የትምህርቱ ርዕስ | ብርቱ ሰልፍ

“በምድር ላይ የሰው ሕይወት ብርቱ ሰልፍ አይደለምን ? ወራቱም እንደ ምንደኛ ወራት አይደለምን ?” ኢዮብ. 7 ፡ 1 ።

ነገር ነገርን እያነሣው የፍቅር ወሬ ወደ ጠብ የሚቀየርባት ፣ አዲሱ ቂም የቆየውን በቀል የሚቀሰቅስባት ሕይወት በምድር ላይ ብርቱ ሰልፍ ናት ። ይቅር ለማለት የሚታገሉባት ፣ ይቅር ያሉትን መልሰው የሚያቄሙባት ፣ ከባዱ ሰው የሚቀልባት ፣ ትልቁ ትንሽ የሚሆንባት ሕይወት በምድር ላይ ብርቱ ውጣ-ውረድ ናት ። “አገሩ ነው ችግሩ አገር እንለውጥ” እያሉ ሲያወጉ ቆይተው መልሰው “ዘመኑ ነው የሚባልባት” የራስን ችግር ለአገሩና ለዘመኑ እየሰጡ የሚቃዡባት ሕይወት በምድር ላይ ብርቱ ጥያቄ ናት ። በሽተኛው የሚያክምባት ፣ ወንጀለኛው ዳኛ የሚሆንባት ፣ መሃይም እየለፈለፈ ምሁር ጸጥ የሚልባት ሕይወት በምድር ላይ ብርቱ ወጀብ ናት ። ያጠኑት ምርምር ውሸት የሚሆንባት ፣ የናቁት ልማድ ክቡር ሁኖ የሚመጣባት ፣ ዓርብ ረቡዕ የሚገድፉባት ፣ እንደገና ጾም ጤና ነው የሚባልባት ፤ ማንም አያስፈልገኝም የሚሉባት ፣ መልሰው ያለ ሰው እንዴት እኖራለሁ? ብለው የሚያለቃቅሱባት ሕይወት በምድር ላይ ብርቱ ዕብደት ናት ። አያስፈልገኝም ብለው የሚኮሩባት ፣ የናቁትን መልሰው የሚከጅሉባት ፣ የሰሙትን የሚዘነጉባት ፣ ያልሰሙትን እንደ ሰሙ አድርገው የሚጣሉባት ሕይወት በምድር ላይ ብርቱ ስካር ናት ። መቆም ያልቻሉ ስለ አቋቋም የሚያሰለጥኑባት ፣ መራመድ ያልጀመሩ ስለ ግብ የሚጨፍሩባት ሕይወት በምድር ላይ ብርቱ ውጥን ናት ።

ነፍስ እያጠፉ ስለ እጽዋት የሚጨነቁባት ፣ የሰው ደም እንደ ቀይ ጽጌረዳ የሚታይባት ፣ ለራስ ሕይወት እየሰሰቱ “ያለ ደም ስርየት የለም” እያሉ በሌላው አንገት የሚፈርዱባት ሕይወት በምድር ላይ ፍርድ አልባ ናት ። ከራስና ከሰው አመል ጋር ትግል ፣ ከንጋትና ከምሽት ጋር ትግል ፣ ከደመናና ከፀሐይ ትኩሳት ጋር ትግል ፣ ከኑሮና ከሕመም ጋር ትግል ፣ ከረሀብና ከጥጋብ ጋር ትግል ያለባት ሕይወት በምድር ላይ መልከ ብዙ ናት ። የበለጸጉ በድሀ እንቅልፍ የሚቀኑባት ፣ ድሆች በባለጠጎች ኑሮ የሚመሰጡባት ፣ ምንም የሌላቸው የሌሎችን ገቢ የሚቆጥሩባት ፣ ያላቸው አልበቃ እያላቸው የሚጨነቁባት ፣ ሚሊየን የቸገረውና አንድ ብር የቸገረው እኩል የሚያምጡባት ሕይወት በምድር ላይ ብርቱ የቤት ሥራ ናት ።

ሕይወት በሰማይ ብርቱ ዕረፍት ናት ። ከቻሉ አለመቻል የሌለባት ፣ ከታመኑ ክዳት የማያገኛት ፣ ሥጋ የማይሟገትባት ፣ የሰዎች ክፋት የማይደርስባት ሕይወት በሰማይ ብርቱ ተድላ ናት ። የምድር መከራ በሰማይ እንኳን አለተከተለን ፤ የሰማይ ደስታም በሙላት እንኳን በምድር ላይ አለፈሰሰ ። አማኑኤል ሆይ! ይህን ያመጣጠነ እጅህ ቡሩክ ነው ። ረሀቡንም ጥጋቡንም እንችለው ዘንድ በትዕግሥት ባርከን ። ብርሃን በሚረጨው እጅህ ለዘላለሙ አሜን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 20 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም