መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ተፈጥሮ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት

የትምህርቱ ርዕስ | ተፈጥሮ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት

ዮሐንስ መጥምቅ እግዚአብሔር በተፈጥሮ አማካይነት ያስተማረው ነቢይ ነው ። ተፈጥሮ ስለ እግዚአብሔር ደግነት ፣ ጥበብና ኃይል ይናገራል ። ተፈጥሮ በዝምታ ስለ እግዚአብሔር መኖር/ሀልዎት ይጮኻል ። ታላላቅ የእግዚአብሔር ሰዎች በተፈጥሮ ተሰብከው ወደ አሚነ ሥላሴ ተመልሰዋል ። ዮሐንስ መጥምቅ እግዚአብሔር በተፈጥሮ ያስተማረውና እርሱም በተፈጥሮ መርጃነት ያስተማረ ነው ። በምሥራቅ ሲዞር የናባው ተራራ ይታየዋል ። ተራራው ይደልደል ብሎ ትዕቢትን ይገሥጻል ። በምዕራብ ሲዞር ጠመዝማዛውና የደጉ ሳምራዊ የቸርነት ቦታ የሆነው የኢያሪኮ ቁልቁለት ይታወሰዋል ፣ ጠማማው ይቅና በማለት ድብቆችን ፣ በፍቅር የቀረባቸውን በብልጠት የሚቀርቡትን ከንቱዎች ይመክርበታል ። ወደ ሰሜን ሲመለከት ሸካራው የገሊላ መንገድ ይታወሰዋል ፤ በቂም በበቀል ውስጣቸው የነኮረባቸውን ሰዎች ተመለሱ ይልበታል ። ወደ ደቡብ ሲያማትር የምድራችን ዝቅተኛ ቦታ የሆነውን ሙት ባሕር ይመለከትና የዝቅተኝነት ስሜት ፣ አልችልም ባይነት ፣ ራስን ከሌላው ጋር የማወዳደር ስቃይ ያለባቸውን ምስኪኖች አስታውሶ ፣ ሸለቆው ይሙላ በማለት ያስተምርበታል ። እንደ ዮሐንስ መጥምቅ ስብከት የዓለማችን ችግሮች አራት ናቸው ። እነርሱም ትዕቢት ፣ ሽምቅነት ፣ ቂም በቀል ፣ የበታችነት ስሜት ናቸው ። ጥምቀትን ስናስብ እነዚህን መሰናክሎች ለማንሣት በመጣር ሊሆን ይገባል ።

ተፈጥሮ የእግዚአብሔር የእጁ ሥራ ነው ፣ ልንጠብቀው ይገባል ። ተፈጥሮ ስጦታችን ነው ፣ ልንወደው ይገባል ። ተፈጥሮ ትምህርት ቤት ነው ፣ ልንማርበት ይገባል ። ተፈጥሮ ከተፈጥሮአችን ጋር የተያያዘ ነው ፣ ለመኖራችን አስተዋጽኦ ያደርጋል ። ተፈጥሮ እግዚአብሔር ለእኛ ፍቅሩን የገለጠበት ነው ፣ ልንከባከበው ይገባል ። ጻድቅ ለእንስሳ ነፍስ ይራራል ፣ እጽዋትን እንኳን ሊቆርጥ ቅጠላቸውን ለመበጠስ ይሳሳል ። ዛሬ ዓለም እየተጋረጠባት ያለው አደጋ የተፈጥሮ መጎዳት ነው ። ከሰው ብቻ ደስታ ስለምንጠብቅ እንከስራለን ። እንስሳቱን ፣ እጽዋቱን ባለማስተዋላችን በረከታችንን አጥተነዋል ። አፈሩን ለመንካት ተጸይፈን ለእግራችን ጫማ ፣ ለእጃችን መሸፈኛ አድርገናል ። አፈሩን በመርገጥና በመንካት የምናገኘው ፈውስ አለ ። ከተፈጥሮ ጋር በርቀት የሚኖሩ የሞት ጎረቤት ናቸው ። ጥምቀት በውኃ የሚከናወን ነው ። ውኃ ፣ ጅረት ፈልገን የምናከብረው ከሆነ የወንዞች ንጽሕና ወሳኝ ነው ። ወንዞችን ላለመበከል ምእመናን ቃል የሚገቡበት ቀን ሊሆን ይገባዋል ። የተሰበሰበ ሕዝብ አግኝቶ አለማስተማር ፣ የሚዘምት ሕዝብ ይዞ አገርን አለመቀደስ በእውነት ስንፍና ነው ። እያንዳንዱ ሰው አንድ አንድ ቆሻሻ ቢያነሣ አገር ይጸዳል ።

እግዚአብሔር ራሱ በተፈጥሮ የሚያስተምር ነው ። ስለ በለስ ፣ ስለ ወይን ብዙ ጊዜ ተናግሯል ። ተፈጥሮን መጉዳት መንፈሳዊ ትምህርት ቤትን ማውደም ነው ። በደርግ ዘመን መንግሥትን የጎዳ እየመሰለው ችግኝ ዘቅዝቆ ይተክል የነበረው ወገናችን ዛሬ በድርቅ ፣ በዝናብ እጦት ይሰቃያል ። ደግመን እንናገራለን ። አገሩ የእኛ ነው ፣ ሌላ አገር የለንም ። ልንንከባከበው ይገባል ። የምናወራውና የምንጋጭበት ነገር ፣ ሰው ጠግቦ የጥርስ መጎርጎሪያ ይዞ የሚያወራውን ነው ። ስንዴ እየለመንን መነካከስ አሳፋሪ ነው ። የልመና መስፈርት እንኳ አታሟሉም ተብለን ለብድርና ለምጽዋት ተባርረናል ። ይህ ማቅ የምንለብስበት ዘመናችን ነው ። ጥምቀት ዮሐንስ ንስሐን የሰበከበት ፣ ብዙዎች የተመለሱበት ነው ። በጥምቀት ቀን ስካርና ጭፈራ ሳይሆን እግዚኦታ ሊደርስ ይገባዋል ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 23 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም