“ወንድሞች በኅብረት ቢቀመጡ፥ እነሆ፥ መልካም ነው፥ እነሆም፥ ያማረ ነው።” መዝ. 132 ፡ 1።
እግዚአብሔርን የሚያገለግሉ ካህናት ወደ ቤተ መቅደስ ሲጓዙ ከሚዘምሯቸው ዝማሬዎች አንዱ፡- “ወንድሞች በኅብረት ቢቀመጡ ፥ እነሆ ፥ መልካም ነው ፥ እነሆም ፥ ያማረ ነው” የሚለው ነው ። ሁሉም ሰው በግሉ በቤቱ መጸለይ ይችላል ። ቤተ መቅደስ ግን የተዘጋጀው በኅብረት ለመጸለይ ነው ። ወደ ቤተ ክርስቲያን የምንሄደው እግዚአብሔርን ብቻ ሳይሆን ሰዎችንም ለማግኘት ነው ። አዎ ሰዎችን ለማግኘት ነው ፤ ይህ ሊሰመርበት የሚገባ አሳብ ነው ። ለመሳሳም ፣ ሰላምታ ለመሰጣጠት ፣ ለመወያየት ፣ በአንድነት የምሕረት ደጅን ለማንኳኳት ነው ። መሳሳም ፣ ሰላምታ መለዋወጥ የቅዳሴው አካል እንደሆነ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ታስተምራለች ፣ ትፈጽማለች ። ክርስትና ከእግዚአብሔርና ከሰዎች ጋር ኅብረት ማድረግ ነው ። ክርስቶስም ያስታረቀው ሕዝብና አሕዛብን ነው ።
ወንድምነት ብዙ መገናኛዎች አሉት ። ነቢዩ “ወንድሞች” የሚለው በተፈጥሮ እኛን የሚመስሉትን ሁሉ ነው ። አንድ ዓይነት ማኅተም ያረፈባቸው ንብረቶች ዋጋቸው እኩል እንደሆነ ፣ በአንዱ እግዚአብሔር እጅ የተሠሩ የሰው ልጆች እኩል ናቸው ። ወንድምነት የእኩያነት ግንኙነት ነው ። እኩያነቱን የሚያመጣው ግን መልክና ችሎታ ሳይሆን ከአንድ አባት መወለድ ነው ። ከአንድ አባት የተወለዱ ባይተዋወቁም ወንድማማች ናቸው ። ወንድምነት የተፈጥሮ ማሰሪያ ነው ። ይህን ማሰሪያ እንቁረጥህ ባልን ቍጥር አደጋዎች ይፈጠራሉ ። እግዚአብሔር የሰጠን ተፈጥሮ በኅብረት የሚከወን በመሆኑ ግለኝነት እየጎዳን ይመጣል ። የሚገርመው ብዙዎቻችን መንግሥተ ሰማያትን እንመኛለን ፣ መንግሥተ ሰማያት ግን ከእኛ ዘመን በፊትና ኋላ ያሉ አእላፋት ያሉባት ስፍራ ናት ። የምንጠላውን ሰው በመንግሥተ ሰማያት ባላገኘሁ ብለን እንፈራ ይሆናል ። የጥላቻ ሰው ግን መንግሥተ ሰማያትን መውረስ አይችልም ። የፍቅርን ዓለም የፍቅር ሰው ብቻ ይወርሳታል ።
ወንድም የሚባል ብዙ ነው ። የሥጋ ዘመድ ፣ የአገር ልጅ ፣ የመከራ ጓድ ፣ ጽኑ ወዳጅ ፣ አብሮ የኖረ ፣ አብሮ ያደገ ፣ የሃይማኖት ቤተሰብ ፣ የአሳብ ተስማሚ … ይህ ሁሉ ወንድም ይባላል ። ጌታችን አብረውት ያደጉት ወንድሞቹ ተብለው ተጠርተዋል ። እርሱ ወንድሞቼ ሲላቸው ባያፍርባቸውም እነርሱ ግን ልካቸውን አውቀው ጌታ ብለው ጠርተውታል ፣ ራሳቸውንም “የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያ” ብለው ሰይመዋል ። ቅዱስነት ራስን ማወቅ ነውና ። (ያዕ. 1፡1፤ ይሁዳ ቁ. 1)። ከሥጋ ዘመድም የአሳብ ዘመድ ይበልጣል ። እመቤታችን ብዙ የሥጋ ዘመዶች ሳሉዋት ፣ መስቀሉ ሥርም እኅትዋና የእኅትዋ ባል ቀለዮጳ ሳሉ ጌታችን አደራ የሰጣት ለሚወደው ደቀ መዝሙር ለዮሐንስ ነው ። (ዮሐ. 19፡25-26)።
ይቀጥላል
ዕለተ ብርሃን 12
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መስከረም 23 ቀን 2016 ዓ.ም.