መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » አልተዋችሁም

የትምህርቱ ርዕስ | አልተዋችሁም

“ወላጆች እንደ ሌላቸው ልጆች አልተዋችሁም ፤ ወደ እናንተ እመጣለሁ ።”
                     
ዮሐ. 14፡18 ።

እግዚአብሔር ለሚያቃስተው ምእመን በፍቅር ተናገረ፡-

ልጄ ሆይ ፣
ከባድ ቃላትን አይደለም ዝምታንም ማዳመጥ እንደ ጀመርህ ፣ ትችትን አይደለም ፣ ጎበዝ የሚል ድምፅን ማጣጣም እንዳቃተህ ፤ ጩኸትን አይደለም የለኆሳስ ንግግርን መቋቋም እንደ ተሳነህ ፣ ክስን አይደለም ወቀሳንም መስማት እንደ ቸገረህ አውቃለሁ ። መተንፈስንም እንደ ሥራ ቆጥረህ እንደ ደከመህ ፣ ሞትን እየተመኘህ ላለመሞት ብዙ እንደምትመገብ እገነዘባለሁ ። ሞትና ሕይወት የልብህን ከበሮ ሲደልቁት የቱን መምረጥ እንዳለብህ አቅቶህ ስትዋትት አይሃለሁ ፤ ላንተ ለመቸር ከተሰየሙት ከፀሐይና ከዝናብ ጋር እንደ ተጣላህ አውቃለሁ ። ልብስህ ባለ መድረቁ ትበሳጫለህ ፣ ፀሐይ በመውጣቷ ደግሞ ትተክዛለህ ። ደመናው ጨገገኝ ትላለህ ፣ ዋዕዩ አላስወጣ አለኝ ብለህ ደግሞ ታዝናለህ ። በቀጣይ ዓመት ራብ እንዳይመጣ ብለህ ትሰጋለህ ፣ ዝናቡን ደግሞ ታማርራለህ ። ልጄ ሆይ ፣ የምትፈልገውን ባለማወቅ እንደ ደከምህ ባውቅም ሳልታዘብ አይሃለሁ ። እኔ ስታዘብ ፍቅር መሆኔ ይቀራል ። ራሴን አልክድምና መታዘብ በእኔ ዘንድ የለም ። የምትለምነውን ባልሰጠሁህ ዘመን ደስተኛ ነበርህ ፣ ሳትለምን እየሰጠሁህ ግን አመስጋኝ አይደለህም ። ጊዜ ብታገኝ ብዙ እንደምትሮጥልኝ ነግረኸኝ ነበር ። ያገኘኸውን ጊዜ ግን ለድንዛዜ ሰጥተኸዋል ። የራስህን ድምፅ መልሰህ የምትሰማበት ፣ ቅዱስ ቃሌን ለማሰስ እጅ እግርህ የተያዘበት ይህ ማመንታት በጎ አይደለም ። ቀኑን አጋምሰህ ከመኝታህ ትነሣለህ ፣ ስሜ ሲቀደስ ግን በመኝታህ ላይ ሁነህ ትሰማለህ ። ሌሊቱን ነቅተህ ያለ ክፍያ ዘበኛ ሆነህ ራስህን ታደክማለህ ።

ልጄ ሆይ ፣
አዲሱ ቀን አዲስ ሁኖ አይታይህም ። የተደገመ ቀን አድርገህ ታየዋለህ ። የገዛሁልህን ልብሶች እንኳ ለመልበስ መነሣሣት ታጣለህ ። ብርሃኑን ምሽት ፣ ዕድሉን አጋጣሚ ፣ በረከቱን መሆን ስላለበት የሆነ ፣ ረዳቶችህን መሄጃ እንዳጡ ትቆጥራለህ ። ላለማየት ፣ ላለመስማት ፣ ላለመናገር ሁልጊዜ ትምላለህ ። መሐላህን በማፍረስህ ደግሞ ታዝናለህ ። ፍቅር ትንሽ ፈገግ ያደርግሃል ፣ ጥላቻ ግን ዓመት ሙሉ ያስለቅስሃል ። ዕድሜ ለቂም እንጂ ለይቅርታ አልሰጠህም ። የዳነው ስሜትህ መልሶ ያውክሃል ። ረግረጉ ጉዞ ወጣሁ ስትል ያስቀርሃል ። ትላንት የሚቀልህ የገዛ አካልህ ዛሬ እንደ በድን ይከብድሃል ። በፈተና ውስጥ ለበጎ ነው ይል የነበረው ብርታትህ በብርሃን ውስጥ ማመስገን አልቻለም ። እንደ ቀላል የነጋ መስሎህ ወደ ሥራህ ትሄዳለህ ፣ ግድ ስለሆነ የመሸ እየመሰለህ ወደ መኝታህ ትሰየማለህ ። በዚህ ሁሉ ውስጥ ልታመሰግነኝ አልቻልህም ። የበዛብህ የምስጋና ዕዳ ደስታህን እየተጋፋው ነው ። ለመሥራት የተፈጠሩ እጆችህ ስለለሰለሱ ሰውነትህ እየተሳሰረ ነው ። ወደ እግዚአብሔር ቤት እንድትሄድ የተፈጠረው እግርህ ስለሰነፈ አካልህ እየከበደህ ነው ። ስለሚሰቃዩት ማሰብ ባለመቻልህ ወደ ራስህ በጣም እያተኮርህ ነው ። ድሆችን ስለዘነጋህ የውሸት ፍቅር እያደከመህ ነው ።

እጆችህ ሱስ ስላለባቸው ይሰጣሉ እንጂ ደስታ እየተሰማህ አትሰጥም ። መራራትህ የእግዚአብሔርን ባሕርይ መካፈል መሆኑን ዘንግተህ ከመደሰት ትጸጸትበታለህ ። ሰዎች ባንተ ደስ የሚላቸውን ያህል አንተ በራስህ ደስ አይልህም ። የወላጆችህን መከተል እንደ ቀላል ታየዋለህ ፣ ሲፈልጉህ ትበሳጫለህ ። በሰርግ ጀምረህ በእሮሮ መኖርህን ታዝንበታለህ ። ሰዎች ያሻቸውን አድርገው ሲተኙ ምነው እንደ እነርሱ ለመሆን በቻልኩኝ ትላለህ ። ፍጻሜአቸውን ሳታይ በጅምራቸው ትቀናለህ ። ብታደርገውም እውቀት ቀድሞ በውስጥ ገብቷልና እንደ አላዋቂዎች መደሰት አትችልም ። በአሻንጉሊት ሕፃናት የሚደሰቱትን ያህል አዋቂዎች መደሰት አይችሉምና ።

ልጄ ሆይ ፣
መሪው ላይ ተቀምጠህ መሪውን ለቀሃል ፣ በአባትነት ሹመት ውስጥ ሁነህ የልጆችን ዓለም ተቀላቅለሃል ። እሳት ጥደህ ረስተሃል ፣ ልጅ አስተኝተህ አገር ለቀህ ሂደሃል ። ሰዎችን ሁሉ በጥቂት ክፉዎች መዝነህ ከሁሉ ርቀሃል ። አንድ ጊዜ ሞክረህ አቁመሃል ። እግዚአብሔርም ከሰው ጋር ያደመ መስሎህ ተቀይመሃል ። በመንፈሳዊነት ጀምረው በሥጋ ሲጨርሱ ፣ ቤተ ክርስቲያን ያገር ልጅ ዕድር ሲሆን ፣ የክርስትና ፍቅር በሥጋ ፍቅር ሲጠናቀቅ አዝነሃል ። የምትወዳቸውን ስትፈልግ የሚወዱህን ረስተሃል ። ብትጮህ የማይሰሙህን ስትጣራ የሚፈልጉህን ችላ ብለሃል ። ያልከውን ባለማግኘትህ እልህ ይተናነቅሃል ፣ የፈቀድኩትን በማግኘትህ ደስታ አጥተሃል ።

ልጄ ሆይ፣
የሚሞቱ እናትና አባትን የምሰጥ የማልሞተው እናትና አባት እኔ ነኝ ። አንተ “አባታችን ነህ ፣ አንተ እናታችን ነህ” ተብዬ በአባቶችህ የተመሰገንሁ ነኝ ። አንተ ግን ስሜትህ እንደ ሙት ልጅ ስሜት ቶሎ የሚከፋ ፣ ለማልቀስ ምክንያት የሚሻ ፣ ሲገፈትሩት ለመውደቅ በጥፍሩ እንደ ቆመ ሰው ነህ ። የጎደለህን እንጂ ያለህን ብዙ ማየት አልቻልህም ። የሞትና የወረት ገደብ ካላቸው ሰዎች ጋር ለዘላለም ፍቅር ትጀምራለህ ፣ ስለዚህ እልፍ ሲሉ መኖርን ትጠላለህ ። ባለህ ነገር ከመደሰት በሌለህ ነገር ውስጥ ደስታህን ታስሳለህ ። ዛሬ ያለህ ትላንት ያልነበረህና አልቅሰህ የጨበጥከው ነው ። ዓለም እንደ ተስፋው ፍጻሜው አያስደስትም ። በእኔ ካላረፍህ በሥጋዊም በመንፈሳዊም በረከት ማረፍ አትችልም ። ድውይ ብትፈውስ ፣ ሙት ብታስነሣም ደስተኛ አትሆንም ።

ልጄ ሆይ ፣
የመተው ስሜት ፣ የመጣል ዕዳ ውድቆብሃል ። በሰው መካከል ብቸኝነት ፣ በለማው ከተማ በረሃማነት እያሰቃየህ ነው ። የስሜት ሥዕልህን በጣም ታምነዋለህ ። የአሳብ ጎጆህም ስትነቃ እየፈረሰ ትበሳጫለህ ። እኔ ግን ካንተ ጋር ነኝ ። ቅዱስ መንፈሴም አይለይህም ። ዓርብ ሞት ቢመጣም እሑድ ትንሣኤ ነው ። ከመሬት በታች ብትከተትና ዝናህ ቢረሳ ዕርገት በአርባኛው ቀን ነው ። ትጥቅህ ቢፈታ የበዓለ ሃምሳ ደስታ በቤትህ ነው ። የተሰማህና እውነቱ ለየራስ ነው ። እኔ ካንተ ጋር ነኝ ። እኔ ከሺህ ወዳጆች ፣ ከሺህ ዕድሎች እበልጣለሁ ። በዚህ ቃል ተጽናና።

ምእመኑ በእንባ መለሰ፡-

ጌታዬ ሆይ ፣ እውነት ነጻ ታወጣለች ብለሃል ፤ እውነትም እኔ ነኝ ብለሃል ። በእውነትህ ከአሳቤና ከክፉ ምኞቴ ፍታኝ ። ወደ ውስጤ ጠልቀህ በአሳቤ አደባባይ ያለውን ጦርነት አንሣልኝ ። የሚታዘንልኝ ሰው ለመሆን ምስኪንነትን እንዳልለማመድ የትንሣኤህ ሠራዊት አድርገኝ ። እኔ ትቼህ አንተ ተውከኝ እልሃለሁ ፣ አለመኖር ውስጥ ሆኜ የለህም እልሃለሁ ። በውስጤ ሳለህ በደጅ እፈልግሃለሁ ። ለሌሎች ላደርስ የሚገባኝን ከልክዬ የራሴ በረከት ተይዞብኛል ። ደስታዬ ጎረቤቴ ድሀ ውስጥ ሳለ የባሕር ዳርቻ ላይ እፈልገዋለሁ ። አንተ የነገርከኝን ተጠራጥሬ የጠላትን ድምፅ እውነት ብዬ እቀበላለሁ ። እባክህን ጌታዬ ከስሜቴ ቃልህ ፣ ከፍርሃቴ እምነት እንዲበልጥብኝ እለምንሃለሁ ። ሆደ ባሻነቴ በልበ ሰፊነት ይለወጥ ። እያስፈራራሁህ ማገልገሌ ቀርቶ እየፈራሁህ እንድገዛልህ እርዳኝ ። አንተ ሕያው ጌታዬ ነህና የሙት ልጅ ስሜትን ፣ የእጓለ ማውታ ፍርሃትን ከእኔ አርቅ ። በዘላለማዊ ሥልጣንህ ፣ ከመቃብር በላይ በገነነው ክብርህ አሜን ። የሰማይ መላእክት አሜን ይበሉ ።

የፍቅር ድምፅ /3

ሰኔ 10 ቀን 2012 ዓ.ም.

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም