መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » ብሉይ ኪዳን » መዝሙረ ዳዊት » በኅብረት ተቀመጡ (3)

የትምህርቱ ርዕስ | በኅብረት ተቀመጡ (3)

“ከራስ እስከ ጢም እንደሚፈስስ፥ እስከ አሮን ጢም፥ በልብሱ መደረቢያ እንደሚወርድ ሽቱ ነው።”

መዝ. 132 ፡ 2 ።

ነቢዩ ዳዊት በእግዚአብሔር መንፈስ ሆኖ ከዛሬ ሦስት ሺህ ዓመት በፊት የሰጠው ምክር አጭርና ሦስት ቍጥሮች ያሉት መዝሙር ነው ። ይህን የኅብረት ምክር ለመኖር ግን እስካሁን አልተቻለም ። የጥንት ግሪካውያን “አንድነት ኃይል ነው” ይሉ ነበር ። ደካማ አገርና ትውልድ የሚወለደው አንድነትን በማጣት ነው ። በሰሎሞን ልጅ በሮብዓም ዘመን የእስራኤል መንግሥት ለሁለት ተከፈለ ። ሰሜኑ በአሦራውያን ጠፋ ፣ ደቡቡ በባቢሎናውያን ተደመሰሰ ። መለያየት ጥፋትን ይጠራል ። አንድ ሳሉ የተለያዩ አገራት እስካሁን ሰላም አላገኙም ። ኢትዮጵያና ኤርትራ ፣ ሱዳንና ደቡብ ሱዳን ፣ ሕንድና ፓኪስታን ፣ ሰሜን ኮሪያና ደቡብ ኮሪያ ተጠቃሽ ናቸው ። በመለያየት ውስጥ ማነስ ፣ ደካማነት ፣ ሁከት ጸንቶ ይኖራል ። ኅብረት አስፈላጊ ነው ያለን እግዚአብሔር ነው ። ምክንያቱም የፈጠረን ለኅብረት ስለሆነ ነው ። ትእዛዛቱም ከሰው ጋር ስላለን ግንኙነት የሚናገሩ ናቸው ። የመጨረሻው ቀን ጥያቄም ሰው ለሰው ስላሳየው ፍቅር የሚሸልም ነው ። (ማቴ. 25 ፡ 35) ። መለኮት በባሕርይው አይራብም ፣ በረሀብተኞች ውስጥ ሆኖ ግን ተርቧል ። ሰው የሆነ ለሰው ይገደዋል ፣ ያዝናል ።

ነቢዩ በመንፈሰ እግዚአብሔር ሁኖ የኅብረትን ውበት አሁንም እየገለጠ ነው ። የአሮን ጢም ኅብረትን ገላጭ ነበር ። ካህናት ጢማቸውን ያሳድጋሉ ። “ጢም የሌለው መምህር ፣ አጸድ የሌለው ደብር” ይባላል ። አይከብድም ማለት ነው ። ካህናት ጢማቸውን ያሳድጋሉ ። ይህ እርጅናን አባትነትን የሚያመለክት ነው ። ኅብረት በአሮን ጢም ከተመሰለ አንድ ስንሆን ለትውልድ አባት መሆን እንችላለን ማለት ነው ። ጢም ወንድነትን የሚገልጥ ነው ። የካህናት ጢምም ራስነትን ፣ መሪነትንና ሥልጣንን የሚገልጥ ነው ። ኅብረት ሲኖረን ሥልጣን አለን ማለት ነው ። ጸሎታችንም ሥልጣን ያለው ጸሎት ይሆናል ። “ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰበሰቡበት በዚያ በመካከላቸው እሆናለሁና።” (ማቴ. 18 ፡ 20) ።

ጢም ሊቆጠር አይችልም ። ብዙ ነው ። ካህናትም አበ ብዙኃን የብዙዎች አባት ናቸው ። ወይም የብዙኃን አባትነት ሊሰማቸው ይገባል ። ኅብረት ሲኖረንም ለድሆች አባት ፣ ለምስኪኖች መጠጊያ እንሆናለን ። ብዙ የእርዳታ ተቋማት የተመሠረቱትና የሚቀጥሉት በተባበሩ እጆች ነው ። “ሃምሳ ሎሚ ለአንድ ሰው ሸክም ፣ ለሃምሳ ሰው ጌጡ ነው” ይባላል ። ስንከፋፈለው ትልቁ ችግር ትንሽ ይሆናል ማለት ነው ። አንድ ሎሚ ወደ ላይ እየወረወሩ ይጫወቱበታል ፣ እያሸተቱ መዓዛዋን ይደሰቱበታል ። እየመጠጡ ይመገቡታል ። በኅብረት የየራሳችንን ድርሻ ስንወጣ የምንወስደው ግዳጅ መዝናኛ ፣ ደስታና ጥጋብ ይሆናል ፣ መልካም ራእይም ከሚመርዝ ክፉ አሳብ የሚያድነን ነው ። “የአንድ አሳቢ ፣ የአንድ በሬ ሳቢ” እንዲሉ አገርም ቤትም በአንድ ሰው አሳብ አይቆምም ። አንዱ ላይ ስንጥለው በሌላው ሞት ለመኖር አቅደናል ማለት ነው ።

በአንገት ተጠልቆ ከትከሻ እስከ ጉልበት በሚደርሰው የካህኑ ኤፉድ ላይ በደረቱ ሁለት አቅጣጫ የዐሥራ ሁለቱ ነገደ እስራኤል ስም አለበት ። በዚህ ኤፉድ ላይ ሽቱውን ሲረጭ መዓዛ ለእግዚአብሔር ሕዝብ ይሁን ማለት ነው ። ካህን የእግዚአብሔር ወኪል ነውና ንጽሕና በጎ መዓዛ ያለው ሊሆን ይገባዋል ። እጆቹ ደም ሳይሆን ዕጣን ይሸትታሉ ፣ በልብሱም መደረቢያ ሽቱ ያውዳል ። የእግዚአብሔር አገልጋይ ሥጋውም ነፍሱም ንጹሕና ምዑዝ ሊሆኑ ይገባቸዋል ። ኅብረት በካህኑ ልብስ ላይ እንደ ተረጨው ሽቱ ጣፋጭ ነው ። ካህኑ ሲባርክ ምእመናን ሽቱው ያውዳቸዋል፣ ደስ ያሰኛቸዋል ። ኅብረትም ሽቱ ነውና የራቁትን ያቀርባል ። ፍቅር ያጣው ዓለም ወደ እኛ የሚመጣው ፍቅራችንን ሲያይ ነው ። ለመባላትማ ዓለሙ መች አነሰው ! ኅብረታችን ምስክርነታችንም ነው ።

ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! እባክህ አንድ አድርገን!

ይቀጥላል ዕለተ ብርሃን 14

#ዲያቆን #አሸናፊ #መኰንን

መስከረም 25 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም