መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » አንተ ግን ….

የትምህርቱ ርዕስ | አንተ ግን ….

በደቂቃ ነገሮች በሚለዋወጡበት ዓለም አንተ ግን በስፍራህ ፣ አንተ ግን በህልውናህ ጽኑ ነህ ። ሰዎች ሥሩልኝ ሳይሆን ልሥራላችሁ ቢባሉ በቅን በማይመለከቱበት ዓለም ፣ አንተ ግን የበደሉህን በፍቅር ታያለህ ። መጠባበቅ በዝቶ ፣ ጣልና ልጣልልህ የሚል የዕቁብ ኑሮ ደርቶ ቢታይም ፣ አንተ ግን ሁሉን በጸጋ ትለቃለህ ። የጸናውን ለመንቀል ፣ ያመነውን ለማስካድ ትግል ባለበት ዘመን ፣ አንተ ግን ፈሪውን ታበረታለህ ። ጻድቁን በሚያረክሰው ዓለም ፣ አንተ ግን ደካማውን ብርቱ ነህ ትላለህ ። ጀርባን እያየ ፣ “ማን አለው?” ብሎ ዙሪያን እያጠና በሚያፈቅረው ዓለም ፣ አንተ ግን የብቸኛው ወዳጅ ነህ ። ጊዜ ከድቶት አንገት ሲደፋ ፣ በወደቀው ላይ ምሣር ሲበዛ አንተ ግን መፍረድ ስትችል ትምራለህ ።

“አንቱ” ያለውን ሰው “አንተ” ለማለት በሚጣደፈው ዓለም ላይ ፣ አንተ ግን ከፍታህ ዝቅታ ፣ ክብርህ ማዋረድ የለበትም ። እጅግ የወደደ እጅግ በሚጠላበት ዓለም ፣ አንተ ግን እስከ መጨረሻው ትወዳለህ ። ያገለገለ ሰው “አህያ” በሚባልበት ዓለም ፣ አንተ ግን የተናቀውን ታከብራለህ ። ሥራን ትቶ ስፍራን በሚሻው ዓለም ላይ ፣ አንተ ግን ዝናን ታስንቃለህ ። ያልፈጠረው ላይ በሚጨክነው ዓለም ውስጥ ፣ አንተ ግን ፍጥረትህ ነውና ለሁሉ ትራራለህ ። የፈተናው ነፋስ የተሰበሰበውን ስንዴ በሚበትንበት ዓለም ፣ አንተ ግን “ትጉና ጸልዩ” ትላለህ ። በአንድ ጆሮ ሰምቶ በሌላው በሚያፈስሰው ዓለም መካከል ፣ አንተ ግን የነገሩህን ላትረሳ ትሰማለህ ። “እርሱ ነው ፣ እርሷ” የሚል ክስ በበዛበት ዓለም ፣ አንተ ግን ሁሉን ለንስሐ ትጠራለህ ።

ቃላቸውን ለመፈጸም ዳተኛ ፣ ለመድረስ ዘገምተኛ የሆኑ በበዙበት ዓለም ፣ አንተ ግን ደመና ጠቅሰህ ፣ ባሕር ተራምደህ ትደርሳለህ ። ለማክበር ተሰባስቦ በሚያዋርድ ፣ ለድጋፍ ሰልፍ ወጥቶ በሚቃወም ዓለም ላይ ፣ አንተ ግን ላታሳንስ ከፍ ታደርጋለህ ።

አንተ እንደ እኔ ፣ አንተ እንደ ሰዎች ፣ አንተ እንደ ጊዜው አይደለህም ። አንተ መግለጫ ፣ አንተ እኩያ ፣ አንተ አምሳያ ፣ አንተ ተቀራራቢ ፣ አንተ ተካካይ ፣ … የሌለህ ብቸኛ ነህ ። ያህዌ አንተ ግን ያው አንተ ነህ ። የሚወድህ ሁሉ አሜን ይበል !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ተጻፈ ሰኔ 23 ቀን 2015 ዓ.ም

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም