መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ብቻ ወጣ ብለህ ና » ብቻ ወጣ ብለህ ና ! ክፍል 1

የትምህርቱ ርዕስ | ብቻ ወጣ ብለህ ና ! ክፍል 1

አገርህን መውደድህ ፣ አገርህን መጠበቅህ ፣ የአገር መከራ ተካፋይ መሆንህ ዋጋ አይሰጠውም ። ብቻ ወጣ ብለህ ና ፣ ዲያስፖራ ተብለህ መንግሥታዊ አቀባበል ታገኛለህ ። በቤተ ክርስቲያን ጥላ ተዘርግቶልህ የክብር ወንበር ላይ ትፈናጠጣለህ ።  አባም ብትሆን መምህር ወደ ገዳም ፣ ወደ ደብር ሳይሆን ወደ ቅርቡ ወደ ሱዳን ፣ ወደ ጦርነቱ አገር ደርሰህ ና ። እርሳቸው እኮ ሁሉን ትተው የመጡ ናቸው ይሉሃል ። በምንኵስና ስምህ እንደ ተለወጠልህ ወጣ ብለህ ስትመጣ ከጀርመን ከሆነ “አባ ጀርመን” ፣ ከቅርቡ ከሆነ “አባ ኬንያ” ትባላለህ ። አንተም እንዲህ ብለው ሲጠሩህ በብርዱ ይሞቅሃል ።

ብቻ ወጣ ብለህ ና ! እንዳንተ ጋምቤላ የሄደ ሰው በአራት ዓመቱ ቢመጣ እርሱን የሚጋብዙት የሉም ፤ የአንተ የግብዣ ፕሮግራም ግን አንድ ወር ሙሉ ተይዟል ፤ የሚጋብዙት ፍቅርን ፣ የሚጋብዙት ናፍቆትን ሳይሆን የመጣህበትን አገር ነው ። ብቻ ወጣ ብለህ ና ፣ ያወቅኸው ጠፍቶህ ሳለ ፣ ዶክተር ሆኛለሁ ብትል ያምኑሃል ። ለነገሩ የግሪክንና የአውሮፓን ፎቅ ማየት በራሱ ዶክትሬት ያሰጣል እያሉ ስንቱን ባለ ወረቀት አድርገውት ሲያታግሉን ኖረዋል ። የምመክርህ ወጣ ብለህ ና ፤ ሰዎች ሳይጠጡ ሰክረው ፣ ሳይቅሙ ነቅተው አንተ እኮ ይሉሃል ።

ወጣ ብለህ ና ፤ አማርኛ ሲጠፋህ እንደ ክብር ይቆጠርልሃል ። እዚህ ሰዋስዉ አልጠበቀም ተብሎ ስንቱ ከመድረክ ይባረራል ፣ አንተ ግን በአዛጦናዊ ቋንቋ በድብልቅልቁ ሁሉ ፈገግ ብሎ እንደ ኮልታፋ ሕፃን ይሰማሃል ። ወዳጄ ወጣ ብል ና ! እኔም በአገሬ ስላለሁ አትሰማኝም ። የአገር ምክር አይሰማምና ። የአገር ልጅ ታረቁ ሲል ባንዳ ነው ፣ የውጩ ታረቁ ሲል ብእሴ ሰላም ነው።

ወጣ ሳንል ቀርተን ስም ተሰጥቶን ፣ መናፍቅ ተብለን እንወገዛለን ። አገሪቱ ደርሶ ለመጣ እንጂ ለነዋሪው አትሆንምና ወጣ ብለህ ና ። ወጣ ብለህ ስትመጣ ዲያስፖራ መንደር ተብሎ መሬት ይሰጥሃል ። አገሩን የጠበቀው ድሀ የጨረቃ ቤት ተብሎ ይፈርስበታል ። ወጣ ብለህ ስትመጣ አገርህ ላንተ የሚሆን ሀብት አታጣም ። አንድ ዶላር አልሰጥም ብለህ ማንም አይቀየምህም ፣ እኔ ሕይወቴን ብሰጥ ማንም አይምረኝም ። ወጣ ብለህ ስትናገር ሁሉ ይሰማሃል ። አንዳንዴ ሰልፍ የምትወጣው ጭንቀትህን ፣ የቢል ጣጣህን ለመርሳት መሆኑን ማንም አያውቀውምና አክቲቪስት ብሎ ሁሉ ያወድስሃል ። ኧረ ወጣ ብለህ “ስንታገል ነበር” ብለህ ስታወራ ያጨበጭቡልሃል ። መድረክ ይለቁልሃል ። የድሀ ምክር አትሰማም እንጂ ወጣ ብለህ ና ።

ከቀሃ ወንዝ ማዶ ግጥም ብትገጥም ማንም ከቁብ አይቆጥርህም ፤ ከእንትን ወንዝ ማዶ ብለህ የፈረንጅን ወንዝ ስትጠቅስ ሁሉ እንደ ጋዜጠኛ ይስልሃል ። ወንዞች ለሚያያቸው ሰው የጋዜጠኝነት የምስክር ወረቀት መስጠት መጀመራቸውን የሰማሁት በቅርብ ነው ። ከጋምቤላው የባሮ ወንዝ ማዶ ቅኔ ብትቀኝ ማንም አይሰማህም ። ከፈረንጅ ወንዝ ማዶ ብቸኝነት ተሰምቶህ ስትቀመጥ ግን የዓለም ሰብአዊ መብት ተሟጋች ትባላለህ ። በአገርህ ሺህ መጽሐፍ ብትጽፍ የሚገዛህ ጠፍቶ በክረምት እሳት እያነደድህ ትሞቀዋለህ ። ወጣ ብለህ አንድ የሞኝ ንግግር ስትናገር ሊቅ ትባላለህ ። ስትሳደብ የአገሩ ቅንዓት በልቶት ነው ተብሎ ይታረምልሃል ። ብቻ ወጣ በል ፣ ደምህ መራራ እንዳይሆን ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ተጻፈ ሚያዝያ 20 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም