መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ተጠየቅ እግዚአብሔር

የትምህርቱ ርዕስ | ተጠየቅ እግዚአብሔር

ረገፈ እንደ ቅጠል ያ ሁሉ ትውልድ ፣ ያ ሁሉ ጠምበለል ። እንደ ወጣ አልተመለሰም ያ ሁሉ ወጣት ፣ የከፈተውን አልከደነም ያ ሁሉ ልጅ ። ሠርክ በጅምር ፣ በጥዋት ማታ የሆነበት ያ ሁሉ ጎበዝ ። በሜዳ የወደቀው ፣ አሞራ የበላው ያ ሁሉ ቡቃያ ። ተጠየቅ እግዚአብሔር ። እንዲህ ልታፈርሰው ለምን ገነባኸው ? እንዲህ ልትቀየመው ለምን አመጣኸው ? ተጠየቅ እግዚአብሔር ባንተ ቦታ እኔ ሳልመጣ ፣ በእኔ ቦታ አንተ ሳትቆም ተጠየቅ ባለ ዙፋኑ እግዚአብሔር ። መውለድ ቅጣት እስኪመስል ፣ ወገንን ለመጨረስ ገዥዎቻችን ሲታጠቁ ተጠየቅ እግዚአብሔር ሰው ሰውን ስለበላባት ስለእኛ ምድር ። እንደ እስራኤል አርባ ዓመት ቢሞላንም አልገባንም ከነዓን ። በተስፋ ያወጡን በረሃ ቀርተዋል ፣ የሰበኩን ሊቃነ ካህናትም ጥርኝ አፈር ሁነዋል ። እኛ ግን ገና ተስፋ ይዘን በቃዴስ በርኔ እንማስናለን ። እኮ ተጠየቅ እግዚአብሔር ። የረገጥነውን እንረግጣለን ፣ የሄድንበት ላይ እንመለሳለን ፣ የመጣው ክፉ ሲጣበቀን ፣ ደጉ ግን አይበረክትልንም ፤ የምንኖርበትን ከተማ መንገድ አጥተን ይህ ሁሉ ዘመን ለምንንከራተት ተጠየቅ እግዚአብሔር ።

ያ ሁሉ ሽበት ሲዋረድ ፣ ያ ሁሉ አእምሮ አደባባይ ሲወድቅ ። ዕድሜና እውቀት ወንጀል ሲሆን ለምን ዝም አልህ ተጠየቅ እግዚአብሔር ። የቅጣት ደረጃ የሌለን የመጀሪያውም የመጨረሻውም ቅጣታችን ሞት የሆነውን እኛን ለእኛ ስለተውከን ተጠየቅ እግዚአብሔር ። ብሶት ወልዶን ብሶት የምናስወልደውን ፣ ያለ ምንም ደም ብለን ደም ጨርሰን የምንወርደውን ፣ ለሰፊ ሕዝብ ብለን ለግለሰብ የምንኖረውን ፣ ለግፍ ተዋግተን ግፈኛ የምንሆነውን እኛን ስናብድ ስላላቆምከን ተጠየቅ እግዚአብሔር ። ስንጮህ የሚደርስልን ፣ ስንጣራ አቤት የሚልልን የሌለን ሕዝቦች ስንሆን ፣ ጥዋት ያበላነውን ከሰዓት ስንሰቅለው ፣ ሰውነትና ሰይጣንነት ሲቀላቀልብን ለፈቃዳችን ስለተውከን ተጠየቅ እግዚአብሔር ። የደም ምንጫችንን የሚዘጋው ሲጠፋ ፣ የምንታጠበው በሕፃናት ደም ሲሆን ይህንን ክፉ ግብር ዝም ስላልከው ተጠየቅ እግዚአብሔር ። ገደቤ እስከዚህ ነው ብለን ራሳችንን በመንደራችን ለማሰር እንደ ባቢሎን ሰዎች ግንብ ስንገነባ ፣ ግንቡን ለማፍረስ ስላልወረድህ ፣ ክፋታቸውን ይጨርሱት ብለህ ስለተውከን ተጠየቅ እግዚአብሔር ። ነጻ የሚያወጣን ነጻ የወጣ ስናጣ ፣ ቀኝ እጃችን ግራ እጃችንን ለዘመናት ሲቀጣ ፣ በመሳሪያ ተገደን ስንዘፍን በመሳሪያ ስናለቅስ የኖርነውን ፣ ለመሞት እንኳ ፈቃድ የተከለከልነውን እኛን ዝም ስላልህ ተጠየቅ እግዚአብሔር።
ትውልድ ግራ ሲጋባ ፣ ሊጫወት የሚገባው ሕፃን ስለ ምሳው አሳብ ሲያንገላታው ፣ የኑሮ ደረጃው አርያምና እንጦሮጦስ ሲሆን ፣ የከፋው በደንብ ሲከፋው ፣ ያገኘው በጣም ሲያገኝ ይህን ሚዛን አልባ ኑሮ ዝም ስላልከው ተጠየቅ እግዚአብሔር ። የሚመራን አጥተን ወደ ጉድጓድ ስንጓዝ ፣ በእሳት ወላፈን ስንጫወት ፣ ኪዳንን አፍርሰን ወንድማችንን ስንሸጥ ፣ ትዳር አቃለን ቤትን ስንንድ ዝም ስላልከን ተጠየቅ እግዚአብሔር ። ምኞታችን ሲጋልበን ፣ ለእውነት ሳይሆን ለስሜት ስንኖር ፣ ተዋርደን አላበቃ ስንል ፣ አንዱ ባንዱ ጣቱን ሲቀስር ፣ መንገድ የጠፋውን ስናደናብር ፣ የወደቀው ላይ መጥረቢያ ስናበዛ ፣ የሳተው ላይ ስላቅ ስናመርት ፣ የሄደውን አበሳውን ስናበዛ ፣ ላለው ስንዘፍን ፣ የሌለው የለውም ስንል ዝም ብለኸናል ተጠየቅ እግዚአብሔር ።
የተከፋ ብዙ ፣ የሚቅበዘበዝ ቊጥር የለሽ ነው ። የሚያጽናና አባት ፣ የሚሰበስብ እረኛ አጥተን ፣ በሞታችን የሚቀልዱ ፣ ለተዝካር ያገናኘን የሚሉ ሲገዙን ዝም ብለኸናል ፣ ስለዚህ እግዚአብሔር ተጠየቅ ። ሰው እኮ ያንተ ነው ። አንተ ጻድቅ ነህ ፣ ሰው ግን አፈር ነውና ቢያጥቡት የማይጠራ ነው ። ግድ አይልህም ወይ ? የፈጠርከው መጫወቻ ሲሆን አታዝንም ወይ ? ደግሞስ እንደ ሞኝ እንዴት ንብረትህን ትጥለዋለህ ? ነጻ ፈቃድ ብትሰጥስ ሁሉም ነገር ፀጥ ይበል ብለህ ልጆችህን አትሰበስብም ወይ ? ራሳችንን እንዳንጠይቅ የምንጠየቅበት በዝቶ እየረሳነው ነው ። እኛ ብንጠየቅም ጥቅም የለውም ። በዚያ ዓርብ በርባን ቢጠየቅ ዓለም አይድንም ነበረ ። መጠየቅ የነበረበት ወንጀለኛ ነው ። ነገር ግን በርባን ቢጠየቅ ሞት አይሞትም ። ወልድ ሆይ ዛሬም አንተ ተጠየቅና ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን አድን !!!   
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም