መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » ብሉይ ኪዳን » መዝሙረ ዳዊት » በኅብረት ተቀመጡ (4)

የትምህርቱ ርዕስ | በኅብረት ተቀመጡ (4)

“በጽዮን ተራሮች እንደሚወርድ እንደ አርሞንዔም ጠል ነው በዚያ እግዚአብሔር በረከቱን ሕይወትንም እስከ ዘላለም አዝዞአልና።” መዝ. 132 ፡ 3 ።

ኅብረት ማለት ያበረ ፣ የተባበረ ፣ አንድ የሆነ ፣ በቃል ኪዳን የተሳሰረ ፣ ዓላማን ለመነሻ መልካም ፍጻሜን ለመድረሻ አድርጎ ለፍቅር የዘመተ ማለት ነው ። የሚተባበር ሁሉ የተለያየ ቀለምና መልክ ያለው ነው ። አንድ ዓይነት ሊተባበር አይችልም ። የሚተባበር የተለያየ ቅርጽና ይዘት ያለው ነው ። የተለያየ ነገር ሲያብር ውበት አለው ። አበባ ውብ ነው ግን አንድ ዓይነት መልክ ያለው አይደለም ። በአንዱ ግንድ ላይ እንኳ ቢያንስ አረንጓዴና ሌላ ቀለም አለ ። ውበት የትብብር ውጤት ነው ። ነቢዩ፡- “በውኑ ኢትዮጵያዊ መልኩን ወይስ ነብር ዝንጕርጕርነትን ይለውጥ ዘንድ ይችላልን?” ይላል ። (ኤር. 13 ፡ 23 ።) ነብር በአንድ ቆዳ ላይ ብዙ ዓይነት ቀለም አለው ። ኢትዮጵያዊ የሚባለውም የተለያየ መልክና ቋንቋ ያለው ነው ። ይህ መልክ ከዛሬ 2600 ዓመታት በፊት እንደ ነበረ ነቢዩ ጠቁሞናል ። ለእውነቱ ስናየው በቅርብ ቀን የመጣ ቋንቋና ጎሣ የለም ። ለምን እንግዳ እንደሆንን ፣ የዓይናችንን በጆሮአችን እንዳመንን ግራ ያጋባል ። የተንኮለኞች ማሽን ሆነን ሲያስሩንና ሲበትኑን መኖራችን ይደንቃል ።

ኅብረት የሥላሴ መገለጫ ነው ። እግዚአብሔር በሦስት አካላት ፣ በአንድ ሥልጣን የሚኖር ነው ። ሦስት ስሞች አንድ አምላክነት አለው ። ሦስት ግብራት አንድ ህልውና ይነገርለታል ። ሦስት ኩነታት አንድ መለኮታዊ አሠራር አለው ። አካላችን የተለያየ መሆኑ በአንድ ቤተ ክርስቲያን መጠራታችንን አይገድበውም ። ስሞቻችን መለያየታቸው በአንድ ሰንደቅ ለማደር እንቅፋት አይሆኑም ። አባት ልጅ ብንባልም ሁላችንም አንድ ሰውነት ያዋሕደናል ። አንዳችን በአንዳችን ውስጥ በአሳብ ፣ በቃል ፣ በእንቅስቃሴ አለን ። ድርሻችን ቢለያይም የመገፋፋት ሳይሆን የመፈላለግ ምክንያት ነው ። እግዚአብሔር ኅብረትን የፈለገው የእርሱ መገለጫ ስለሆነም ነው ። በእግዚአብሔር መልክ መፈጠር ማለት በኅብረት መኖር ማለት ነው ። አንድ ዓይነትነት የምንፈልግ ከሆነ ከገዛ አካላችን ጋርም መኖር አንችልም። ፀጉራችን ከቆዳችን ፣ አጥንታችን ከጅማታችን ልዩ ነው ። በአንድ አካል ግን ተባብሮ ይኖራል ። የመልካችን መብዛት በረከት እንጂ ርግማን አይደለም ።

የአርሞንየም ጠል ለኅብረት ትልቅ ምሳሌ ሁኗል ። አርሞንየም አናቱ በበረዶ የተሸፈነ ነው ። በረዶውም ሲቀልጥ ከተራራው ሥር ምንጭ ይገኛል ። በአርሞንየም ተራራ ሥር ያሉ መንደሮች ሁልጊዜ ለምለም ፣ በበጋም ቀዝቃዛ ውኃ የሚያገኙ ናቸው ። በኅብረት የሚኖሩም ልምላሜ ደስታ ይኖራቸዋል ። ቤተሰባዊና ማኅበራዊ ኑሮ ያላቸው በጭንቀት አይጠቁም ። አንዱ ለአንዱ የጭንቀት መድኃኒት ነው ።

እግዚአብሔር ላዘዘው ነገር ሽልማት አለው ። ምንም እንኳ ጥቅሙ ለራሳችን ቢሆንም እርሱ ግን ቸር ነውና ይሸልመናል ። በኅብረት ውስጥ ያለው ሽልማት እንዲህ ተገልጧል ። “በዚያ እግዚአብሔር በረከቱን ሕይወትንም እስከ ዘላለም አዝዞአልና።” እግዚአብሔር በረከትንና ሕይወትን ጠራቸው ። እንዲህም አላቸው፡- ስሙ ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘላለም ኅብረት ባለበት ኑሩ።

በረከት ባለን ነገር መደሰት ነው ። በረከት የሚኖረን ነገር ሳይሆን ባለን ነገር መስፋት ነው ። ሕይወትም መቆምና መጽናት ነው ። ግለኝነትን ስንመርጥ መርገምና ሞት ያጠቃናል ። እግዚአብሔር ባዘዘን ነገር ውስጥ ምንም የሚያጸጽት ነገር የለም ። በኅብረት ውስጥ በረከትና ሕይወት ለዘላለም ይኖራሉ ።

ተፈጸመ
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መስከረም 26 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም