መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ና ተመላለስ

የትምህርቱ ርዕስ | ና ተመላለስ

ያማረውን የፈጠርህልን ፣ እጅግም ያማሩ አድርገህ የፈጠርከን ፣ ቸል ያልናትን ነፍሳችንን ሰማይን ያየህላት ፣ ለሥጋችን ሕይወት የሰጠሃት ፣ የዓይንህ ማረፊያ ፣ የልብህ ደስታ እንድንሆን የፈቀድህ እግዚአብሔር እናመሰግንሃለን ። ለሚለምኑህ ትላንት የሰጠኸውን ችላ ብለህ እንደ ገና ትሰጣቸዋለህ ፤ አንተ የሰጠኸውን አትቆጥርም ። ላሰጣጥህም መስፈሪያ የለህም ። ለሚጠሩህም መልስ ትሰጣለህ ፣ ሰምተህ እንዳልሰማ አትሆንም ። ደግሞ ምን ፈለጉ ? ብለህ አትሰለችም ። ሳትሰማ አትበይንም ። ሁሉን እንደ አመሉ የቻልህ ፣ እንደ ጉድለቱ የሞላህለት አንተ ነህ ። ገንዘብ ሳይዙ የሚሸምቱብህ ገበያ ፣ የሕይወት ከተማ ክርስቶስ አንተ ነህ ። ያላስቀመጥነውን አምጣ እያልን ስናለቅስብህ በክብር የምትሰማን አንተ ነህ ። ልጅነታችን ባያስደስትህም አባትነትህ ግን አሳርፎናል ተመስገን ። በአንድ ልብ ሆነን ልናመልክህ ሰማይን እንናፍቃለን ። ዛሬ ከወሬ በኋላ ቃልህን ፣ ከዜና በኋላ ጸሎትን እናገፋፋለን ። ሰማይ ግን በአንድ ልብ እናመልክሃለን ። የምድር ኑሮ እንደ ድንጋይ መቀመጫ እያደር ቢቆረቁርም ከእርሱ ላለመለየት ብዙ እንጨነቃለን ። ከሰማይ እንዳንጎድል ግን ማሰብ እንኳ አንችልም ። እኛ የጨከንባትን ነፍሳችንን የራራህላት ምስጉን ነህ ።
ከሞት ወዲያ ዘመድም ወንድምም አንተ ነህ ። ምንነቱ በማይታወቅ ዓለም ፣ አረም በሚያበቅለው ሥጋ ውስጥ ፣ አበባ ሰጥተው አፈር በሚበትኑ በሰዎች መካከል ዛሬ አለን ። በሰማይ ግን ፍቅር ጽኑ ፣ ቅድስናም ብሩህ ነው ። በአገራችን ባንጋብዝህም በአገርህ ግብዣ እንዳታጎድለን አደራ እንልሃለን ። የውኃን ሙላት የምታጎድል ፣ የጎርፉንም ጽናት የምትገድብ ፣ ባሕሩን ገሥጸህ ሰላም የምትሰጥ ፣ መሻገሪያ አጥቶ ዙሪያው ባሕር ለሆነበት ጥፋትን የምታሸንፍለት አንተ ነህ ። አገርም መሸሻ ፣ ሥልጣንም ማምለጫ አይሆንም ። ሁሉም ነገር ያላንተ ከንቱ ነው ። እስከ ዛሬ መርከብ ማዕበል ያሰጋታል ፣ ማዕበልን ያሰጋ መርከብ ግን የለም ። የተጠለልንህ የእግዚአብሔር ልጅ ሆይ ሞገድ የማይበረታታብህ መርከባችን ነህ ። ሁሉን በሞት አንድ አድርገኸው እንደነቅ ነበር ፣ ሁሉንም በበሽታ አንድ አደረግኸው ። አንተ ስንመጣ ለእጅህ ጭብጥም የማንበቃ ነን ። ያመለክነውም አያድነንም ።
ተሸሽጎ የሚያለቅሰውን የምታይ ፣ እንባውን ሰው እንዳያይበት የሚፈራውን የምታስተውለው ፣ የልብን ትካዜ ከልብ ከተማ ላይ የምታስወግድ ፣ መንገድ ለጠፋው መንገዱ ፣ እውነቱ የት ነው ? ለሚል እውነቱ ፣ ሕይወቴ አለቀች ለሚል ሕይወቱ የሆንከው አንተ ክርስቶስ ነን ። የሥልጣንህ ዘንግ ፣ የጌትነትህ በትር ፣ የገዥነትህ ሕለተ ወርቅ ዛሬ ይዘርጋ ። እጅህን ካልዘረጋህልን የሚቀበለን ሞት ነው ። በአዳራሽህ ሞገስ ፣ በፊትም ደስታ ይሁንልን ። ከነቃን በኋላ መልሰን የተኛነውን እንደገና አንቃን ። በአንተ ጀምረን ያላንተ ለመኖር እቅድ ያወጣነውን ይቅር በለን ። ሰማዩም አፈሩም ያንተ ሳለ ልንሸሽህ ማቀዳችንን ልጅነት ነው ብለህ ውሰድልን ። በሚያስፈራው ሌሊት ከአጠገባችን እንዳትርቅ ። የክብር አክሊላችን ሲወርድ አንተ ክብራችን ሁንልን ። አመዱን አራግፈህ መጎናፀፊያን ፣ ማቁንም ቀደህ ወርቅ አልብሰን ። ዛሬም ያንተ ነውና ደስታን አብዛልን ። ከደመናት በላይ የምትመላለስ ፣ በምድራችንም ና ተመላለስ ። ምድሩ የእኛም ነውና ጋበዝንህ ። ጭንገፋንም አርቅልን ። ለዘላለሙ አሜን ።
የነግህ ምስጋና 13
መጋቢት 8 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም