መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ብቻዬን አይደለሁም

የትምህርቱ ርዕስ | ብቻዬን አይደለሁም

“ነገር ግን አብ ከእኔ ጋር ስለ ሆነ ብቻዬን አይደለሁም።” ዮሐ. 16፡32 ።

እግዚአብሔር ተናገረ፡-

ልጄ ሆይ፣ የመሸበትን እንግዳ ማን ያሳድራል  ቀን ሲስቁ የቆዩ ፣ በር ከፍተው ፣ ወንበር ዘርግተው ያጫወቱ ፣ አትሂዱ ብለው የተማጸኑ ፣ ዕድሜ ማራዘሚያ የሚበላ የሚጠጣ ደጋግመው ያቀረቡ ሲመሽ በልባቸው ውጡ ይላሉ ። “የገና ጀንበር ቶሎ ይመሻል” እያሉ አስወጥቶ በር ለመቆለፍ ይቸኩላሉ ። የምሽት ወዳጅ እኔ ብቻ ነኝ ። ጨለማ ቢያስፈራም ሰው የሚተኛው በጨለማ ነው ። በአስፈሪው ጨለማ እንቅልፍ የምሰጥ ፣ በመዓቱ የምባርክ እኔ ነኝ ። ትላንት የወደደ ዛሬ ላይወድ ፣ ትላንት የተለመነ ዛሬ ሊጨክን ፣ ትላንት የመሰከረ ዛሬ ሊክድ ይችላል ። መውደዴን የማከብር ፣ መለመንን የምሻ ፣ ቅዱስ ብዬ ርኵስ የማልል እኔ ነኝ ። የወጣሁ ፀሐይ ይጠልቃል ፣ የጠለቀውም ጀንበር መልሶ ይወጣል ። እኔ ግን ካየሁ የማልጨፍን ፣ ካበራሁ የማልጨልም ፣ ከያዝሁ የማልጥል ነኝ ።

ልጄ ሆይ ፣
ይህ ሁሉ የልብ ማመንታት ፣ ይህ ሁሉ የማያልቅ የተኩስ ወረዳ ምንድነው  ወዳጅህ ምሎ ቢከዳህ ፣ “እግዜር ምስክሬ ነው አላውቀውም” ቢልህ ምዬ የወደድኩህ ፣ “መሐለ እግዚአብሔር ለዳዊት በጽድቅ ፤ ወኢይኔስሕ” የተባለልኝ እኔ ነኝ ። /መዝ. 131፡11/ ፍቅሬ ጸጸት የለበትም ። መሐላዬም የጸና ነው ። ቀኔ አይደለም ብለህ መሸማቀቅህ ትክክል አይደለም ። አንዳንዶች በቀን ፣ ሌሎች በዕድል ፣ ሌሎችም በጥንቆላ ፣ ጥቂቶችም ባጋጣሚ ቸርነት ያምናሉ ። ሰጪና ነሺ ግን እኔ ነኝ ። ቀን ሁሉ የእኔ ሎሌ ነውና ቀኔ ዛሬ ነው በል ። ወደ ወጣህበት ቤት መመለስ ብታፍር ፣ ወደተዳርክበት ቤት ፈት ሁነህ መገስገስ ቢያሸማቅቅህ ፣ ወልደህ ሌጣ ፣ አግብተህ ብቸኛ ብትሆንም እኔ ግን የማልተው እግዚአብሔር ነኝ ። ስለ አንተ ያለኝ አሳብ ከዓለማትና ከዘመናት ፣ ከዓመታትና ከጽርሐ አርያም በላይ ነው ። ስለ አንተ ፣ አንተ የምትለው ብዙ ቢሆንም እርሱ ላይ እኔ ባለሥልጣኑ አልፈርምበትም ። ሰዎች ያሉህም እርሱ ያንተ መልክ አይደለም ። መልክህ በፍቅር ልቤ ተሰውሯልና አትፍራ ። ተናግረህ የተናገርከውን የምታዳምጥ ፣ ቃላት ቆጥረህ አውርተህም ምን አስቀየምኩ የምትል ፣ በእብዶች የምትሰቀቅ ፣ እንዳሻቸው በሚራመዱ የምትገረም ፣ እኔ ነኝ የተሳሳትኩት ወይስ ሌላው እያልክ የምታመነታ ፣ መንገድ የጠፋህ ደንባራ መሆንህን አውቄአለሁ ። ትላንት ያየኸው ፍቅር የዛሬውን ወረት ለመቀበል ፣ ትላንት ያየኸው መልካም ሰው የዛሬውን እሾኽ እንዳትለምድ አድርጎሃል ። ግራ ስትጋባ ቀኙን ላሳይህ ሁልጊዜ አጠገብ ነኝ ።

ልጄ ሆይ ፣
ስሜ ቢጠራ አይታወቅ ፣ ስሜ ለእኔም የጠፋኝ ፣ ስሜ በወረቀት ላይ ብቻ የቀረ ፣ እንደ መጣሁ ልሄድ ነው ብለህ የምትፈራ ብትሆንም ባላለቀ ተስፋ ላስደስተህ መጥቻለሁና ደስ ይበልህ ። የመከራ ጽዋህን ወስጄ የደስታ ዘይት ልቀባህ ቆርጫለሁና የእኔ ሆይ አትደናገር ። ራስህን ፣ ደግነትህን ፣ መንገድህን ለማስተርጎም አትሻ ። በምናገርበት ዘመን ሳትሰማ ፣ በዝምታ ዘመን ሰማኸኝ ። እኔ በዝምታም እሠራለሁ ። ዓለም ግን በወሬም አይሠራም ። ስመክርህ ያልገባህን ስትኖረው ተረዳኸው ። ስጠራህ ሳትሰማ ስትጎሰም አቤት አልከኝ ። መምጣትህ እንጂ እንዴት መምጣትህ አያሳስበኝም ። ከትላንት ታሪክህ ፣ የነገ ተስፋህ ብቻ ያሳስበኛል ።

ልጄ ሆይ ፣
አባብለህም የሚቀየምህ ፣ ወደህም የሚጠላህ ሲጠፋ ተናዳፊ እንደሆንክ ፣ የተሰማህንም ያለ ማጥለያ ለማውራት እንደቆረጥህ አውቃለሁ ። መጠየቅን እንደ ጠላህ ፣ ማስረዳትም እንደ ደከመህ አይቻለሁ ። ቅንነትህም ጭካኔህም ሁለቱም ደጋፊ እንዳጣ አውቄአለሁ ። በእግዚአብሔር ተፈጥረህ ያለ እግዚአብሔር አትኑር ። ወደ መጣህበት ልትመለስ ዘመኑ ሩቅ አይደለም ። እየወደዱህ ትሞታለህ ፣ እየጠሉህ ትኖራለህ ። ገንዘብም የመኖር ዋስትና አይሆንም ። ካንተ ጋር ነኝ ያሉት ከጠላት ጋር ይሆናሉ ። ልብህን የሰጠሃቸው ድንጋይ ይወረውራሉ ። የውስጤ ያልካቸው የውስጥ በሽታ ይሆናሉ ። ሰማይም ሊጠቁር ፣ ምድርም ልትከዳህ ፣ ቀትርም ሊጨልም ፣ ወዳጅም ሊበተን ፣ ያመሰገነም ሊረግም ይችላል ። እኔ ግን ካንተ ጋር ነኝና ብቻህን አይደለህም ።

ልጄ ሆይ፣
የሰውን ሥጋ ለብሼ ፣ በድንግል እናቴ ሥጋ ለባሽን ተዛምጄ መጥቻለሁ ። ደቀ መዝሙር ሁሉ ለምኖ መምህሩን ያበላል ፣ እኔ ግን ደቀ መዛሙርቴን ሁለት ዓሣና አምስት እንጀራ አበርክቼ ያበላሁ ነኝ ። መምህር ሁሉ ይፈለጋል ፣ እኔ ግን ጥብርያዶስ ድረስ ሄጄ የፈለግሁ ነኝ ። መምህር ሁሉ እግሩን ያጥቡታል ፣ እኔ ግን የደቀ መዛሙርቴን እግር አጥቤአለሁ ። መምህር ሁሉ ተማሪዎቹ ቀድመው ይሞቱለታል ፣ እኔ ግን ሞቼላቸዋለሁ ። መምህር በተማሪው ስሙ ይጠራል ። እኔ ግን ለደቀ መዛሙርቴ ስሜን ሰጥቻቸዋለሁ ። በወልድ ውሉድ ፣ በክርስቶስ ክርስቲያን ፣ በመንፈስ ቅዱስ መንፈሳውያን ተብለዋል ። እነዚህ ሁሉ ወዳጆቼ ግን ሐሙስ ምሽት ብቻዬን ትተውኝ ሂደዋል ። ስነሣ ግን ፈለኳቸው ። አንተም ስትነሣ ለገደሉህ ይቅርታ አድርግ ። እኔ ከካስኩ ሰውን መቀየም ከንቱ ነው ።

ምእመኑ መለሰ፡-

ጌታዬ ሆይ ፣ የተደናገረውን መንገድ የምትመራ ፣ ሕመምተኛውንና አስታማሚውን አብረህ የምትፈውስ ፣ በመሪዎች ጀርባ የምትመራ ፣ ማንም ሳይጠቁምህ ድሀን የምትረዳ ፣ ለችግረኛ ያለ ማስታወቂያ የምትሰጥ አምላክ ነህ ። ሁሉም ነገር ጥያቄ ሲሆንብኝ የሁሉም ነገር መልሴ አንተ ነህ ። ሰባራ በሰንጣራ በሚስቅበት ዓለም አዝነህ ሁላችንን ትሰበስበናለህ ። በተሻለ ደግነት ሳይሆን በተሻለ ክፋት ስንጽናና ታርመናለህ ። ልበ ሙሉ ሆኜ ለመበደል አምላክ የለም አልኩኝ ። ሰነፍ ከሚሠራ ምነው ጉንድሽ በሆንኩኝ ይላል ። እግዚአብሔር የለም ያልኩህ ለመታዘዝ ሰንፌ ነው ። ሱሰኛ ከሀዲ ነው ። ከሕሊና ጸጸት የዳንኩ እየመሰለኝም አባቶቼም እንደ እኔ ናቸው እላለሁ ። ራሴ ራሴን ሊሰናበተው ሲል ወዴት ነህ እልሃለሁ ። አለሁ ትለኛለህ ። እንደ ካድሁህ ያልካድከኝ ፣ ጀርባዬን ስሰጥህ ፊትህን ያሳየኸኝ አንተ ነህ ። መስጠም ስጀምር ፣ የማየው ሲሰወር ፣ የረገጥኩት ሲከዳኝ ፣ የምጨብጠው ምሰሶ ሲሰወርብኝ ጌታ ሆይ አድነኝ እልሃለሁ ። የጠራኸኝ አንተ ዓይንህን ከእኔ አታነሣም ። ያስጀመርከኝ ልታስፈጽመኝ ትተጋለህ ።

አምላኬ ሆይ ፣ የክፍል ትምህርት ደስ ይላል ። ፀሐይና ሩጫ የለውም ። ተቀምጦ ዓለምን ማሰስ ፣ ወንበር ተደግፎ መብረር ነው ። መምህሩ ካፒቴን ተማሪው የአሳብ ተሳፋሪ ሆነው የሚገሰግሱበት ነው ። የመስክ ትምህርት ግን ያወቅሁ የመሰለኝን እንዳላወቅሁት ፣ ሳይገባኝ ገባኝ ያልኩህን እንዳፍርበት ያደርገኛል ። ካልጨለመ ከዋክብት አይፈኩም ፣ አንዳንድ ሰዎችም ያለ ፈተና አያበሩም ። ከጠባብ ክፍል አውጥተህ ፣ ሰማይን ጠፈር ፣ ምድርን ሜዳ ፣ አድማሳትን ግዛት አድርገህ ስታስተምረኝ የመስኩ ስልጠና ከበደኝ ። የተጨበጠ እውቀት አገኝ ዘንድ ለጊዜው ጨከንክብኝ ። መስቀሌ ያሸሻቸውን ትተህ ፣ የመስቀል ወዳጆች ሰጠኸኝ ።

አዎን ጌታዬ ፣
ቀኑ ቢሻል ቢከፋ ፣ ዘመኑ ቢሮጥ ቢመጣ አንተ ከእኔ ጋር ነህና ብቻዬን አይደለሁም ። የተሰበሰበ ቢበተን ፣ የተካበ ቢናድ ፣ ፍርድ ከፍርድ አደባባይ ቢታጣ ፣ የነገው ስጋት ከዛሬው ችግር ቢከፋ አንተ ከእኔ ጋር ነህና ብቻዬን አይደለሁም ። ትንተናው ቢያስፈራ ፣ ኢኮኖሚው ቢመታ ፣ የሰው ዘር በስምምነት ሰውነቱን ቢከዳ ፤ ኪዳን ቢፈርስ ፣ መሐላ ቢታጠፍ አንተ ከእኔ ጋር ነህና ብቻዬን አይደለሁም ። የሠራሁት ቢፈርስ ፣ ያሳደኩት እሾህ ሁኖ ቢወጋኝ ፣ ያከበርኩት ዝቅ ሊያደርገኝ ሽቅብ ቁልቁል ቢል አንተ ከእኔ ጋር ነህና ብቻዬን አይደለሁም ። የለመንኩት ባይመጣ ፣ የጸለይኩበት መልሱ ቢዘገይ መላሹ ጌታ ግን አንተ ከእኔ ጋር ነህና ብቻዬን አይደለሁም ። የማይሸበር ልብ ፣ የማይዛነፍ እግር ፣ የተፈተነ ሕይወት ስጠኝ ። ለዘላለሙ አሜን ። የሚሰማህ አሜን ይበል ። ዕድሌ ተወሰደብኝ የሚል ይህም ዕድሉ ነውና አሜን ይበልህ ።

የፍቅር ጥሪ /2
ሰኔ 9 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኮንን

https://t.me/Nolawii

እባክዎ ይህን ቻናል ይቀላቀሉ፣  ለሌሎች ወገኖቻችንም ያስተዋውቁ

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም