መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ነፍሴን አሸንፈህ ስጠኝ

የትምህርቱ ርዕስ | ነፍሴን አሸንፈህ ስጠኝ

 “ለራስህ ታላቅን ነገር ትፈልጋለህን ? በሥጋ ለባሽ ሁሉ ላይ ፥ እነሆ ፥ ክፉ ነገርን አመጣለሁና አትፈልገው ፥ ይላል እግዚአብሔር ነገር ግን በሄድህበት ስፍራ ሁሉ ነፍስህን እንደ ምርኮ አድርጌ እሰጥሃለሁ ።” ኤር. 45 ፡ 5 ።

ጠቢባን ሽማግሌዎች ፣ ጸጋ እግዚአብሔር የበዛላቸው አባቶች ፣ የሚያስተውሉ ወጣቶች ፣ እንደ ሕዝቡ እየተመሳሰሉ መኖር አቅቶአቸው እብድ የተባሉ ሰዎች ፣ ቀን የጣላቸው ምስኪኖች ፣ መከራ እንደ በረዶ የወረደባቸው ምንዱባኖች ፣ ድህነት ዘመድ ሁኖ ያልተለያቸው ኅዙናን የሚናገሩትን ንግግር በጽሑፍ ማስቀመጥ በጣም ወሳኝ ነው ። ስንሰማው የማንጽፈው ነገር “ይህንማ አልረሳውም” የምንለውን ነገር ነው ። የሚገርመው ቀድመን የምንረሳው እርሱን ነው ። ምክንያቱም ሁለት ነው፡- የመጀመሪያው አእምሮአችን በማይመለከተው ነገር ስለተጣበበ የሚመለከተውን ነገር ለመያዝ ሙሉ ነው እያለ ይመልሳል ። ሁለተኛው፡- በተማመንበት ነገር ዝንጉ ስለሆንን እንረሳዋለን ። በፈተና የምንወድቀውም “እኔማ በዚህ አልወድቅም” በምንለው ኃጢአት ነው ። ምክንያቱም በዚያ ጉዳይ ስለማንጸልይ ነው ። ባሮክ ግን ስለ ሕዝቡ ፣ ስለ ሥነ መንግሥቱ ፣ ስለሚመጣው ዘመን በነቢዩ ኤርምያስ ይነገር የነበረውን ትንቢት በጥንቃቄ ይመዘግብ ነበር ። የመዘገበውንም ሕዝቡ በጾም በጸሎት ሕሊናው በሚሰበሰብበት ጊዜ ያነብ ነበር ። ለንጉሡም በድፍረት ያነብ ፣ ንጉሡ ሲያቃጥለውም ደግሞ ይጽፍ ነበር ። ባሮክ ማለት የስሙ ትርጉም “ቡሩክ” ማለት ነው ። ቡሩክ የሚባል ቁምነገርን መዝግቦ የሚይዝ ነው ። የእግዚአብሔርን ቃል በመዝገብ የሚያሰፍር ሰው ዛሬ እያነሰ ነው ። አባቶች፡- “በቃል ያለ ይረሳል ፣ በመጽሐፍ ያለ ይወረሳል” የሚሉት ለዚህ ነው ። ፊደልና መጽሐፍ እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ከሰጣቸው መገለጦች ቀዳሚ ናቸው ። ያልኖርንበትን ዘመንና የማንኖርበትን ዘመን የምናይበት መነጽር መጽሐፍ ነው ። 

መጽሐፍ ጽሞናን የሚጠይቅ ነገር ነው ። ባሮክ ግን ሕዝብና መንግሥት በራሳቸው ማስተዋል ተደግፈው በሚዋከቡበት ዘመን ፣ የሚያፈስሰ ጉልላት በሚደፍኑበት ዘመን በብራና ይመዘግብ ነበር ። በአስቸጋሪ ዘመን ያለውን የእግዚአብሔር መልእክት መዝግቦ መያዝ በጣም አስፈላጊ ነው ። እንዲህ ያለውን የመከራ ዘመንም የሚያልፉ እነዚህ አስተዋዮች ናቸው። በነቢዩ በሆሴዕ፡- “የማያስተውልም ሕዝብ ይገለበጣል” ይላል ። /ሆሴዕ . 4፡14።/

ታማኝ ወዳጅ መሆን ለራስ ያለን ክብር መገለጫ ነው ። ከዘመን ጋር የሚገለባበጥ እርሱ ታማኝ ወዳጅ መባል አይችልም ። በከፍታም በዝቅታም ከወዳጁ ጋር የሚቆም እርሱ ታማኝ ተብሎ በምድር በሰማይ ይከበራል ። ባሮክ የኤርምያስ የልብ ወዳጅ ነበረ ። የልብ ወዳጅነት በሰላም ዘመን ነው ። ታማኝ ወዳጅነት ደግሞ በመከራ ዘመን ነው ። ሰላምም ሁከትም ያልለወጠው ሰው ቢኖር ባሮክ ነው ። ምቀኛ ወዳጆች ስታገኙ ይርቃሉ ፣ ደካማ ወዳጆች ስትገፉ ይሸሻሉ ። እንደ ጴጥሮስ እንዳንክድ ፣ የመስቀል ሳይሆን የገበታ ወዳጅ ብቻ እንዳንሆን ተግተን መጸለይ ይገባናል ። ጸሎት ከዳተኝነት የተባለውን ዝንብ የምናባርርበት ጭራ ነው ። በዚያ ዘመን ከኤርምያስ አጠገብ መቆም ከባድ ነበር ። ኤርምያስ ሐሰተኛ ነቢያት ገበያችንን ይነካብናል ብለው ስሙን የሚያጠፉት ፣ ነገሥታት ባንዳ ነው ብለው ግዞት የሚሰዱት ፣ ሕዝቡ ደግ ደግ አያወራም ብለው እንደ ሟርተኛ የሚያዩት ሰው ነበር ። ያ ዘመን ሦስቱ ሕጎች በመንግሥትና በሕዝብ ተግባራዊ ተደርገው ነበር ። አንሰማም ፣ አናይም ፣ አንናገርም ። ኤርምያስ ግን የሐሰተኛ ነቢያት ምላስ ፣ የነገሥታት ጅራፍ ፣ የሕዝብ ውርደት ሳይከለክለው የሚመጣውን ነገር ይናገር ነበር ። ጥፋት እየመጣ መልካም ነው የሚሉት ነቢያተ ሐሰት እየተወደዱ እውነቱን የሚናገረው ኤርምያስ ግን ተጠላ ። በዚያ በደቦ ኃጢአት በሚሠራበት ዘመን የኤርምያስ ወዳጆች ኢትዮጵያዊው አቤሜሌክና ባሮክ ነበሩ ። እነዚህ ሰዎች ከቤተ መንግሥቱ ጋር ቅርብ ግንኙነት ቢኖራቸውም ወዳጅን በንጉሥ ቍጣ አልለወጡም ። የኤርምያስ ቃል እንዲሰማ ባሮክ በጽሕፈት በስብከት ፣ ከሞት እንዲድን አቤሜሌክ በምክር አደግድገው ቆመው ነበር ። በዚህም ምክንያት የደረሰባቸው ክፉ ነገር የለም። 

ባሮክ በመጨረሻ ከነቢዩ ኤርምያስ ጋር ወደ ግብጽ የተሰደደ ነው ። ወዳጅነት መውረጃ ፌርማታ የለውም ። ወዳጅነት እስከ ሞት ነው ። አብሮ መብላት ቃል ኪዳን ነው ። መንፈቅ የማይቆየው የዛሬው ፍቅር ተገለባባጭ ትውልድ እያፈራ ነው ። የአገራችን ገጣሚ እንዲህ ብሏል፡-

“ቀይ ሰው ሲጠቁር ፣ 

ጥቁር ሰው ሲቀላ ፣ 

እርሳስ ሾልኮ ሲሄድ በሰውዬው ገላ ፣

ልብ አይታመንም እንኳን ባልንጀራ ፤ 

አሁን ምንድነው ? ቅብጥር ቅብጥርጥር ፣ 

እገጭ ያለ ለት ቋሚው በቍጥር”

በሰላሙ ቀን እወድሃለሁ ፣ እወድሻለሁ አበዛዙ ። ምስክርነት ፣ የአድናቆት ቀን ለእገሌ የሚባል ድግስ መደገሱ ። ችግር የመጣ ቀን ያ ሁሉ ወድቆ የሚቀረው ጥቂት ባልንጀራ ነው ። ሌላም ገጣሚ እንዲህ ብሏል፡-

“ረጅም መቀነት ሳይስቡት ይጠብቃል ፣

የዘመኑ ፍቅር ሳይጀምሩት ያልቃል ፤

አሁን ምን ይባላል ሐተታ መናገር ፣ 

እየሰሙ መቻል ሳለ ደግ ነገር ፤ 

ከዚያም ከዚያም አትበይ እንደ ቆዳ ገድጋጅ ፣

አምላክ ከወደደው ይበቃል አንድ ወዳጅ ። 

ባሮክ ግን ፍቅሩ ቁምነገር ያለው ቋሚ ነገርን ለመተው የሚጥር ፣ ንጉሥና ሕዝብን ሳይቀር እየሞገተ ኤርምያስን የሚያድን ነበር ። ለዚህ ታላቅ ሰው እግዚአብሔር የሰጠው ቃል በመግቢያችን ላይ የጠቀስነው ነው፡- 

“ለራስህ ታላቅን ነገር ትፈልጋለህን ? በሥጋ ለባሽ ሁሉ ላይ ፥ እነሆ ፥ ክፉ ነገርን አመጣለሁና አትፈልገው ፥ ይላል እግዚአብሔር ነገር ግን በሄድህበት ስፍራ ሁሉ ነፍስህን እንደ ምርኮ አድርጌ እሰጥሃለሁ ።” /ኤር. 45 ፡ 5 ።/

ቤት መሥራት እንፈልጋለን ፣ አገር ከሌለ የት ልንኖርበት ነው ? ወይን መትከል እንሻለን ፣ አገር ከፈረሰ የት ሆነን ልንበላው ነው ? ትዳር እንሻለን ፣ አገር ከሌለን የት ሆነን ልንመራው ነው ? ልጆች እንፈልጋለን ፣ አገር ከሌለ የት ልናሳድጋቸው ነው ?

“አባት የሞተ እንደሁ በልጅ ይለቀሳል ፣

ባል የሞተ እንደሁ በሚስት ይለቀሳል ፣

ወንድም የሞተ እንደሁ በእኅት ይለቀሳል ፣ 

አገር የሞተ እንደሁ ወዴት ይደረሳል ፤” 

የተባለው ቀላል ነገር አይደለም ። እግዚአብሔርም ባሮክን ለራስህ ትልቅ ነገር ትፈልጋለህ ? ነገር ግን አትፈልገው አለው ። ኢየሩሳሌም ልትፈርስ ተቃርቦአልና ። አገር በሌለበት ሥልጣን ፣ ሀብት ፣ ዝና ፣ ከበሬታ ጥቅም የለውም ። በቅንጦት ይኖሩ የነበሩ ሶርያውያን ዛሬ ተበትነው ስናያቸው ያሳዝናሉ ። ክብራቸውን ፣ እውቀታቸውን የሚያውቅላቸው አጥተው በአውሮፓ ምድር ፣ በእኛም አገር ጎዳና ላይ ወድቀው ስናይ አገር ከሚሞት እኔ ልሙት ያሰኛል ። በፈረሰች አገር ላይ ካለ ባለጠጋ ፣ በቆመች አገር ላይ ያለ ለማኝ ክብር አለው ። ባሮክ ስደት እንደሚመጣበት እግዚአብሔር ከነገረው በኋላ፡- “ነገር ግን በሄድህበት ስፍራ ሁሉ ነፍስህን እንደ ምርኮ አድርጌ እሰጥሃለሁ” አለው ። 

ነፍስን ምርኮ አድርጎ መቀበል ቀላል ነገር መስሎን እንዳንታለል አደራ እላለሁ ። ዛሬ በሰለጠነው አገር ከአራት ሰው አንድ ሰው ፣ የአእምሮ ሕመም አለበት ይባላል ። ይህ ነፍስን የሚመለከት ጉዳይ ነው ። ባሮክ በሚሰደድበት አገር፡-

ልቡ እንዳይሰበር ፣

ሕሊናው እንዳይጎዳ ፣

ስሜቱ እንዳይረበሽ ፣

ጥያቄ ውስጡን እንዳያተራምሰው ፣

ቀልቡ ልቀቀኝ ብሎ እንዳያመልጠው ፣

ፈቃዱ ኃጢአትን መርጦ እንዳያዋርደው እግዚአብሔር ነፍስህን ምርኮ አድርጌ እሰጥሃለሁ አለው ። 

ከጸሎት ሁሉ የሚበልጥ ጸሎት ልብን የሚመለከት ጸሎት ነው ። “አቤቱ ንጹሕ ልብ ፍጠርልኝ” ፣ “አቤቱ ልቤን ጠብቅ” ፣ “አቤቱ ልቤን ወደ ክፉ ነገር አትመልሰው” ብሎ መጸለይ ትልቅ ጸሎት ነው ። 

ዓይንና ልብ የሕሊና መስኮት ናቸው ። በምናየውና በምንሰማው እንዳንሰበር ፣ የገዛ ልባችንን ማመን አቅቶን በማዕበል እንዳንመታ ፣ ሁሉም ነገር የዜሮ ድምር ሁኖብን ለመኖር ትርጉም እንዳናጣ እግዚአብሔር ነፍሳችንን ምርኮ አድርጎ ሊሰጠን ያስፈልጋል ። ለዚህ ደግሞ መድኃኒቱ ታማኝ ወዳጅ መሆን ፣ የእግዚአብሔርን ቃል ጽፎ ለትውልድ ሁሉ ማሰማት ፣ አንቱ ያሉትን ሰው አንተ ለማለት አለመቸኮል ፣ እንዲሁም መጸለይ ወሳኝ ነው ። 

እግዚአብሔር በምንሄድበት ሁሉ ነፍሳችንን ምርኮ አድርጎ ይስጠን ። አሜን!

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ነሐሴ 12 ቀን 2012 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም