መግቢያ » ትረካ » በተዘጋው የሚመጣ » በተዘጋው የሚመጣ

የትምህርቱ ርዕስ | በተዘጋው የሚመጣ

“ደጆች ተዘግተው ሳሉ ኢየሱስ መጣ።” ዮሐ. 20፡26  ።
በጫካ ውስጥ በምሽት የሚገኝ መንገድ የጠፋው ነው ። በጫካ ውስጥ የሚደበቅ ወንበዴ የሚያሳድደው ነው ። በጫካ ውስጥ የጨለመበት ቀኑን ያባከነ ነው ። በጫካ ውስጥ ጨለማ ድርብ ነው ። ሌሊቱም መንታ ነው ። ግርማ ሌሊቱ ፣ ፀብአ አራዊቱ የሚያስፈራ ነው ። አዳም ስለ መሄጃው መንገድ እንጂ ስለ መመለሻው አላሰበም ። በገነት መጥፋት በጣም የሚደንቅ ነው ። በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሁነው ለጠፉት ምሳሌ ነው ። በምድር የጠፋ ይታዘንለታል ፣ በገነት የጠፋ ምን እንደሚባል ቃላት የሚያውስ ሰው ያስፈልጋል ። አዳም መንገድ እንደ ሳተ ወዴት ነህ ? የሚለው አምላካዊ ድምፅ አመልካች ነው ። አዳም የጠፋው መንገድ የዱሩ ሳይሆን የሕይወት መንገድ ነው ። የዱሩም የሕይወትም መንገድ ሲጠፋ ሁለቱም ጊዜ ያባክናሉ ፣ መንፈስን ያስጨንቃሉ ። መንገድ የሚጠፋው በሚያውቀው ነገር ውስጥ የማያውቀው ነገር እንዳለ ያሳያል ። አዳም አውቆ በመጥፋቱ ፍርድን ተቀበለ ፣ በማወቁ ውስጥ አለማወቅ ስለ ነበረ የመዳን ተስፋን ሰማ ።

“አዳምና ሔዋን ጠፍቷቸው መንገዱ ፣
ለሰው ልጅ መከራን ትተውለት ሄዱ፤” ተብሏል ። ይደብቃሉ የተባሉ ነገሮች ሁሉ አዳምን መሸሸግ አልቻሉም ። ከእግዚአብሔር መደበቅ አይቻልም ፣ በእግዚአብሔር መደበቅ ግን ይቻላል ። ከእግዚአብሔር መደበቅ ምክንያታዊነት ፣ በእግዚአብሔር መደበቅ ንስሐ ነው ። አዳም የተዘጋ ደጅ ባይታየውም መውጣት አልቻለምና ደጁ ተዘግቶበታል ። እውቀት ሲሰወርም የደጅ መዘጋት ነው ። አዳም ደጁን የዘጋው ከእግዚአብሔር ይልቅ ሰይጣንን ፣ ሚስቱንና ምኞቱን በመስማቱ ነው ። ከዚህ በፊት ባያውቀውም የኃጢአት እውቀትን ተለማመደ ፣ ከዚህ በፊት ባያውቀውም የንስሐን መድኃኒት ግን እንቢ አለ ። ለኃጢአት ፈጣን ፣ ለንስሐ ዳተኛ ሆነ ። በተዘጋው ደጅ ኢየሱስ መጣ ። በገነት ውስጥ የሰው ሕሊና ተዘግቶ ፣ በአዳምና በሔዋን መካከልም ግድግዳ ተገንብቶ ነበር ። መንገድ የጠፋው የዓለሙ ንጉሥ የሆነው አዳም ምሽት ደርሶበት ፣ ፀብአ አጋንንት በክስ ያስጨንቁት ነበር ። ምንም ያህል ጥፋት እንሥራ ከሳሽ ሰይጣን ነው ። ወቃሽ ሕሊና ግን የመንፈስ ቅዱስ መቅረብ ምስክር ነው ። አዳም ከእግዚአብሔር ሲጣላ አጋንንት ደፈሩት ። አራዊት ጠላት ሆኑበት ። የገዛ ሕሊናውም ከዳው ። እግዚአብሔር ለመንግሥተ ሰማያት ብቻ ሳይሆን ለሕሊና ሰላምም ያስፈልጋል ። ምኞታችንን የሚያረኩ ፣ እልህአችንን የሚያደምቁ ግፎች የሕሊና ሰላምን ያሳጡናል ። አዳም ተራቁቷል ፣ ነገር ግን ተራቁቻለሁ ማለት አልፈለገም ። ሰብአዊ ውድቀት ወደ ሰብአዊ ኩራት ወሰደው ። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የሰው ልጆች መንገዱ ጣለን እንጂ እኛ አልወደቅንም ይላሉ ። ገዥዎችም ከያዢዎቻችን ድክመት እንጂ እኛ አልወደቅንም በማለት ይናገራሉ ። ወድቆ መፎከር በንስሐ ፣ ወድቆ መሸለል በአምላክ ምሕረት ይቻላል ። ነቢዩ፡- ጠላቴ ሆይ ፥ ብወድቅ እነሣለሁና ፥ በጨለማም ብቀመጥ እግዚአብሔር ብርሃን ይሆንልኛልና በእኔ ላይ ደስ አይበልሽ ብሏል ። /ሚክ. 7 ፡ 8 ።/
አዳምን ለምን ወደቅህ ? አላለውም ። እንዴት ወደቅህም አልተባለም ። አዳም ግን በማን ምክንያት እንደ ወደቀ ለመናገር ቸኮለ ። ለምሕረት ተጠርቶ ሌላውን ከሰሰ ። የእግዚአብሔር ምሕረት የእርሱንም የሌላውንም በደል መሸፈን ይችላል ። የራሱ የጸጸት ድምፅ የሸሸገው አዳም አሁን ወዴት ነህ? በሚለው የእግዚአብሔር የፍለጋ ድምፅ ብቅ አለ ። ወዴት ነህ ? ሲባል እዚህ ነኝ ማለትም አልቻለም ። የወደቀ ሰው እዚህ ነኝ ለማለትም እውቀት ያስፈልገዋል ። በደሉን አልተናዘዘም ፣ በደሉ ያመጣበትን ዕራቁትነት ግን ተናገረ ። ቀድሞ ደስ የሚለው የእግዚአብሔር ድምፅ አሁን ፍርሃት ሆነበት ። የእግዚአብሔርን ቃል መሸሽ ስንጀምር በጣም ወድቀናል ማለት ነው ። ሰው የሚወደው ምግብ እያስጠላው ሲመጣ ታሟል ማለት ነው ። አዳም ለበደሉ ምክንያት እስኪያገኝለት ተጨነቀ ። እግዚአብሔር ያን በደለኛውን ይጠይቃል እንጂ ምክንያቱ እንደማይጠየቅለት አላወቀም ።
እግዚአብሔር ሰውን በመውቀስ አልጀመረም ። ውስጡ የሚናገረውን መናገር ተገቢ አይደለም ። አስፈቅዶ ማዳን ግን መለኮታዊ ግብር ነው ። ወዴት ነህ ? በማለት ያለበትን ሁኔታ እንዲያይ አደረገው ። ያለበትን ሁኔታ አይቶ አውጣኝ ካለ እንደ ጴጥሮስ ሰጥሞ ሳያልቅ እጁን ይዘረጋለታል ። ሰው በመለኮታዊ ርኅራኄ ካልተወቀሰ ወድቆ ሊቀር ይችላል ። የሕክምና ስህተት የሚባለው በሽታው ሳይሆን በሽታውን ለማዳን በተደረገ ሥራ የተፈጠረ አደጋ ነው ። አጽናናለሁ እያሉ ማቍሰል ፣ አተርፋለሁ እያሉ የበለጠ በእሳት ውስጥ መማገድ ሊኖር ይችላልና ጥንቃቄ ያስፈልጋል ። የአንዳንድ ሰዎች አቀራረብና አሰባበክ የበለጠ ሊያስክድ ይችላል ። የንስሐ ድምፆች በሰው ኃጢአተኝነት ላይ ሳይሆን በእግዚአብሔር ምሕረት ላይ ማተኮር አለባቸው ። የንስሐንና የማማከርን ሥራ የሚሠሩ አባቶችም እንደ መርማሪ ፖሊስ ሊሆኑ በርግጥ አይገባቸውም ። ሰውዬው እስከዚህ ድረስ ነው የሚሸከመኝ ብሎ ያመነውን ያህል ቢያማክራቸው የተሻለ ነው ።
ወዴት ነህ ? የሚለው ድምፅ የሕይወት ደጃፍ ለተዘጋበት ለአዳም የተነገረ ነው ። በኋለኛው ዘመን ወዴት ነህ ? ብዬ እፈልግሃለሁ ፣ ዛሬ በቃል በኋለኛው ዘመን ግን ሥጋ ለብሼ አድንሃለሁ ማለቱ ነው ። ፍለጋው በገነት ጫካዎች ጀመረ ፣ በቀራንዮ ፈጸመ ። ልብ አድርጉ እንጨት በልቶ የጠፋውን አዳምን ጌታችን እንጨት ተሸክሞ አዳነው ። ጸጋን ተራቁቶ ነበርና አምላካችን ዕርቃኑን ተሰቅሎ ክብር አለበሰው ። የዓለሙ ደጃፍ ሁሉ ተዘግቶ ፣ የገነት በርም ተቆልፎ ሳለ ኢየሱስ ክርስቶስ መጣ ።
ዓለም ሁሉ ግራ ተጋብቶ ነበር ። የነቢያት ትንቢት ፣ የሱባዔ ቆጠራ ፣ የጠቢባን የጥበብ ፍለጋ ሕዝብና አሕዛብ መሢሑን እንደ ጠበቁ ያሳያል ። በቤተ ልሔም የተገኙት መላውን ዓለም የወከሉ ናቸው  ። እረኞችና ነገሥታት ተገኝተዋል ። ሕዝብና አሕዛብም ሰግደዋል ። ደጆች ተዘግተው ሳለ ክርስቶስ መጣ   ። በዝግ ማኅጸን ተፀነሰ ። በዝግ ማኅጸንም ተወለደ ።
ዘመናችንን ልዩ የሚያደርገው ሁሉም እንደ ተቆለፈበት ግራ ሲጋባ ስናይ ነው ። በገዛ ቤቱም የተቆለፈበት በእስር ቤትም የተቆለፈበት ሁለቱም ስሜታቸው አንድ ዓይነት ነው ። ቤት ከእስር ቤት የማይሻልበት የስሜት እስራት ያለበት እየሆነ ነው ። የአዋቂዎች እውቀት አለማወቅ ለመሆን እየቸኮለ ነው ። አንዱን ቀዳዳ የሚደፍነው ሥልጣኔ ዘጠና ዘጠኝ ቀዳዳ የሚከፍት ነው ። ከአድማስ አድማስ በደቂቃ መገናኘትና ማውራት ይቻላል ፣ እንደዚህ ዘመን የሰው ልብ አልተራራቀም ። ሰዎች በሚመለከታቸው ርእስ ጠበኛ ናቸው ፣ የማውራት ትዕግሥት የላቸውም ። በማይመለከታቸው ርእስ ግን ቀኑን ሙሉ ያወራሉ ። ብዙ ደጆች ተዘግተው ሊሆን ይችላል ። የዓለሙ ፣ የአገሩ ፣ የቤቱ ፣ የሥራው ፣ የአገልግሎቱ ፣ … ደጆች ቢዘጉም ኢየሱስ ክርስቶስ ጌታችን ይመጣል ። በስሜታችን ሳይፈርድ የሚረዳን ጌታ ይመጣል ። በንስሐ በእምነት ሁነን እንጠብቀው ። የተበዳደልን ይቅርታ እንጠያየቅ ፤ ዘመኑ እንኳን ክፉ ሠርቶ ፣ ደግ ሠርቶም የሚያስጨንቅ ነው ።
ይቀጥላል
የመስቀሉ ገጽ 9/ሀ
ግንቦት 14 ቀን 2012 ዓ. ም.
ዲያቆን መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም