የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ተመስገን ጌታዬ

ጸጋህ አይጓደል ተመስገን ጌታዬ ፣
ሁሉን ያረክልኝ ባለውለታዬ ፤
አንድ አለኝ የምልህ ዘወትር ሁልጊዜ ፣
አንተ ነህ ጋሻዬ ደጋፊ ምርኵዜ ።
አቤቱ አምላክ ሆይ የሰማይ አባቴ ፣
አካሌ ሲደክም አንተ ነህ ጉልበቴ ፤
በሰላም በጤና ስኖር በዕድሜ ጸጋ ፣
ምስጋና ብቻ ነው የምሰጥህ ዋጋ ።

የኑሮዬ ባላ የሕይወቴ ቤዛ ፣
ለእኔ ያረክልኝ ውለታህ የበዛ ፤
ተመስገን ፈጣሪ ልበልህ ጠዋት ማታ ፣
ረዳቴ አንተ ነህ የቸገረኝ ለታ ።
ሲርበኝ አጉርሰህ ስታረዝ አልብሰህ ፣
ስጨነቅ አጽናንተህ ስታመም ፈውሰህ ፣
ድረስልኝ ስልህ ስምህን ጠርቼ ፣
የምፈልገውን አላውቅም አጥቼ ።

ቸኩለህ እንደ ሰው ቅጣት የማትሰጠው ፣
ሀብታምና ድሀ የማታስበልጠው ፤
ቸሩ መድኃኔ ዓለም ይድረስህ ምስጋና ፣
ረዳቴ አንተ ነህ በስምህ ልጽናና ።
ለኮንትራት ሕይወት ነገ ለሚቀረው ፣
በመንፈስ አጽናኝ ቃልህን እንዳልሽረው ፤
ኃጢአቴን ሰርዘህ አድነኝ ከዕዳ ፣
መሐሪው አንተ ነህ ለሰው ልጆች ፍዳ ።

እመካብሃለሁ በሰማዩ አባቴ ፣
የፈጠርከኝ አምላክ አውጣኝ ከኃጢአቴ ፤
ሳዝን ፈጥነህ ደራሽ ስከፋ መካሪ ፣
መከታ ጋሻዬ አንተ ነህ ፈጣሪ ፤
ዕዝራ በመሰንቆ ዳዊት በበገና ፣
እንዳቀረቡልህ ለሥራህ ምስጋና ፣
አወድስሃለሁ እኔም በዜማዬ ፣
አንተ ነህ ጠባቂ የሕይወት ጋሻዬ ።

(ምንጭ፡- ዘለሰኛ)

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሚያዝያ 10 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ