በጸናው የምስጋና ርስትህ ፣
በማይደፈረው ግዛትህ ፣
በማይናወጸው ዙፋንህ ፣
በማይለያየው አንድነትህ ፣
በማይጠቀለለው ሦስትነትህ ፣
በማይሰጋው መንግሥትህ ፣
በማይታበለው ቃልህ ፣
በማያማክሩት ጥበብህ ፣
በማይመረመር ማስተዋልህ ፣
በማያበድሩት እውቀትህ ፣
በማይፈርስ ምክርህ ፣
በማይክደው አባትነትህ ፣
በማይቀየመው አፍቃሪነትህ ፣
በማይሰለቸው ቸርነትህ ፣
በማይገፋው ጥላህ ፣
በማያባርረው ማደሪያህ ፣
በማይዘናጋው ጥበቃህ ፣
በማይጠገበው ጣዕምህ ፣
በማይሻረው ፍርድህ ፣
በማይጨክነው ርኅራኄህ ፣
በማይጥለው ትዕግሥትህ ፣
በማይካደው ጻድቅነትህ ፣
በማያልፈው ስጦታህ ፣
በማይነጥፈው እጅህ ፣
በማይዝለው ትከሻህ ፣
በማያባራው ምስጋናህ ፣
በማይተካው ጌትነትህ ፣
በማይሰረቀው አምልኮህ ፣
በማይሞተው ሕያውነትህ ፣
በማይገሠሥ ሥልጣንህ ፣
በማያልፍ ዓይንህ ፣
በማያፈስስ ጆሮህ ፣
በማይሰበር ምክርህ ፣
በማይነገር ሐሤትህ ፣
በማይሸነፍ መድኃኒትህ ፣
በማይደመሰስ መሐላህ ፣
በማይቀር ኪዳንህ ፣
በማይከዳ ወዳጅነትህ ፣
በማይረሳ ወንድምነትህ ፣
በማያጋልጥ እናትነትህ ፣
በማይታዘብ አበ ነፍስነትህ
አቤቱ አሁን አስበን !!!
የነግህ ምስጋና /15
መጋቢት 12 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን