የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ትቀመጥ ዘንድ

 “ወደ መቄዶንያ በሄድሁ ጊዜ፥ አንዳንዶች ልዩ ትምህርትን እንዳያስተምሩና ወደ ተረት መጨረሻም ወደሌለው ወደ ትውልዶች ታሪክ እንዳያደምጡ ልታዛቸው በኤፌሶን ትቀመጥ ዘንድ ለመንሁህ ፤ እንደ እነዚህ ያሉ ነገሮች ክርክርን ያመጣሉና በእምነት ግን ላለ ለእግዚአብሔር መጋቢነት አይጠቅሙም።” 1ጢሞ. 1፡3-4 ።
የሮም መንግሥት በሚገዛበት ዘመን እስያ እንደ አውራጃ ትቆጠር ነበር ። ይህችውም የዛሬዋ ቱርክ ናት ። በዛሬዋ ቱርክ በኤጂያን ባሕር ዳርቻ ላይ የተመሠረተችው የኤፌሶን ከተማ ተለይታ የምትታወቅባቸው ሁለት ነገሮች ነበሩአት ። የመጀመሪያው፡- ሠላሳ ሺህ ሰዎችን በወንበር የሚያስተናግድ ትልቅ የጨዋታ ስፍራ ሲሆን ሁለተኛው አርጤምስ ወይም ዲያና የተባለች ጣዖት የምትመለክበት ትልቅ መቅደስ ነው ። ለአርጤምስም አምልኮት ይፈጸም የነበረው በዝሙት ስለ ነበር ብዙ ሴቶች የነበሩባትና ርኩሰትም የበዛባት ከተማ ነበረች ። ዝነኛዋ የኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን የተመሠረተችው በዚህች ከተማ ነው ። ቤተ ክርስቲያን በረከሰው ዓለም ላይ በቅድስና የምትኖር ፣ ኃጢአትን ማሸነፍ አይቻልም በሚል ማኅበረሰብ ዘንድ እንዴት ለእግዚአብሔር መኖር እንደሚቻል የምታሳይ የከተማ ገዳም ናት ። የቤተ ክርስቲያን ልጆችም የከተማ መናንያን ናቸው ። በኤፌሶን ከተማ ቤተ ክርስቲያን እንድትመሠረት ምክንያት የሆኑት አቂላና ጵርስቅላ የሚባሉ ባልና ሚስት ናቸው ። በኋላም ሐዋርያው ጳውሎስ አጠናክሯታል ። አዋቂው አጵሎስም አገልግሎባታል ። ጢሞቴዎስ ሐዋርያው ጳውሎስን ተክቶ ሲያገለግል ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊም እስከ ዘመኑ ፍጻሜ ድረስ የዚህች ቤተ ክርስቲያን የበላይ ጠባቂ ነበር ።

የኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን በመመሥረቷ ምክንያት የከተማይቱ ብረት ቀጥቃጮችና ጣዖት ሠሪዎች ገቢያችን ቀነሰ በማለት በሐዋርያው ጳውሎስ ላይ ብዙ እንግልት አምጥተውበታል ። ጣዖታውያንና አላዋቂዎች ወንጌልን የሚቃወሙት ንግዳቸው እንዳይቀዘቅዝና አደንቊረው የሚገዙት ወገን እንዳይነቃ ብለው ነው ።
የኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን የኤፌሶን መልእክት የተጻፈላት ፣ በወደቀው ከተማ ብትኖርም በሰማያዊ ስፍራ የተቀመጠች ፣ በመንፈሳዊ በረከትም የተባረከች አካለ ክርስቶስ ናት ። የስህተት ትምህርቶች ቆይተው ለእግዚአብሔር ያለንን ፍቅር ያሳጡናል ። ይህች ቤተ ክርስቲያን ስህተት እያንዣበበባት መሆኑን ሐዋርያው ተረድቶ መሪዎቿን አስጠንቅቆ ነበር ። ቸልተኛ መሪዎች ለትጉ መናፍቃን ሕዝብን አሳልፈው ይሰጣሉ ። ለሦስት ዓመታት ያህል በታላቅ ትጋት ያገለገላት ሐዋርያው ጳውሎስ የኢየሩሳሌም እስራቱ እየተቃረበ ሲመጣ ለመሪዎቿ፡- በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ”  አላቸው ። /የሐዋ. 20፡28/ ።
ይህች ቤተ ክርስቲያን ለጣዖት የተሠዋ ነገርን እንዲበሉና እንዲሴስኑ የሚያበረታታውን የኒቆላውያንን ትምህርት ተቃውማለች ። ነገር ግን ከአባላቷ በዚህ ትምህርት የተሳቡ ሳይኖሩ አይቀሩም ። /ራእ. 2፡6፤ ቁ. 14/ ። በዚህ ምክንያት የቀደመ ትጋቷን በመቀነስዋ፡- ዳሩ ግን የምነቅፍብህ ነገር አለኝ የቀደመውን ፍቅርህን ትተሃልና የሚል ወቀሳ ደርሶባታል ። /ራእ. 2፡4 ።/ ያንዣበባት ኑፋቄ ክርክርና ጥላቻን በመካከሏ አስነሥቶ ነበር ። ሐዋርያው ጳውሎስ ከእስራቱ በተፈታ ጊዜ ምናልባት በ62 ዓ.ም ገደማ ጢሞቴዎስ የኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ እንዲሆን ልኮት ነበር ። የጢሞቴዎስን መልእክት እንዲጻፍ ያደረገውም በኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን የገባው የስህተት ትምህርትና የጢሞቴዎስ ወጣት የቤተ ክርስቲያን መሪነት ነው ።
ይህች ቤተ ክርስቲያን የዮሐንስ ራእይ በተጻፈበት በ95 ዓ.ም ገደማ መንፈሳዊ መቀዛቀዝ ታይቶባት ነበረ ። ለሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት መልእክት ሲጻፍም የመጀመሪያው መልእክት የተጻፈው ለኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ነው ። /ራእ. 2፡1 ።/
መቄዶንያ ሰሜናዊ የግሪክ ግዛት ስትሆን ቱርክ ወይም ኤፌሶንም ለዚህች ግዛት ቅርብ ናት ። ሐዋርያው በሰሜናዊው በታላቁ እስክንድር መናገሻ ከተማ የማይፈርሰውን የክርስቶስን መንግሥት እየሰበከ ነበር ። የሚያያቸውን የመቄዶንያ ሰዎች ሲያገለግል በልቡ የሚመላለሱትን የኤፌሶን ሰዎችን እንዲያገለግል ጢሞቴዎስን ላከው ። ሐዋርያው፡- አንዳንዶች ልዩ ትምህርትን እንዳያስተምሩና ወደ ተረት መጨረሻም ወደሌለው ወደ ትውልዶች ታሪክ እንዳያደምጡ ልታዛቸው በኤፌሶን ትቀመጥ ዘንድ ለመንሁህ” ይለዋል ። የስህተት ትምህርቶች የፈጠራ ትምህርቶች እንጂ መለኮታዊ መገለጦች አይደሉም ። በጎችን የሚደፍር ተኩላ ፣ እረኛው ካለ ይፈራል ፣ እረኛው ሲዘናጋ ደግሞ ይደፍራል ። ትጉህ እረኛ የሆነው ጢሞቴዎስ የተላከው የስህተት አስተማሪዎች እንዲደነግጡ ነው ። የስህተት አስተማሪዎች በጎች አይደሉምና እረኛ አይወዱም ። መንጋውንም ለመስረቅ ከእረኛው ጋር እንዲጣላ ያደርጉታል ። ልዩ ትምህርቶች በየጊዜው ይፈጠራሉ ። እነርሱን ሁሉ በየጊዜው ማጥናት አይቻልም ። እውነቱን ማወቅ ግን እውነተኛ ያልሆነውን ለመለየት ያግዛል ።
ተረቶች ሁሉ ክፉ አይደሉም ። እውነትን ለማብራራት አጋዥ ማስተማሪዎች ናቸው ። ተረቶች እውነቱን ተክተው ሲቆሙ ግን ከባድ ነው ። የስህተት ትምህርት የሚባለው ይህ ነው ። መጨረሻም የሌለው የትውልዶች ታሪክ የተባለው ስለ ዓለምና ስለ ሰው አፈጣጠር የሚናገሩ የግሪክ አፈ ታሪኮችና ሐተታ አማልክት ናቸው ። ታሪኮችና የትውልዶች ታሪክ ዓለምን የፈጠረውንና ዘመንን ያስጀመረውን እግዚአብሔርን ማሳየት ካልቻሉ መቆሚያ የላቸውም ። የብዙ የጎሣ ግጭቶች መነሻ መጨረሻ የሌለው ሐተታ አማልክትና የትውልዶች ታሪክ ነው ። እነዚህ ተረቶችና የትውልድ ታሪኮች በመካከላቸው የጎሣና የቋንቋ ጠብ አሥነሥተው ይሆናል ። እስከ ዛሬ አማኝ የነበሩ አሁን ግን ጎሣቸው ውስጥ የተደበቁ በጣም ምስኪን ናቸው ። ከማይጠፋ ዘር ተወልደናል እያሉ ሲፎክሩ የነበሩ የሚጠፋ ዘርን ማቀንቀን ከጀመሩ የሚገርም ነው ። ትላንት ክርስቲያን ዛሬ ጎሠኛ የሆኑ ፣ የተራራቀውን የሚያገናኝ ድልድይ ከመሆን ተጨማሪ ግንብ የሚገነቡ በጣም ሊመከሩ ይገባል ። “ጊዜ የሰጠው ዘፈን እንቅርት ያፈርጣል” እንዲሉ የምንጮህበት ነገር ሁሉ በቃለ እግዚአብሔር መገምገም አለበት ። ትኩስን ቂም ተዉ በሚል ክርስትና የፈረሱ ቂሞችን ሕያው ማድረግና መጋደል ከአማንያን አይጠበቅም ። መምህራን ፈርተው ሊቀመጡ ሳይሆን ሊገሥጹ ይገባል ። ጢሞቴዎስ ወደ ኤፌሶን የተላከው ለዚህ ነበርና ። 
ሐዋርያው፡- “እንዳያደምጡ ልታዛቸው” ይላል ። ሰዎች እንዳይሰሙ ማዘዝ አንችልም ። እንዳያደምጡ ማለት በውስጣቸው እንዳይጽፉት ግን ማዘዝ አለብን ።
ሐዋርያው በመቀጠል፡- “ለመንሁህ”ይላል ። ሐዋርያው በዕድሜም ፣ በሥልጣንም ፣ በአባትነትም ማዘዝ ሲችል መለመኑ ትሕትናውን ያሳያል ። ትሕትና የሚያስፈልገው ከፍ ላለ ሰው ነው ። ዝቅ ያለውማ በግድ ትሑት ነው ። ትሕትና ያስፈለገው በከፍታ ላሉት ነው ።
ሐዋርያዊ መጻሕፍት የማጽናናት ብቻ ሳይሆን ከስህተት ትምህርት የመጠበቅ አደራ ያዘሉ ናቸው ። የስህተት ትምህርት እንክርዳድ በመሆኑ ስንዴውን ይጋፋል ። ነፍስን ያሰክራል ። ፍቅርን ያጠፋል ። ቁመት መለካካት ስለሚያመጣ በክርክር ምክንያት መናናቅና መነቃቀፍን ይከስታል ።
“በኤፌሶን ትቀመጥ ዘንድ” ይላል ። ይህ ጽሞና ለነበረው ለወጣቱ ጢሞቴዎስ ቀላል ትእዛዝ ሊሆን ይችላል ። ጽሞና የሌላቸው ወጣት አገልጋዮች ግን መቀመጥን አይወዱም ። ብክነት ትጋት ይመስላቸዋል ። መቀመጥን የማይወዱ ምእመናንም በሃይማኖት ቅምሻ አገሩን ሲያስሱት ይኖራሉ ። “ወጥን የሚያውቅ ቀላዋጭ ነው” እንዲሉ ስለ ሁሉም ቦታዎች ትንታኔ ያበዛሉ ። ብዙ ድስት የለመደ ተረጋግቶ መመገብ ፣ ከአንድ ስፍራ መማር አይሆንለትም ። የዘመኑ ሰማዕትነት መቀመጥ ነው ።
ጌታ እግዚአብሔር ሆይ ፣ እባክህን ባስቀመጥከን ቦታ መገኘት ይሁንልን !!!
1ጢሞቴዎስ /8/
ኅዳር 12 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ