የትምህርቱ ርዕስ | አትፍራ

“አሁንም ያዕቆብ ሆይ ፥ የፈጠረህ ፥ እስራኤልም ሆይ ፥ የሠራህ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ተቤዥቼሃለሁና አትፍራ በስምህም ጠርቼሃለሁ፥ አንተ የእኔ ነህ ።” ኢሳ. 43፡1
አንድ ሰው፡- “ሁልጊዜ የሚጠጡ ፍጹም አያጣጥሙም ፤ ሁልጊዜ የሚናገሩ ፍጹም አያስቡም” ብሏል ። እግዚአብሔር የሚናገረንን የማናስበው ለምንድነው ? ካልን ሁልጊዜ ስለምንናገር ነው ። አስበን እንናገራለን ፣ የተናገርነውንም እናስባለን ። በዚህ ዙረት ውስጥ ስለምንሆን በምናየው በምንሰማው ተወስነን እንታወካለን ። የተጨማደዱ የሰዎች ፊት ፣ የቀዘቀዙ ሰላምታዎች ፣ ለየት ያሉ የሰዎች እንቅስቃሴዎች ደግሞ ምን እየታሰበብኝ ነው ? እያልን እንድንጨነቅ ያደርጉናል ። እግዚአብሔር የሰጠን የተስፋ ቃል ግን ከሰማይና ምድር ማለፍ የሚበልጥ ነው ። የገዛ ጥላችን የሚያስደነብረን ፣ እያንዳንዱ ኮሽታ የሚያስበረግገን ከሆነ እግዚአብሔር የነገረንን ተስፋዎች ማሰብ አልቻልንም ማለት ነው ። መናገር ብዙ ጊዜ ውጤታማ የሚያደርገን ይመስለናል ፤ ለእግዚአብሔር መናገር ሳይሆን ለሰው መናገር ድል የሚሰጠን ይመስለናል ። መናገራችን ግን እያቀጣጠለን እንጂ እያበረደን አይመጣም ። እግዚአብሔር የሰጠንን ተስፋ ስናስብ ግን መልሰን መበርታት እንጀምራለን ። “ተማሪ የለም እንጂ አስተማሪው ብዙ ነው” ይባላል ። ማኅበረሰቡ ፣ ቀኑ ፣ ክሰተቱ ፣ አደጋዎች ፣ ሰዎች የሚያልፉበት ምጥ ፣ ስህተታችን የሚያመጣብን ቊስለት ፣ ምቀኛ ጎረቤቶች የሚስገዙን ዕቃ ፣ ያለፈው ዘመን ጠባሳ ፣ ትኩሱ የኑሮ ቊስል ፣ የሞቱት ወገኖቻችን እነዚህ ሁሉ አስተማሪዎች ናቸው ። የሚማር ግን እያነሰ ነው ። በዓለም ላይ ከትምህርት ነጻ የሆነ ቀን ፣ ሰውና ክስተት የለም ። ብንማር ስጋትን እናሸንፍ ነበር ። ከልኩ አያልፍምና ።
የሰው ልጅ ፍርሃቶች ዕለት ዕለት እየጨመሩ ነው ። መኪናውን ከፍቶ የሚነዳ ፣ ቤቱን በርግዶ የሚቀመጥ ፣ ሰው አፍጥጦ ሲያየው የሚረጋጋ እየጠፋ ነው ።ፍርሃት በማያቋርጥ ሁኔታ ያዋራናል ። ለተቀመጥንበት ቤት ዋስትና ማጣት ፣ ለምንጓዝባቸው ከተሞች ያለን አመኔታ ዘወትር ይበጠብጠናል ። ሰውን መፍራት ሲጠቃለል ራስን መፍራት በመሆኑ ራሳችንን በመፍራት ተይዘናል ማለት ነው ። የእግዚአብሔር ቃል ግን “አትፍራ” ይለናል ። በቅዱስ መጽሐፍ ላይ “አትፍራ” የሚል ቃል 365 ጊዜ ተጠቅሶአል ። የዓመቱ ቀኖች 365 ናቸውና በየቀኑ አትፍራ ማለት ነው ። “አትፍራ” የሚል ድምፅ ከተሰማባቸው የቅዱስ መጽሐፍ ክፍሎች አንዱ የነቢዩ የኢሳይያስ መጽሐፍ አንዱ ነው ።
እግዚአብሔር በዚህ ስፍራ ላይ በስም የሚጠራ ወዳጅ ፣ የፈጠረ ፣ የሠራ፣ የተቤዠ እንደሆነ ተጠቅሷል ።
እግዚአብሔር በስም የሚጠራ ወዳጅ ነው ። “ሰው ሁሉ በምድር ላይ ሊሰማው የሚወደው ሙዚቃ ቢኖር የገዛ ስሙ ነው” ይባላል ። ሰዎች በስማቸው ስንጠራቸው ከፍ ያለ ደስታ ይሰማቸዋል ። የጠራቸው ሰው እንዳልረሳቸው ፣ በልቡ እንደ ጻፋቸው ፣ ዋጋ እንደ ሰጣቸው ይረዳሉ ። እግዚአብሔር በስማችን ይጠራናል ። ያውቀናል ፣ በልቡ ጽፎናል ፣ በእኛም ደስ ይለዋል ።ሰዎች በስማችን ካልጠሩን እንደ ተቀየሙን ይሰማናል ። እግዚአብሔር በስማችን ሲጠራን እንደሚወደን እንገነዘባለን ። ሰዎች በስማችን ካልጠሩን ፍርሃት ውስጣችን ይጸነሳል ። እግዚአብሔር ግን በስማችን ጠርቶናልና ልንፈራ አይገባንም ።
እግዚአብሔር የፈጠረን ነው ። ፍጡር ፈጣሪ እንዳለ ፣ ፈጣሪም ፍጡር እንዳለው ያስረዳል ። መድረክ ላይ ቆምን ባንሰብክም ህልውናችን ብቻውን እግዚአብሔር አለ ብሎ የሚመሰክር ነው ። እግዚአብሔር ካለመኖር ወደ መኖር ፍጥረትን አምጥቶአል ። በራሳችን ምክር ሳይሆን በእግዚአብሔር ምክር ይህን ዓለም ተቀላቅለናል ። የፈጠረ ከወለደ በላይ የሚወድ ነው ። እግዚአብሔር በጸጋ የወለደን አባታችን ብቻ ሳይሆን ያስገኘን ፈጣሪያችን ነው ። ሰዎች በማመን ከእግዚአብሔር ጋር ግንኙነት ባይኖራቸውም በፍጡርነትና በመግቦቱ ግን የእርሱ ጥገኞች ናቸው ። የፈጠረን አለና መፍራት አይገባንም ። የፈጠረን ሳንፈጠር ያየን ነው ። የማይወደውንም የሚፈጥር የለምና ዓለም ሳይፈጠር ወዶናል ። ስለዚህ አትፍራ ይለናል ።
“የሠራህ” ይላል ። መሬት ላይ ዝቅ ብሎ ከአፈር ቅርጽ አውጥቶ የሠራን ፣ በእስትንፋሱ ሕይወትን ለግሶ ያቆመን ፣ ከአፈርነት በአፉ ትንፋሽ ያነሣን እግዚአብሔር ነው ። ያ እስትንፋስ ባያገኘን ኑሮ አፈር ሁኑን እንቀር ነበር ። የሰማይ ወራሽ የሆነው ደግሞም ቆመን የምንሄደው በአፉ እስትንፋስ ነው ። ዓይናችን በቦታው ፣ እጃችንን በቦታው ያስቀመጠ እርሱ ነው ። የሠራን የዳሰሰን ነው ። ሌሎች ፍጥረቶች ሁሉ በቃሉ ጥሪ ካለ መኖር ወደ መኖር መጥተዋል ። ሰው ግን በእጁ ተሠርቷል ። ይህንን አካሌን መለኮታዊ እጆች አበጃጅተውታል ፣ ነክተውታል ብለን ስናስብ ፍርሃትን ድል እንነሣለን ።
“የተቤዠህ” ይላል ። የሚቤዥ ዋጋ ከፍሎ የሚገዛ ነው ። እስራኤልን በዋጋ ከግብጽ ገዝቷታል ። መላውን ዓለም ራሱን በመስቀል ላይ በመስጠት ዋጅቶታል ። የተገዛ ነገር ገዥው የጥበቃ ዋስትናም ያደርግለታል ። የተገዛ ነገር እንደውም አይፈራም ፣ ገዥው ግን ሊፈራ ይችላል ። እግዚአብሔር ግን የሚሰጋው የሌለው ገዥ ነው ። እኛም ተገዝተናል ፣ ባለቤት አለንና ልንደፍር ይገባናል ።
“አንተ የእኔ ነህ” ይላል ። የእግዚአብሔር መሆን ትልቅ ነገር ነው ። የራሳችንና የሰዎች ሁነን እናውቀዋለን ። የእግዚአብሔር መሆን ግን ትልቅ ነገር ነው ። እግዚአብሔር ይህን ማንነት የእኔ ነው ሲለው ደስታ ሊሰማን ይገባል ። እኛ ራሳችን ለመቀበል የከበደንን ማንነት ፣ ይቅር ልንለው ያልቻልነውን በደለኛነታችንን እግዚአብሔር የእኔ ነው ይለዋል ። በዚህ ዓለም ላይ የእኔ የምንለውና የእኔ የሚሉን እያነሱ ነው ። እግዚአብሔር ግን የእኔ ነህ ይለናል ። እኛ የዓለምም ፣ የቤተሰብም ፣ የሰይጣንም አይደለንም ፣ የእግዚአብሔር ነን ። ስለዚህ ልንፈራ አይገባንም ። በብዙ ነገር ራሳችንን እንፈራዋለን ። እግዚአብሔር ካልሰለጠነበት ይህ ማንነታችን የሚሆነውን ነገር ገና በመስጋት እንደነግጣለን ። እኛ ግን የእኛ አይደለንም ፣ እኛ የእግዚአብሔር ነን ።
ሐዋርያው ጳውሎስ፡- በዋጋ ተገዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም ፤ ስለዚህ በሥጋችሁ እግዚአብሔርን አክብሩ” ይለናል ። 1ቆሮ. 6፡20 ። የራስ መሆን ከባድ ነው ። ሥጋችን ወደ ገደል የሚነዳን ነው ። እኛ የእግዚአብሔር ነን ። ይህን የተረዳን ቀን በሥጋችን እርሱን ለማክበር እንነሣለን ። ብዙ ሰው በሥጋው እግዚአብሔርን ማክበር እንደማይችል ፣ ይህን ዓለም ካለቀቀም የእግዚአብሔር እንደማይሆን ያስባል ። መንፈስ ቅዱስ ግን ማኅደረ ሥላሴ ሊያደርገን መጥቷልና በሥጋችን እርሱን ልናከብር ይገባናል ። ዛሬ ብንወድቅም ብንነሣም የእግዚአብሔር ነንና ልንፈራ አይገባንም ። ፍርሃታችንን ድል የምንነሣበት ቀን ይሁንልን ።
የወደቀን የምታነሣ ፣ የቆሰለን አልፈህ የማትሄድ ፣ እረኛ ለሌለው እረኛ ፣ ሰሚ ላጣ አድማጭ የሆንህ እግዚአብሔር ሆይ አመሰግንሃለሁ ። ብዙ ልመና በፊት አቅርቤአለሁ ፣ የአንተን ቃል ግን በልቤ መጻፍ አልሆነልኝም ። እየተናገርከኝ እፈራለሁ ። ባትናገረኝ ምን ልሆን ነው ? ይህን ማንነቴን ውሰደውና አዲስ ልብ ፍጠርልኝ ። አንተን በማመን አጽናኝ ። ለዘላለሙ አሜን ።
የዕለቱ መና 27
ግንቦት 27 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም