የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

አምላካችን

“አምላካችን መጠጊያችንና ኃይላችን ፥ ባገኘን በታላቅ መከራም ረዳታችን ነው።” (መዝ. 45 ፡ 1 ።)

እግዚአብሔር አምላክ ነው ። ፍጡራን አምላክ ብለው ያልሰየሙት ፣ አምላክ ያላደረጉት ነው ። አምላክነቱ የባሕርይ ገንዘቡ የሆነ ፣ አምላክ ሳይሆን ያልኖረ ፣ አምላክነቱን አጣዋለሁ ብሎ የማይሰጋ ብቸኛ አምላክ ነው ። ለአምላክነቱ የጊዜና የቦታ ዳርቻ የሌለው የሁሉ ዘመን ፣ የሁሉ ስፍራ አምላክ ነው ። አምላክነቱ ከጥንት ዘመን ጀምሮ ታውቆ የኖረ ፣ ለአምላክነቱ እንኳን ሕያው ፍጡር ግዙፍ ሰማይ አንደበት ያለው ፣ “አምላክ ነው” ብሎ የሚመሰክርለት ነው ። የእርሱ አምላክነት ከፍ ብሎ ቢታየን ፣ የሚያስጨንቁን ከፍታዎች አይኖሩም ነበር ። ሁሉ ከእርሱ አምላክነት በታች ሲሆን እርሱ ግን ማነስ የማይስማማው የዘላለም ክብር ባለቤት ነው ። “ለከፍተኛነቱም ፍጻሜ የለውም” የተባለለት ፣ በአርያም አገሩ በዓይነ ምሕረት ድሆችን የሚመለከት ነው ። ራሳቸውን አምላክ አድርገው የቀቡ ብዙ ኃያላን ነበሩ ። “ቄሣር ጌታ ነው ፣ ቄሣር የእግዚአብሔር ልጅ ነው” ብለው ያወጁ ፣ ለምስላቸውም በመንፈስ እንዲሰገድ ያዘዙ ነበሩ ። ለምስላቸው በመንፈስ ያልሰገደውን ፣ “ቄሣር ጌታ ነው” ብሎ ያልመሰከረውን በሰይፍ ይገድሉ ፣ በእሳት ያቃጥሉ ነበር ። እነዚህ ሰዎች አምላክ ነን አሉ ፣ ግን በግድ አምልኩኝ የሚሉ ነበሩ ። ሐሰት ጭካኔ ይከተለዋልና ብዙዎችን ጨረሱ ። እውነተኛው አምላክ ግን በነጻነት የሚገዛ አምላክ ነው ። የአንድ አገር ዜጋ ሁሉ ለመንግሥቱ ግብር እንዲከፍል የሰማዩ መንግሥትም ግብሩ አምልኮ ነው ።

አንድ ሰው አሥራቱን ሲሰጥ እንዲህ ሲል ሰማሁ፡- “አሥራቴን የሚቀበለኝ በማግኘቴ በምድር ላይ ዕድለኛ ሰው ነኝ” አለ ። አሥራታችንን እናቆማለን እያሉ የሚያስፈራሩ ምእመናን ባሉበት ዓለም እንዲህ የተረዳ ሰው ማግኘት ደስ ይላል ። ዕድለኛው መንፈሳዊ አገልጋዮች ወይም ቤተ ክርስቲያን አይደሉም ፣ አሥራት ሰጪው ሰው ተቀባይ ማግኘቱ ነው ። የአገራችን ሕዝብ የማይባረከው መሠረታዊ ችግሩ አሥራትን ከማይሰረቀው እግዚአብሔር ስለሚሰርቅ ነው ። አሥራትን የሚሰርቁ የእንቧይ ካብ ይክባሉ ። የሠሩት ቤትና ኑሮአቸውን ጨረስኩት ሲሉ መፍረስ ይጀምራል ። አገልጋዮችም የአሥራት አሥራት የማውጣት ግዴታ አለብን ። አሊያ ያልተባረከ ኑሮና ቤተሰብ እንይዛለን ። አዎ የምናመልከውን እውነተኛውን አምላክ ማግኘት ዕድለኛነት ነው ። ብዙዎች አላገኙም ። የአጋንንት አምልኮ ያለባቸው ሰዎች ግብር ሲደርስ ይጨነቃሉ ። ርኵስ መንፈስ ሽቶ እያስጠጣ ፣ እሳት እያስበላ ሲያሰቃይ ይታያል ። ሰይጣን ወዳጅ አያውቅም ። ስለ እግዚአብሔር ሀልወት ሳይሆን ስለ ሰይጣን አብዝተው የሚያወሩትን ብንነቅፍም ሰይጣን እንዳለም እናውቃለን ። አክብሮ የሚገዛውን ጌታ ማግኘት መታደል ነው ። ሰይጣናዊ አምልኮ ልጅን ሳይቀር መሥዋዕት አድርገው የሚያቀርቡበት ነው ። የተከለከለው ለልጃችን እንኳ የማይራራ በእሳት ውስጥ አሳልፉልኝ የሚል ጨካኝ ስለሆነ ነው ። እኛ ግን ልጅን የምንሠዋለት ሳይሆን አንድ ልጁን ሳይራራ ለመስቀል ሞት የሰጠውን እናመልካለን ።

“እግዚአብሔር አምላኬ ነው” ማለት ድንቅ ምስክርነት ነው ። እግዚአብሔር አምላኩ የሆነው ሕዝብም የታደለ ፣ የተመሰገነ ነው ። ነቢዩ ዳዊት “አምላካችን” ይለዋል ። ልዕልናው ቅርበትን ያልከለከለው ፣ ከፍታው ትሑትነትን ያላስቀረበት አምላክ አለን ። ስናከብረው የማያዋርደን ፣ ስንቀርበው የማይሸሸን አምላክ አለን ። እርሱ አምላካችን መሆኑን እንመሰክራለን ። የአገሩ መሪ ልጃቸው ቢታዘዛቸውም ባይታዘዛቸውም እርሳቸውን የሚጠላ ልጃቸውንም ሊጠላ ይችላል ። እኛም እግዚአብሔርን ብንታዘዘውም ባንታዘዘውም የእርሱ በመሆናችን ብቻ ጠላት አትርፈናል ። እርሱን የሚጠላ ይጠላናል ። እርሱን ያገኘ መስሎት ያዋርደናል ፣ ይገድለናል ። እንዳይገድሉን አድርጎ ሳይሆን እየገደሉን እንድንበዛ አድርጎ ይረዳናል ።

እግዚአብሔርንም ሰይጣንንም አናምንም የሚሉ ወገኖች ሊኖሩ ይችላሉ ። እግዚአብሔርን የምናምነው ስናምነው ብቻ ነው ። ሰይጣን ግን ረክሷልና እየሰደብነውም ሥራውን ከሠራንለት እንዳመለክነው ይቆጥረዋል ። እግዚአብሔርም ሰይጣንም የለም የሚሉ ሰዎች ይኖራሉ ። እግዚአብሔርን አለ ብሎ አለማመን ዋጋ ያስከፍላል ። አንድ ሰው በጎዳና ወጥቶ መንግሥት የለም ቢል በዝምታ አይታለፍም ። ሰይጣን ግን የለም ሲሉት የበለጠ ይደሰታል ። ምክንያቱም ጠላት የለም ብለው ሲዘናጉለት ማጥቃት ይችላል ። አምላክ ያለው ሕዝብ ፈራጅ አለው ። እግዚአብሔር አምላኩ የሆነ ሕዝብ ደመና ተጋርዶለት ፣ የውርጭ ገበታ ተዘርግቶለት ፣ መና እየወረደለት ምድረ በዳውን የሰነጠቀ ነው ።

ያለብን ችግር ምንም ይሁን ፤ ብቻ አምላክ አለን ! እርሱ እኛን ልጆቼ ማለት ካላፈረ እኛ እርሱን አምላኬ ማለት አያሳፍረንም ።

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ኅዳር 21 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ