌለው ትዳር ሊኖር ይችላል ፣ ትዳር የሌለው ሰርግ ግን ሊኖር አይችልም ። እግዚአብሔር ጥረትህን እንጂ ምኞትህን አያግዝም ። የሰው ትልቅነት የሚለካው ደስታን ብቻ ሳይሆን መከራንም በጸጋ በመቀበሉ ነው ። በበረሃው ዓለም ላይ ለምን አተኮሰኝ ማለት የትንሽ አስተሳሰብ ውጤት ነው ።
ማግኘት የሚያስደስተው ከመከራ ቀን ወዳጅ ጋር ሲካፈሉት ነው ። ድልም የሚያረካው ለራስ ሳይሆን ለአገር ሲከፈል ነው ። ሃይማኖትም በረከት ያለው ስለሌሎች ማሰብ ሲችል ነው ። ከኪስ ብዙ ገንዘብ በአእምሮ ያለ ትንሽ እውቀት ይበልጣል ። እውቀት ማለት ያልተመነዘረ ሀብት ማለት ነውና ። ቀኑ በጨመረ ቁጥር ያወቅኸው እየጠፋህ ይመጣልና ያወቅኸውን ዛሬ ተርጉመው ። ከሚያንስህ ጋር ለመርዳት ፣ ከእኩያህ ጋር ለጨዋታ ፣ ከሚበልጡህ ጋር ለምክር ተገናኝ ።
ችግረኛን ስታይ የተጨነቅህበትን ቀን አስበው ። በዚያ ቀን ማንም እንዲያልፍህ አትፈልግም ነበር ። አንተም አትለፍ ። እግዚአብሔር ላንተ የሚበቃህን ብቻ ሳይሆን የምትሰጠውንም አስታቅፎ ልኮሃል ። ሁሉ ባለ ራእይ አይሆንም ፣ ባለ ራእዩንም መንከባከብ ባለ ራእይነት ነው ። ትላንትን በሽማግሌዎች ፣ ዛሬን በትዳር አጋርህ ፣ ነገን በልጆችህ ማየት ትችላለህ ። በቁጥጥር ሥር የዋለ ችግር አያስፈራም ፣ የተሸነፈን ጦር ሕጻን ይማርከዋል፤ ለእግዚአብሔር የነገርከው ችግርም እንዲሁ ነው ። የሌላውን ስህተት ሲያወሩ የሚውሉ ማሰብ የማይፈልጉት ትልቅ ወንጀል ስላላቸው ነው ። ሲተች የሚውልን ሥራ ስጠው ። ለምን ይህ አልተደረገም የሚለውን እንዲያደርግ ኃላፊነትን አስታቅፈው ። ተቀምጠን ስናየውና ቆመን ስናየው ሁሉም ነገር ልዩነት አለው ። ከሺህ ምኞት አንድ እርምጃ ወደ ግቡ የተደረገ ጥረት ነው።
ከሞተ ደግ የቆመ ክፉ ያሳዝናል ። የሞተ ሰው ደግ የመሥራት አጋጣሚ የለውም ፣ የቆመ ግን ንስሐ የመግባት ዕድል አለው ።
ቤተ ክርስቲያን እስከ ዛሬ ትገፋለች ፣ የገፉአት እየወደቁ እርስዋ ግን ትኖራለች ። ከነቢያት አሻግሮ ማየትን ፣ ከሐዋርያት እውነትን መግለጥን ፣ ከወንጌላውያን የምሥራቹን ማዳረስን ፣ ከአስተማሪዎች ተክሉን ማጠጣትን ፣ ከእረኞች መንከባከብን ፣ ከሰማዕታት ቆራጥነትን ፣ ከጻድቃን ዓለም መናቅን ፣ ከደናግል በተሰጠን መኖርን ፣ ከመነኮሳት በኪዳን መጽናትን ፣ ከካህናት ምሥጢር መሰወርን ፣ ከሊቃውንትን ቃለ አሚንን ፣ ከእመቤታችን ከድንግል ማርያም ትሕትናን ተማር ። እግዚአብሔር ያከበረውን ማክበር በረከት እንዳለው አትርሳ።
የደስታ ቋጠሮ/20
ተጻፈ አዲስ አበባ
ሐምሌ 30/2010 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም